>

በሥጋ እየሞትን በመንፈስ እየኖርን እግዚአብሔርን እናመልካለን (ቀሲስ ዘላለም ጽጌ)

ትላንት የተከበረው የጥምቀት በዓል በሀገራችን በኢትዮጵያ እና በሌችም ሀገራት የነበረው ገጽታ ደስታም ሀዘንም የቀላቀለ ነበር። የበዓሉን አከባበር በተለያዩ መገናኛዎች ስንመለከት በደስታ አክብረው ወደ ቤታቸው የተመለሱ እንዳሉት ሁሉ ህይዎታቸውን ያጡና በሀዘን በለቅሶ ላይ ያሉ ወገኖቻችን እንዳሉ ለማየት ችለናል። የሚገርመው ከዚህ ቀደም የክርስቲያኖች ደም ሲፈስ የነበረው በአረቡ ሀገራት ነበር። የአሁኑ ግን የተገላቢጦሽ በአረብ ኢምሬትስ በሰላምና በደስታ በድምቀት ሲያከብሩ ባየንበት ዓይናችን የክርስቲያን ደሴት በተባለችው ኢትዮጵያ የወጣቶች ደም ሲፈስ፣ የእናቶች እንባ ሲረጭ፣ የቃልኪዳኑን ታቦት በተሸከሙ ካህናት ላይ የአድማ መበተኛ ጭስ ሲወረወር ለማየት በቃን። ይህ ነገር በእኔ መረዳት የቤተክርስቲያንን ሥም ለማጉደፍ የተሰራ ተንኮል እንደሆነ ይሰማኛል። በየእለቱ ስለ ዓለም ሰላም የምትጸልይና የምታስተምር ቤተክርስቲያን ሰላም አስከባሪ ምን ያደርግላታል?። ሰበብ ተፈልጎ የንጹሃንን ደም ለማፍሰስ ታስቦ የተደረገ ይመስላል። እኛ ስናውቅ የኢትዮጵያ ፓሊሶች በጥምቀት እለት እንኳን መሳሪያ ተኩሰው ሰው ሊገድሉ ይቅርና በራሳቸው ያለ ኮፍያ አውልቀው ከህዝቡ ጋር የሚዘምሩ ነበሩ። ታቦት የተሸከሙ ካህናት ላይ የሚተኩስ ኢትዮጵያዊ እያፈራን ነው ማለት ነው? እንንኳን ከርስቲያኑ ሙስሊሙ ለእግዚአብሔር ታቦት ክብር ይሰጥ እንደነበር እናውቃለን።

ቤተክርስቲያን እንዳስተማረችን ወደ እግዚአብሔር ለሄደው፣ ክብር ላገኘው አይደለም የምናዝነው ህሊናው ታውሮ እንደ ቃኤል የወንድሙን ደም ለሚያፈሰው እንጅ። በተለያየ ምክንያት ክርስቲያኖችን የምትገድሉ ወዮላችሁ። ነገር ግን ምናልባት በመግደላችሁ እነሱን የጎዳችሁ ከመሰላችሁ አሁንም እላለሁ ለእናንተ በብዙ አዝናለሁ ወዮላችሁ። ክብር እንጅ የምታጎድሉባቸው ነገር የለም። ሰይጣን ዲያቢሎስ አዳምን ለሞት የሚያበቃ ተንኮል ቢሰራበት በኋለኛው ዘመን አምላክ ሰው ሆኖ ሰው አምላክ እንዲሆን ነው ያደረገው። የምድሩን ክብር ለማሳጣት ተንኮል ቢሰራበት ሰማያዊ ክብር እንዲጨመርለት ነው ያደረገው። ክርስቲያን በሥጋ ከሚኖረው ይልቅ ከሞተ በኋላ የሚያገኘው ክብር ። ይበልጣል። እኛ አባታችን በሰማይ ነው።”፤ እግዚአብሔር በተቀደሰው መቅደሱ ነው፤ እግዚአብሔር፥ ዙፋኑ በሰማይ ነው፤ ዓይኖቹ ወደ ድሃ ይመለከታሉ፥ ቅንድቦቹም የሰው ልጆችን ይመረምራሉ። ” (መዝ 11: 4) “፤ እኛ አገራችን በሰማይ ነውና፥ ከዚያም ደግሞ የሚመጣ መድኃኒትን እርሱንም ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንጠባበቃለን፤ ( ፊልጵ3:፥20)።” ስለዚህ እናንተ ገዳዮች የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ። እየሞታችሁ ያላችሁ እናንተ ናችሁ። ክርስቲያን ቢሞት ወደ ተሻለ ቦታ፣ ወደሚወደው ወደ አባቱ ወደ እግዚአብሔር ፣ ወደ ዘላለም መኖሪያ ሀገሩ መንግስተ ሰማያት ነው የሚሄደው ። ብትገድሉትም ብትተውትም የሥጋ ሞት አይቀርም።የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ይላል። ” ከእኛ አንድ ስንኳ ለራሱ የሚኖር የለምና፥ ለራሱም የሚሞት የለም፤ በሕይወት ሆነን ብንኖር ለጌታ እንኖራለንና፥ ብንሞትም ለጌታ እንሞታለን። እንግዲህ በሕይወት ሆነን ብንኖር ወይም ብንሞት የጌታ ነን ሮሜ 14፥7 ” ዛሬ ህሊናችሁ ታውሮ ማየት ቢሳናችሁ የፍጥረታት ባለቤት ለፍጥረቱ የሚፈርድበት ጊዜ አለና ንስሃ ግቡ። ” ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ቅዱስ ነውና፥ ያውም እናንተ ናችሁ። ” (1ኛ ቆሮ 3: 17) ተብሎ እንደተጻፈ ዛሬ እንደቀላል የምታፈሱት ደም ነገ ብዙ ዋጋ ያስከፍላልና ቆም ብላችሁ አስቡ። “፤ እናንተ አሁን የጠገባችሁ ወዮላችሁ፥ ትራባላችሁና። እናንተ አሁን የምትስቁ ወዮላችሁ፥ ታዝናላችሁና ታለቅሱማላችሁ። ” (ሉቃ 6: 25) ።

Filed in: Amharic