>

ወልድያ የጦር ቀጠና ሆናለች -  ትንቅንቁ ቀጥሏል! (ክንፉ አሰፋ)

ወልድያ የበቀል ዱላ አትፎባታል። ግድያና አፈናው ለሶስተኛ ቀን ቀጥሎ ውሏል። የወያኔ ቅልብ ጦር የጅምላ ግድያውን የፈጸመው ከዚህ ቀደም በወልድያ ስታድየም የተፈጠረውን ክስተት ለመበቀል መሆኑን ብዙዎች ይስማማሉ።

ከልምድ እንዳየነው ህወሃት ሕዝብን መጨፍጨፍ ሲፈልግ –  አጋዚ ወታደሮቹን ሕዝብ በሚሰበሰብበት ስፍራ ያሰማራና  በመተንኮስ እንዲነሳሱ ያደርጋል።  ብሶቱ ከቅጥ ያለፈበት ሕዝብ ድምጹን ማሰማት ሲጀምር ህወሃት የበቀል ስራውን ይሰራል።  ከዓመት በፊት የእሬቻ በዓል ላይ  የሆነው ይኸው ነበር።  በወልድያው ጭፍጨፋም ያየነው ይህንኑ ነው።

የቴዲ አፍሮ የባህርዳር ኮንሰርት ላይ አጋዚ ቢኖር ኖሮ እልቂቱ አይቀሬ ነበር።  የዘንድሮው እሬቻ በዓል ከአጋዚ ነጻ ቢሆን  እንደ  አምናው ወገን ይገደል ነበር።

እለተ ቅዳሜ፣ ጥር 12 ቀን 2010 ዓ.ም.  የጥምቀት በዓልን ለማክበር የታደመ ሕዝብ ላይ የጥይት ናዳ ወርዷል። የደብረጺዮን ታዛዦች በታቦት ፊት የንፁሀንን ደም አፍስሰው ህዝቡን በደም አጥምቀውታል።  ይህ ግድያ በእጅጉ  ከልክ ያለፈ፣  ፍጹም አረመኔያዊ ድርጊት ነው።

እርግጥ በአስተሳሳባቸው ገና ከጫካ  ያልወጡ ጉዶች ለሰው ልጅ ክብር ሊኖራቸው አይችልም።  ታቦት ስር ገብቶ ደም ማፍሰስ ግን እምነትንም፣ ፈጣሪንም መድፈር ይሆናል። ከሰው የተፈጠሩ ቢሆኑ ኖሮ፣  ችግር እንኳን ቢፈጠር ታቦቱ በክብር እስኪገባ ጠብቀው መግደል ይችሉ ነበር። እንዲህ አይነቱ ንቀት በቀይ ሽብር ግዜም የተከሰተ አይመስለኝም።  እርግጠኛ ልንሆን የምንችለው ይህ ነገር እንደሌሎቹ ግድያዎች አሻራ ጥሎ  ብቻ የሚያልፍ አለመሆኑን ነው።

ለሰሩት ሁሉ  ይከፍሉበታል!  ለዚህም ይመስላል  ይህ  ግድያ፣  ይህ ጭካኔ ፣ ይህ ግፍ  ዝም ሊባል አይገባም ሲል ሕዝብ ያመረረው።  “የሞተ አህያ ጅብ አይፈራም” እንዲሉ በቁም የገደሉት ሕዝብ ተቃውሞውን ዛሬም ቀጥሏል።  አውራ መንገዶችን እየዘጋ፣ የህወሃት የሆነውን ንብረት እያወደመ አመጹን ቀጥሎበታል።

አነጣጥረው የሚተኩሱ  የወያኔ- አጋዚ ወታደሮች በወልድያ ቀድመው በመግባት አመቺ የሆነ ስፍራ ይዘው እንደነበር እማኞች ይናገራሉ።  ላለፉት ሁለት አመታት በነበረው አመጽ የወሎ ዝምታ ስርዓቱን ስጋት ውስጥ ከትቶት እንደነበርም ግልጽ ነው።  ወሎ የፍቅር ሕዝብ ነው። ፍቅርን ጥግ እንደሚተገብር ሁሉ ሲደፍሩት ደግሞ የጭካኔ ጫፍንም ያውቅበታል።

የወሎ ዝምታ ስርአቱን  በእጅጉ አስፈርቶት ነበር። ወያኔ በእንዲህ አይነቱ አረመኔያዊ ጭፍጨፋ፣  ሽብር ፈጥሮ፣  ዝምታውን መስበር የተጠቀመበት ታክቲክ ሊሆን ይችላል።    ዝምታውን ለመስበር ሲል በዚህ መልኩ የንጹሃንን ደም ማፍሰሱን እንደ መፍትሄ መውሰዱ ግን ከፍተኛ ዋጋ እንደሚያስከፍለው የተረዳው አሁን ነው።  ባይተዋር ታጣቂዎች ከበዓሉ በፊት ወደ ወልድያ መግባታቸው ግድያው ታስቦበት እና ተጠንቶበት መሆኑን ያስረግጥልናል።

በወሎ ውስጥ ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው። በደሴ፣ በወልዲያ እና በኮምቦልቻ ሕዝብ በነቂስ ወጥቶ የወያኔ-አጋዚን የግድያ ወንጀል እንዲያወግዝ የሚደረገው ቅስቀሳ ቀጥሏል። በበርካታ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ግድያ እና ደም ማፍሰስ ወንጀል ተፈጽሞ መላቀቅ እንደማይኖር ሕዝቡ እየተናገረ ነው።

ዜናው ሁሉ የግድያ ሆነና ሕዝቡም አለም ዓቀፉ ህብረተሰቡም ለመደው።  ከትላን በስትያ ዜጎች ተገደሉ፣ ትናንትናም ዜጎች  ተገደሉ፣ ዛሬም ተገደሉ፣ … ዜጎች እንደዋዛ ይገደላሉ፣ ወገን እንደ ዛፍ ግንድ ይጨፈጨፋል፣ ሕዝብ ይሰማል፣ ሕዝብ ይጮሃል፣ ከዚያም ይረሳዋል።  የአጋዚ ሃይሎችም ባሰኛቸው ግዜ ዜጋውን እየተኮሱ የሚገድሉት፣ ይህ ሕዝብ ዛሬ ይጮህና ነገ ይረሰዋል በሚል እሳቤ ይመስላል።

ለቅሶ እና ቀብር ላይ ሰው የሚገደልበት ሃገር፣ በቤተ መቅደስ እና በመስጊድ ህይወት የሚጠፋበት ሃገር፣ በእግር ኳስ ጨዋታ ደጋፊዎች የሚተኮስባቸው ሃገር…   ሌላው ቀርቶ ኮንሰርት ማዘጋጀት ብርቅ የሆነበት ሃገር… ባጠቃላይ የመኖር ዋስትና የሌለበት ሃገር!  ይህ እንዴትስ ሆኖ ሊለመድ  ቻለ?

ማማው ላይ ያወጣቸው፣ ይህንን ሕዝብ ንቀውታል።      አስተሳሰባቸው  አሁንም ከጫካ ለልወጣ  እነዚህ ድኩማን  ንፁሃንን መግደል የችግሮቻቸው መፍትሄ አድርገው ነው የሚወስዱት። ይህ አካሄዳቸው ግን እንደማይቀጥል ቄሮ እና ፋኖ በሚገባቸው ቋንቋ እየነገራቸው ይገኛል። በወልድያም ደም ፈስሶ እንቅልፍ እንደሌለ እነሆ  እያሳየን ነው።

ትእቢት ውድቀትን ትቀድማለች!

በቀጣዩ ጽሁፌ ስለ ቴዲ አፍሮ የባህርዳርና ቀጣይ ኮንሰርት ከመጀመርያ ምንጭ ያገኘሁትን አስደማሚ  መረጃ ጀባ እላለሁ።

Filed in: Amharic