>

በዶ/ር ታደሰ ክስ የቀረቡ ማሰረጃዎች ውድቅ ተደረጉ እገዳውም ተነሳላቸው (በወንድወሰን ተክሉ)

አስራ ሁለት አባላት ያለው ሸንጎ[ጁሪ]የክሱን ጭብጥ ዛሬ መስማት ጀመረ

ልዩ-ሪፖርታዥ ከስናርስብሩክ ክራውን ችሎት

ወንድወሰን ተክሉ

በከሳሹ የእንግሊዝ መንግስት አቃቤ ሕግ በሽብርተኝነት ጋር በተያያዘ ጥርጣሬ በሎንደን ተከሰው ጉዳያቸውን መከታተል የጀመሩት ዶ/ር ታደሰ ብሩ በዛሬው እለት ችሎት ውሎዋቸው ዳኛው የተጣለባቸውን ለፕሬስ የመግለጽ እገዳ እንዳነሱላቸው ባለደረባችን ከችሎት ዘግባል። በትናትናው የችሎት ውሎ በአቃቤ ሕግ በኩል የክሶቹ ማስረጃ መረጃዎች በማለት ለችሎቱ የተሰጠውን ከ300ገጽ በላይ ዶሴ ዳኛው “ለማስረጃነት ለመቀበል ይዘቱ ብቁ አይደለም” በማለት ውድቅ እንዳደረጉት ባለደረባችን ገልጻል።

በትናትናው ውሎ የተመረጡት ስድስት እንስቶችና ስድስት ተባእት የሸንጎ [ጁሪ ]አባላት ዛሬ ከጣቱ 11:20ሰዓት በሃላ በአቃቤ ሕጉ ሲነበብ የነበረውን ክስ ማዳመጥ መጀመራቸው ተገልጻል። በዶ/ር ታደሰ ብሩ ላይ በእንግሊዝ መንግስት አቃቤ ህግ የተመሰረተውን ክስ እየተመለከተ ካለው ስናርስብሩክ ክራውን ፍርድ ቤት ሁለተኛ ቀን ውሎን ባልደረባችን ከስፍራው የዘገበልንን ሪፖርታዥ እንደሚከተለው አቅርበናል።

**ከ900በላይ ገጽ ያለው የክስ ዶሴ ለ12ቱ ሸንጎ አባላት ታድሎ መነበብ ተጀምራል- ዶ/ር ታደሰ ብሩ በከሳሽ አቃቤ ህግ ጀምሰን ከሳሽነት ከታህሳስ 2015 እስከ 2016 ድረስ ለበርካታ ግዜያቶች ወደ ኤርትራ በመመላለስ በለንደን የጸረ-አሸባሪ ፖሊስን እይታ ለመሳብ ችለዋል በማለት ከሳሹ የክሱን መነሻ ለማሳያት የጣረ ሲሆን “በመስከረም ወር ላይ ከኤርትራ ሲመለሱ ሂትሮው ዓለም አቀፍ አይሮፕላን ጣቢያ በተያዙበት ሰዓት በርካታ ዶሴዎችን በእጃቸው ለማግኘት ችለናል”በማለት ለችሎቱ አስረድታል።

እንደ ከሳሽ አቃቤ ህግ ክስ አመሰራራት በግሪንዊች ዩንቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ሌክቸረር ከሆኑት ዶ/ር ታደሰ ብሩ ስራና ሙያ ጋር ተያያዥነት የሌለው ዘርፈ ብዙ ዶሴ ከአስመራ ሲመለሱ በእጃቸው[በላፕ ቶፓቸው]መገኘቱን ገልጾ ዶሴውም ከአመጽና ሽብር ተግባር ጋር የተያያዘ በመሆኑ የኤርትራን ጉዞዋቸውን ምክንያት እንደተረዳ በመግለጽ ለችሎቱ አስደምጣል። ይህ የአቃቤ ህግ በዶ/ር ታደሰ ብሩ እጅ ላይ የተገኘው ዘርፈ ብዙ ዶሴ ምሁሩ ወደ ኤርትራ የሚመላለሱበት ዋና ምክንያት ብሎ እንዲያምን እንዳደረገው ከአገላለጹ መረዳት የተቻለ ሲሆን አገኘሁ ባለው ዶሴ ላይ ተመስርቶ ዶ/ሩን በ2000 እና በ2006 ላይ በጸደቀው የእንግሊዝ ጸረ ሽብር ህግ አንቀጽ 58እና 8መሰረት የሽብርተኛነት ክስ ሊከፍትባቸው እንደቻለ መረዳት ተችላል።

“በአንድ ወቅት እጅግ ወዳጃሞች የነበሩት ኢትዮጵያና ኤርትራ ዛሬ የመረረ ጠላታሞች ሆነው ሳለና ዶ/ር ታደሰ ብሩም ኢትዮጵያዊ ሆኖ ሳለ ምን ሊያደርግ ነው ወደ አስመራ ሲመላለስ የከረመው”በማለት አቃቤ ህጉ ይጠይቅና እራሱ ሲመልስም “ምክንያቱም ዶ/ሩ በእጃቸው በተገኘው ዶሴ መሰረት በኤርትራ ያሸመቀውን ጸረ የኢትዮጵያ መንግስት አማጺን ለመርዳት ነው” ሲል እራሱ ይደመድማል።

አቃቤ ህግ በዶ/ሩ የግል ላፕቶፕ ውስጥ ተገኘ ያለው ዘርፈ ብዙ ዶሴ ከኢንተርኔት ላይ የተሰበሰበ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን ለአንድ አማጺ ሃይል በወታደራዊ ስልትና ስልጠና፣በተለያየ ጦር መሳሪያ፣አደረጃጀትና አወቃቀር ደረጃ ጠቂሚ ናቸው ብሎ አቃቤ ህግ እንዳመነ በመግለጽ ዶ/ሩ ላይ የአሸባሪነት ክስ መክፈቱን ሲገልጽ ዶ/ር ታደሰ ብሩ አባባሉን በማስተባበል ሀሰት ሲሉ እራሳቸውን ተክላክለዋል።

አንድ የንግሊዝ ሚይል የተባለ ጋዜጣ ዛሬ ባወጣው ዜና ላይ አጠቃላይ የአቃቤ ህግን መክሰሻ ፋይል በመጠቀም ለአንባቢያን ሚዛኑን የሳተ ዘገባ ያቀረበ ቢሆንም ጋዜጠኛው የዶ/ሩን አሸባሪነትን ክስ ባስተጋባበት ላይ ‘Certainly, there was nothing to suggest a man involved in political violence or, to put it another way, a man involved in terrorism.በመሰረቱ ዶ/ሩ በማንኛውም አመጽም ሆነ ሽብርተኝነት የተሳተፉበት ሁኔታ መኖሩ መናገር አይቻልም ያልም ሲል ስለክሱ ዘግባል።

በችሎቱ የነበረው ባለደረባችን እንደዘገበው ከሆነ እንግሊዚዊው አቃቤ ህግ ጀምሰን አቀራረቡና ክሱን ያዋቀረበት ጭብጥ በኢትዮጵያ መንግስት በተቃዋሚዎች ላይ የሚያካሂደውን ክስና የማጥቃት ሁኔታ ጋር ተመሳሳይ ሆኖ እየታየ ሲሆን ክሱ የእንግሊዝ መንግስት ነው ወይስ የኢትዮጵያ ክስ ነው ያሚያስብል እንደሆነ ከሂደቱ መረዳት ተችላል።

እስከአሁን በቀረቡትና በተሰሙት የአቃቤ ህግ ክሶችና ማስረጃዎች ላይ በአንዱም ገጽም ሆነ በአንዲትም ቃል ቢሆን በዶ/ር ታደሰ ብሩ የተፈጸመ ተብሎ የተነገረ የሽብር ጥቃትም ይሁን ተግባር እንደሌለ ማረጋገጥ ተችላል። ችሎቱ ነገም የሚቀጥል ሲሆን አቃቤ ህግ ለሸንጎዎቹ ዛሬ ማሰማት የጀመረውን የክሱን ዝርዝር ማሰማት ይቀጥላል ተብላል።

ዶ/ር ታደሰ ብሩ በ2009 ወደ እንግሊዝ ሀገር የተሰደዱ ምሁርና ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሲሆኑ የጥገኘት[ስደተኛነት]መብት ተሰጥቶዋቸው በግሪንዊች ዩንቨርሲቲ ኢኮኖሚክስና ቢዝነስ ዲፓርትመንት ውስጥ በሌክቸረርነት እየሰሩ ያሉ መሆናቸውም በችሎቱ ተገልጻል።

Filed in: Amharic