>

የጠ/ሚ ሃይለማሪያም ስልጣን መልቀቅ ለኢትዮጲያ ትልቅ ውለታ ነው! (ስዩም ተሾመ)

ባለፈው ባወጣነው ፅሁፍ የፖለቲካ አመራር ብቃት የሌላቸው መሪዎች ለሀገር ሰላም፥ ልማትና ዴሞክራሲ “እንቅፋት” እንደሚሆኑ በዝርዝር ተመልክተናል። በመጨረሻም፣ በሀገራችን ወቅታዊ ፖለቲካ ላይ በግልፅ የሚስተዋለው ችግር የመልካም አስተዳደር ወይም የኪራይ ሰብሳቢነት ችግር ሳይሆን የፖለቲካ አመራር ብቃት ማነስ እንደሆነ በፅሁፉ ተጠቁሟል። ከዚህ አንፃር፣ “የኢህአዴግ መንግስት የፖለቲካ አመራር ብቃት እንዴት ይታያል?” የሚለውን በዚህ ፅሁፍ በዝርዝር እንመለከታለን።
በእርግጥ በሀገራችን ፖለቲካዊ ሁኔታ ላይ የሚሰጥ ማንኛውም ሃሳብና አስተያየት ከጭፍን ድጋፍ ወይም ተቃውሞ ስለሚቆጠር በአንድ ነገር ላይ በግልፅ ተነጋግሮ መግባባት አስቸጋሪ ነው። አሁንም ቢሆን ስለ ጠ/ሚ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ አመራር ብቃት የግል አስተያየቴን ስሰጥ “የመንግስት ተቃዋሚ ስለሆነ ነው” መባሉ አይቀርም። ነገር ግን፣ እያንዳንዱ ኢትዮጲያዊ “ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የፖለቲካ አመራር ብቃት አላቸው ወይስ የላቸውም?” የሚለውን ጥያቄ መጠየቅና ተገቢ የሆነ ምላሽ የማግኘት መብት አለው። ጥያቄው ስለ ግለሰቡ የግል ባህሪና ብቃት አይደለም። ከዚያ ይልቅ፣ የሕዝብን ሰላምና ደህንነት፣ የሀገርን ልማትና ዴሞክራሲ ከማረጋገጥ አንፃር የሕልውና ጥያቄ ስለሆነ ነው።

በ2008 ዓ.ም መጋቢት ወር ላይ የመንግስታቸውን የስድስት ወር አፈፃፀም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት ሲያቀርቡ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ በሀገሪቱ ለተፈጠሩት አለመረጋጋቶችና ችግሮች በመንግስታቸው ስም “የኢትዮጲን ሕዝብ ይቅርታ እንጠይቃለን” ማለታቸው ይታወሳል። ጠ/ሚኒስትሩ አያይዘውም

በኦሮሚያና አማራ አንዳንድ አከባቢዎች ለተከሰተው ግጭትና አለመረጋጋት ሌላ ተጨማሪ ምክንያት ሳናቀርብ በመልካም አስተዳደር እጦት ምክንያት ሕዝቡ ምሬት ስላለው የተፈጠረ መሆኑን ተገንዝበናል 

ብለው ነበር።
በ2008 ዓ.ም የመጀመሪያ ግማሽ አመት በሀገሪቱ ለተፈጠረው የፖለቲካ አለመረጋጋት ችግር ዋና መንስዔው የመንግስት አስተዳደራዊ ስርዓት ከሆነና ለተፈጠረው ችግር የሀገሪቱ “ጠቅላይ ሚኒስትር” ሕዝቡን በይፋ ይቅርታ ከጠየቁ በኋላ አስተዳደሩ ይህን ተግባራዊ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል። በመንግስታዊ መዋቅሩ መሰረት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የሀገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን እንደመሆናቸው፣ በስራቸው ያሉት ሁሉም የሥራ ኃላፊዎች የእሳቸውን መመሪያ ተግባራዊ የማድረግ ኃላፊነትና ግዴታ አለባቸው።
ነገር ግን፣ በቀጣይ ወራት የታየው ግን ከዚህ የተለየ ነው። በተለያዩ አከባቢዎች ዜጎች ለአመፅና ተቃውሞ አደባባይ በወጡ ቁጥር የፀጥታ ኃይሎች እንዳለፈው ግዜ መደብደብ፣ ማስርና መግደል ቀጠሉ። በግንቦት 2008 አጋማሽ ላይ ሁኔታው ያሳሰባቸው አንጋፋው የኦሮሞ መብት ታጋይ ኦቦ ሌንጮ ለታ “Who is in control of Ethiopia” በሚል ርዕስ ያቀረቡት ትንታኔ በማሳያነት የሚጠቀስ ነው። እንደ እሳቸው አገላለፅ፣ የሀገሪቱ የፀጥታ ኃይሎች እና በተለያየ ደረጃ ያሉ የመንግስት ኃላፊዎች የጠቅላይ ሚኒስትሩን መመሪያ አልተቀበሉትም፣ ወይም ለተግባራዊነቱ በቁርጠኝነት አልተንቀሳቀሱም።
ከላይ እንደተጠቀሰው፣ የሀገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ በመጋቢት ወር ላይ ሕዝብን ይቅርታ የጠየቁበትና ለችግሩ መንስዔ ነው ያሉትን የመልካም አስተዳደር እጦት በዘላቂነት ለመቅረፍ በይፋ የሰጡት መመሪያ በተለያዩ ደረጃ ባሉ የመንግስት ኃላፊዎችና ተቋማት ተቀባይነት አግኝቶ በአግባቡ ተግባራዊ አልተደረግም። “ለዚህ ዋናው ተጠያቂ ማን ነው?” ካልን ራሳቸው ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ናቸው። ምክንያቱም፣ በመንግስታዊ መዋቅሩ መሰረት የሀገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን እንደመሆናቸው መጠን፣ ለሁሉም የመንግስት ተቋማትና ኃላፊዎች የበላይ ኃላፊ ናቸው። በመሆኑም፣ በስራቸው ላሉ ተቋማትና ኃላፊዎች አፈፃፀም ተጠያቂ ናቸው።
እንደ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ያለ ባለስልጣን ሥራና ኃላፊነት በስሩ ያሉ የመንግስት ኃላፊዎችና ተቋማት ስራቸውን በአግባቡ እንዲሰሩ ማስቻል ነው። እነዚህ የመንግስት ተቋማትና ኃላፊዎች ከሕዝብና መንግስት የተጣለባቸውን ኃላፊነትና ግዴታ በአግባቡ መወጣት ከተሳናቸው የበላይ ኃላፊው ሥራና ኃላፊነቱን በአግባቡ አልተወጣም ማለት ነው። በዚህ መሰረት፣ በመጋቢት 2008 ዓ.ም በተለያየ ደረጃ ያሉ የመንግስት ኃላፊዎችና ተቋማት የጠቅላይ ሚኒስትሩን ውሳኔና መመሪያ ተቀብለው ተግባራዊ ካላደረጉ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የሚጠበቅባቸውን የአመራርነት ሚና በአግባቡ አልተወጡም።
ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እንደ ሀገር መሪ፤ አንደኛ፡- የሰጡትን መመሪያ ተቀብሎ በሚፈለገው ደረጃ ተግባራዊ ማድረግ የማይችሉ ሥራ አስፈፃሚዎችን በመሾማቸው፣ ሁለተኛ፡- አንደኛ ላይ የተጠቀሱትን ሥራ አስፈፃሚዎች በኃላፊነት እንዲቀጥሉ በማድረጋቸው፣ ቢያንስ ከመጋቢት 2008 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች ለተፈጠረው የፀጥታና አለመረጋጋት ችግር፣ በዚህም በሰው እና ንብረት ላይ ለደረሰው ጉዳት ግንባር-ቀደም ተጠያቂ ናቸው። በአጠቃላይ፣ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የኢትዮጲያን ሕዝብ ሰላምና ደህንነት፣ እንዲሁም ልማትና ዴሞክራሲ ለማረጋገጥ የሚያስፈልገው የፖለቲካ አመራር ብቃት እንደሌላቸው በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። የኢትዮጲን የፖለቲካ ሁኔታ በቅርበት የሚከታተሉ ሰዎችም ይኄን ያረጋግጣሉ።
ለምሳሌ፣ ባለፈው አመት ታዋቂው የ“Newyork Times” ጋዜጠኛ “Jeffrey Gettleman” ባወጣው ፅሁፍ በኢትዮጲያ ለሚታየው አመፅና አለመረጋጋት ሦስት መሰረታዊ ምክንያቶችን ይጠቅሳል። ከእነዚህ ውስጥ ሦስተኛ ላይ የተጠቀሰውን ምክንያት፣ “Third reason behind the unrest is the loss of Meles Zenawi” በማለት ገልፆታል። አንደ እሱ አገላለፅ፣ አቶ መለስ ዜናዊ ነገሮችን ከተለያየ አቅጣጫ የማየትና መገንዘብ የሚችሉ ብልሃተኛ መሪ ነበሩ። በተለይ የአለመረጋጋት ምልክቶችን ቀድመው መገንዘብ እና በተላላኪዎች አማካኝነት እንቅስቃሴውን ቶሎ ማኮላሸት ይችላሉ። በእሳቸው እግር የተተኩት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ግን ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎችን ቀድሞ ለመገንዘብና ለመቆጣጠር የሚያስችል ተግባራዊ ልምድና ዕውቀት የላቸውም። የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ለበጎም ይሁን ለክፋት ውሳኔያቸውን ከመነሻ ምክንያቱ እስከ መጨረሻ ውጤቱ ጠንቅቀው ማወቅና መገመት ይችላሉ። ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ግን እንኳን የውሳኔያቸውን የመጨረሻ ውጤት ስለ መነሻ ምክንያቱ ራሱ በቅጡ ሳያውቁ የሚወስኑ ይመስለኛል።
በዘንድሮ አመት የጠ/ሚኒስትሩ የፖለቲካ አመራር ብቃት መሻሻል አልታየበትም። ለዚህ ደግሞ ባለፈው ወር ከአንድ የውጪ ዲፐሎማት ጋር ያደረኩትን ውይይት እንደ ምሳሌ መጥቀስ ይቻላል። የተጠቀሰው ዲፕሎማት እኔን ጨምሮ ከአምስት ጦማሪያንና ጋዜጠኞች ጋር ውይይት ካደረገ በኋላ መጨረሻ ላይ እንዲህ አለን፡- “እስኪ ሁላችንም አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ? ‘የኢትዮጲያ ፖለቲካዊ ሁኔታ በጣም አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ የኢህአዴግ መንግስት የህዝቡን ጥያቄ በአስቸኳይ ተቀበሎ ስር-ነቀል የሆነ ለውጥ ካላደረገ ሁኔታው በጣም አሳሳቢ ነው!’ ብዬ በግልፅ ለመናገር ብፈልግ ማንን ነው የማናግረው? …በእርግጥ እናንተ ስለ ፖለቲካው፣ ኢኮኖሚው፣ የፍትህ ስርዓቱ፣… ወዘተ የምታነሷቸውን ችግሮች በግልፅ እረዳለሁ። ነገር ግን፣ ስለ እነዚህ ችግሮች ከማን ጋር ልነጋገር? …አንዳንዴ ‘መለስ ዜናዊ ቢኖር ኖሮ ብዬ እመኛለሁ” አለን። “ስለ ሀገሪቱ ፖለቲካዊ ሁኔታ አሳሳቢነት ከማን ጋር ልነጋገር?” በሚል ላቀረበልን ጥያቄ ከመካከላችን አንዱ “የጦር ኃይሎች አዛዥን ማነጋገር አለብህ። በተግባር ሀገሪቱን እያስተዳደረ ያለው እሱ” አለ። ሌላኛው ደግሞ “የደህንነት ሃላፊው ማናገር ሳይሻል አይቀርም” አለ፡፡ ሌሎቹም እንዲሁ ‘ከኋላ ወይም ከፊት ሆነው የሀገሪቱን ፖለቲካ እያሽከረከሩ ነው’ ያሏቸው ባለስልጣናትን ጠቆሙ፡፡
የእኔ ምላሽ ግን በሁሉም ዘንድ ያልተጠበቀ ነበር። “ስለ ሀገሪቱ ፖለቲካዊ ሁኔታ አሳሳቢነት ከማን ጋር ልነጋገር?” ለሚለው ጥያቄ ምለሼ “ጠ/ሚ ሃይለማሪያም ደሳለኝ አናግረው” የሚል ነበር። በእርግጥ የተናገርኩት ነገር ለሁሉም አልተዋጠላቸውም! ነገር ግን፣ እንደ እኔ አመለካከት ዲፐሎማቱ ያነሳው ክፍተት የተፈጠረው በዋናነት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም እንደ ሀገር መሪ ሚናቸውን በአግባቡ መወጣት ስለተሳናቸው ነው። ሀገሪቷ እንዲህ መሪ አልባ የሆነችው እሳቸው እንደ ጠ/ሚኒስትር የተሰጣቸውን ስልጣንና ኃላፊነት በተገቢ ሆኔታ ተግባራዊ ስላላደረጉ ነው።
ባለፈው ፅሁፍ በዝርዝር ለማስረዳት እንደሞከርኩት፣ እንደ ኢትዮጲያ ባሉ ደሃና የዳበረ ፖለቲካዊ ሥርዓት በሌላቸው ሀገራት የፖለቲካ መሪዎች ውሳኔና አመራር በሀገሪቱ የወደፊት ዕጣ-ፋንታ እና በሕዝቡ ሕይወት ላይ የሚፈጥረው ተፅዕኖ በጣም ከፍተኛ እንደሆነ ተመልክተናል። ምክንያቱም፣ እንደ ኢትዮጲያ ባሉ ሀገራት የፖለቲካ መሪዎች ብቃት ሰላም፥ ልማትና ዴሞክራሲን ከማስቀጠል እና መቀልበስ ጋር በቀጥታ የተያያዘ ነው። በዚህ ፅሁፍ በዝርዝር ለማስረዳት እንደተሞከረው፣ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የሀገሪቷን ሰላም፣ ልማትና ዴሞክራሲ በዘላቂነት ለማስቀጠል የሚያስችለል የፖለቲካ አመራር ብቃት የላቸውም። ስለዚህ፣ የእሳቸው ከሥልጣን መውረድ ለሀገር ትልቅ ውለታ ነው።
Filed in: Amharic