>

”እስረኛው” ተኝቷል (ጋዜጠኛ ወሰንሰገድ ገብረኪዳን)

የወህኒው ጠባቂ – የወህኒው በረኛ
ይብላኝልህ ላንተ – ተኝቷል እስረኛ!!

ከታጠቅከው ክላሽ – ከጥይት ያለፈ
እውነትን አስታቅፎህ – እጅግ የገዘፈ
በፍፀም ሠላም ውስጥ – ለ….ሽሽሽ ብሎለሃል
በእርካታ ተሞልቶ – እስረኛው ተኝቷል!!

ተኝቷል እስረኛው – ሃሳቡን አራግፎ
ባንተ ህሊና ውስጥ – ሐቅ እውነቱን ፅፎ፡፡

አወይ አለማወቅ …
ለአሳሪው ነው እንጂ – ሰቀቀኑ ጭንቁ
መቼ ታስሮ ያውራል – የእስረኛው ሐቂቁ፡፡

አንዳንደዜ ሰዎች – ሐቅን ይስታሉ
እውነትን ሳይለዩ – ታሰረ ይላሉ!!
ሰዎች ምን ነካቸው – ታሠረ የሚሉ – ቃል የሚያቃልሉ
እንዴት ይታሰራል – እውነት ያለ ውሉ!?
ማነው የታሰረው – ማነው እስቲ ነፃ
ቀኑን የሚያቃዠው – ሌት የሚያባትተው – የእውነት ፍላፃ
አሳሪውን እንጂ – የሚስበረግገው
ሰላም ነው ህሊናው – ታሳሪ ሚባለው!
ደግሞስ በምን ተዓምር – ማቆምስ ይቻላል
እውነት እንዴት ሆኖ – በምን ይታሰራል!?

Filed in: Amharic