>

የመገንጠል ጥያቄ ‹...እኛ ኬንያዊነት አይሰማንም...› (ዮናስ ሃጎስ)

 
ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ትላንት በቀረበባቸው የምርጫ ማጭበርበር ክስ ምክንያት ለዛሬ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረው የቃለ መሐላ ስነ ሥርዓታቸው ወደ ኖቬምበር 28 ተዛውሯል። በነዚህ ቀናቶች ውስጥ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ወይ እንደ ነሐሴው ምርጫውን ውድቅ ያደርገው ይሆናል አሊያም ምርጫውን ያፀድቀው ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
***
ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ይህ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የጭንቀታቸው መጨረሻውን ቦታ እንደሚይዝ በማያጠራጥር ሁኔታ ከሱ በባሱ አስቸጋሪ ጉዳዮች ተወጥረው ተይዘዋል።

– የኬንያ ወደብ ሞምባሳንና ሌሎቹንም አጠቃልሎ የያዘው የጠረፍ ግዛት ‹እኛ ኬንያዊነት አይሰማንም…› ብለው የመገንጠል ጥያቄያቸውን ከውይይት ወደ ሰነድ አውርደውታል። በሰነድፍ የተቀመጠውን ፅንሰ ሐሳብ የጠረፍ ነዋሪዎች እንዲወያዩበት ከተደረገ በኋላ የአብዛኛውን  ድጋፍ ካገኘ በቀጥታ ወደ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ቀርቦ ሪፈረንደም እንዲካሄድበት ይደረጋል። ኡሁሩ ኬንያታ በፕሬዝዳንትነታቸው ከፀኑ የሪፈረንደሙ ውጤት ምን እንደሚሆን ምንም የሚያጠራጥር ነገር አይኖረውም።
*
– በተቃዋሚዎች የተመራው የአንዳንድ ከመንግስት ጋር ግንኙነት ያላቸው ድርጅቶች ላይ እየተካሄደ ያለው ቦይኮት ዱላውን በድርጅቶቹ ላይ እያጠነከረ መጥቷል። የቦይኮቶቹ ሁሉ ተቀዳሚ ኢላማ የሆነው የኬንያ ተቀዳሚ ቴሌኮም ሳፋሪኮም በ10 ቀናት ውስጥ ብቻ 800 ሚልዮን ሺልንግስ (200 ሚልዮን ብር ኪሳራ) ደርሶበታል። ከሳፋሪኮም ምርቶችን ተረክበው የሚሸጡና የሚያከፋፍሉ ወኪሎች ማሕበር በቴሌቭዥን ቀርቦ ተቃዋሚዎችን እስከመለመን ደርሰዋል። ቦይኮቱ በዚህ ከቀጠለ ሳፋሪኮም በሚቀጥሉት ጥቂት ወራቶች ብቻ ከ1 ሚልዮን በላይ ሰራተኞቹን ለማሰናበት ይገደዳል።
*
– በተቃዋሚዎች ክልል የሚገኝ አንድ ካውንቲ ምክር ቤቱን ዛሬ ሰብስቦ የኡሁሩ ኬንያታን ፕሬዝዳንትነት ሙሉ በሙሉ እንደማይቀበለው በሙሉ ድምፅ ያፀደቀ ሲሆን በሌሎችም ተቃዋሚዎች በሚበዙባቸው ካውንቲዎች የሕዝብ ተመራጭ ምክር ቤቶች ከነገ ጀምሮ ተከታታይ ስብሰባዎች እንደሚካሄዱ ለማወቅ ተችሏል።
*
የተቃዋሚዎች መሪ ራይላ ኦዲንጋ ከአሜሪካ ኮንግረስ ተወካዮች ጋር ስብሰባ ለማድረግ ትላንት አመሻሽ ላይ ወደ አሜሪካ ያቀኑ ሲሆን በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ይመለሳሉ ተብሎ ይገመታል። ራይላ ዛሬ ከሮይተርስ ዜና ወኪል ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ከገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎች የተውጣጣ የሽግግር ጊዜ መንግስት ተቋቁሞ መስተካከል ያለባቸው ሕገ መንግስታዊ ችግሮችን ነቅሶ ካወጣ በኋላ ከስድስት ወር በኋላ አዲስ ሐገራዊ ምርጫ መካሄድ እንዳለበት አሳውቀዋል።
*
የኬንያ ፓርላማ የዓመቱን የስራ ዘመን ከጀመረ አንድ ሳምንት ሳይሞላው እንደገና ለእረፍት ተበትኗል። ፓርላማው በተቃዋሚዎች በቀረበው ጥያቄ መሰረት የፕሬዝዳንታዊው ምርጫ ጉዳይ በኖቬምበር 28 እልባት እስኪያገኝ ድረስ ምንም ዓይነት ውሳኔዎችን ማስተላለፍ እንደማይችል በመግለፅ እስከዛው ድረስ እረፍት ወጥቷል።
Filed in: Amharic