>

ጭቆናን በጭካኔ ማሸነፍ አይቻልም!

ስዩም ተሾመ

እኔ፣ ይህን ስርዓት የምነቅፈው፣ ሥራና አሰራሩን ዘወትር የምተቸው፣… ጠዋት ማታ የምፅፈው፣ የምናገረው፣ የማስበው፣ የዜጎች መብትና ነፃነት እንዲከበር ነው! “የአንድ ወገን የበላይነትና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የብዙሃኑ መብትና ነፃነት መጣስ የለበትም” ብዬ ስለማምን ነው። ይህ የአንዱ ብሔር ደጋፊ፣ የሌላው ብሔር ተቃዋሚ በመሆን ሳይሆን፣ “ሁሉም ሰው እንደ ሰው እኩል መብት፥ ነፃነትና ተጠቃሚነት ይገባዋል” የሚል ፅኑ እምነት ስላለኝ ነው። ነጋ ጠባ “የኦሮሞ ሕዝብ መብት ይከበር!” እያልኩ የምጮኸው የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን እንጂ ሰሞኑን በኢሊባቡርና በመቱ፣ ዛሬ ደግሞ በነቀምት እንደሆነው፣ በተለይ የአማራና የትግራይ ተወላጆች መንገድ ላይ ተደፍተው እንዲቀሩ አይደለም።

የኦሮሚያ #አድማ_በተኝና የአከባቢው ፖሊሶች፣ የንፁሃን ዜጎች ሕይወትና ንብረት ሲጠፋ በቅርብ ርቀት ቆመው ሲመለከቱ ማየትን የመሰለ አሳፋሪ ነገር የለም። ይሄ የመጨረሻ ስሜት አልባነት ነው! የሞራል ዝቅጠት ነው! ለኦሮሞ ሕዝብ ሆነ ለክልሉ መንግስት ታላቅ ውርደት ነው! የኦሮሞ ሕዝብ መብትና ነፃነት የሚከበረው በፖለቲካዊ ስልትና የሞራል የበላይነት እንጂ በጭቃኔና ስርዓት-አልበኝነት አይደለም። ጭቆናን በጭካኔ ማሸነፍ አይቻልም።

Filed in: Amharic