>

"በጥልቅ ሀዘን ውስጥ ላለ ሰው ትንቢት አትናገር !" (ዳንኤል ሺበሺ)

ዛሬ ጥቅምት 16 ቀን፡ 2010 ዓም ጠቅላይ ሚኒስትራቸው የፕ/ት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ለሕ/ተ/ም ያደረጉትን መክፈቻ ንግግር ተከትለው የሰጡትን ማብራሪያ (brief) አዳመጥኩኝ ፡፡ አንድ ሪፖርት የሚቀዳው ከዕቅድ እስከ ድርጊት ካለው ክፍል ውስጥ መሆኑ ግልጽ ነው ፡፡ ካልዋሸን ወይም ካልተሳሳትን በስተቀር ሪፖርት እውነት መሆን አለበት ፡፡ ከዚህ ሀሳብ ስንነሳ አንገት ስላስደፋን የመንግሥታቸው ሪፖርት ለፓርቲያቸው አባላት (ለፓርላማው) አቅርበውታል ፡፡ የማብራሪያቸው ይዘት ለኔ በብዙ ውሸቶችና በጥቂት አጃቢ እውነታዎች የታጨቀ ነበር ፡፡
እጅግ የመሰጠኝ ግን በፖሊስ አባላት ላይ የሰነዘሩት አስተያየት ነው፡፡ በተለይ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል ስለተፈጠረው ቀውስ በተመለከተ በቀውሱ ውስጥ የተሳተፉ የፖሊስ ሠራዊት የአመለካከት ችግር እና ኪራይ ሰብሳቢ ጥገኞች ናቸው በማለት ነበር የገለጹት ፡፡ እኛ ባለን መረጃ ግን የፖሊስ አባላት አፈሙዙን ወደ መንግሥትና መንግሥት ፖለቲካል አቅጣጫ ላይ ማዞራቸውን እንጂ አንዱ ሌላውን ሕዝብ ለማጥቃት አይመስለኝም ፡፡ ክቡርነታቸው (አጎቴ lol) እንዳሉትም ከሆነም ማለቴ ነው፡፡

“ልጅን ለማረም አስቸጋሪ የሚሆነው ችግሩ ከወላጆቻኀው ጋር ሲኖር ነው” እንደሚባለው ሁሉ የፖሊሶቹ ችግር ነው የተባለው ችግርም የሚቀዳው ከተቀረጹበት ከአብዮታዊ ዴሞክራሲ አለመለካከታቸው መሆኑ ግልጽ ነው ፡፡ በሊብራል አስተሳሰብ ቢቀረጹ ኖሮ ሊብራልና ዴሞክራቲክ ይሆኑ ነበር እንደ ማለት ፡፡ እንደሚታወቀው ፖሊሶቹ (ልዩ ኃይል) ዕድሜ ክልላቸውን ብናይ እንኳ የሩብ ምዕተ ዓመታት ውጤቶች ናቸው፡፡ በኢሠፓ ወይም በኢህአፓ ማላከክ የሚቻል አይመስለኝም፡፡ ፖሊሶቹ ኪራይ ሰብሳቢ፤ ፀረ ዴሞክራቲክ ወዘተ ከሆኑ ተጠያቂው አሳዳጊዉም ጭምር እንጂ ታዳጊዉ ብቻ አለመሆኑ ሊሰመር ይገባል ፡፡ አሳዳጊው የትግራይ ነፃ አውጪ እና የእጁ ሥራው #አዴ ናቸው ፡፡ የአንድ ወንዝ ምንጩ በየጊዜው ድፍርስ ከሆነ ወራጁ ውሃው እንደት ሊጤራ ይችላል ? ውሃው እንዲጠራ ከተፈለገ የግልና የጋራ ጥረት ያስፈልገዋል ፡፡ በሁሉም በኩል ጥረቱም ትግሉም አሁን የተጀመረ ይመስለኛል ፡፡

ፖሊሶቻችን የኛ ናቸው ፡፡ እንደ ማንኛው ሰው ሁሉ ዕኩልነትንና ፍትሐዊነትን ይፈልጋሉ ፡፡ እንደ ዜጋ ፍትህንና ዘላቂ ተጠቃሚነትን ይናፍቃቸዋል ፡፡ ጥሩ ኑሮ መኖር ይፈልጋሉ ብቻም ሳይሆን ያስፈልጋቸዋልም፡፤ በሰው’ ታቸውም በማዕረጋቸውም መከበርን ይፈልጋሉ ፡፡ ያሠማራቸው ሥርዓቱ ከሕዝብ ጋር ባጣላቸው ቁጥር እንደተጣሉ መኖር አይፈልጉም ፡፡ ማንም ተራ ዜጋ እንደሚረዳው በሀገራችን ለተራ እግረኛ ወታደር ይቅርና ለትላልቆቹ ለባለ መሥመር መኮንኖችም ካለው ክብር ይልቅ ለአንድ ቻይናዊ ጉልበት ሠራተኛ ያለው ክብር ይልቃል ፡፡ ለአንድ ኢንስፔክተር፣ ሱፐርኢንተዳንት፣ ኮሎኔልና ወዘተ ከሚሰጠው ሥፍራ ይልቅ ለተራ ጆሮ-ጠቢ ያለው ታአማኝነት ጎልቶ ይታያል … ፡፡ በኀወሓት ዕዝ ሰንሰለት ሥር ተጠርንፈው የሚተነፍሱበትን አጥተው መኖራቸውን ለማንም ግልጽ ነው ፡፡ ነጋ ጠባ ግምገማ ተብየ አውጫጭን ያረሩ ፖሊስ አባላት’ኮ ሁሌም አንገት ደፍተው ይኖራሉ ማለት ለኔ ይከብደኛል ፡፡ ሰዎች ናቸውና አንድ ቀን <… ግን ለምን?…> ብለው መጠየቃቸው አይቀረ ነው ፡፡

በላይ ላያቸው የተቆለሉትና በድሃው ገበሬ ልጅ ደምና በመሬታቸው ቱጃር የሆኑ ዛሬ ላይ የጨዋታ ህጋቸውን ወደ #ቢሊዮኖች ቤት ከፍ ሲያደርጉ (የሠራዊቱን አዛዦችንም ይጨምራል) እነዚህ ሚስክኖቹ ደሞ የታክሲ ሣንትም ጭምር አጥተውና ተርበው በየመንደሩ ሲያዛጉ እንደት ስለሰላም ሊያወሩ ይቻላል? ግዙፉ ሕገመንግሥት ይቅርና የቅርቡን የአለቃ ትዕዛዝ እንደት ብለው ያከብራሉ?፤ ጠ/ሚሩ እንዳሉት ከሆነም ማለቴ ነው ፡፡ በከባድ ሀዘን ውስጥ ላሌ ሰው ትንቢት አትናገር ይባል የለ!? በከባድ አስተዳደራዊ ጭቆና ውስጥ ያለ ሰራዊት፤ የቤት መክፈያ አጥቶ በየካምፑ የሚከራተት ነው ፡፡ የልፋታቸውን ዋጋ በአንፃራዊነት እንኳ መቅመስ ያልቻለ ሠራዊት ፤ ስለ ሰብዓዊነት እየተሰበከላቸው ግን ሰብዓዊ ክብራቸውን ለተነፈጉ ሠራዊት፤ በቅድሚያ ሕገ መንግሥቱን ለመጠበቅም በሕገ መንግሥቱ የተደነገጉ መብቶቻቸው መጠበቅ ይገባል ባይ ነኝ ፡፡ እንዲያውም የሀገራችን ፖሊሶች በባሕልና በሃይማኖት ተፅዕኖ ውስጥ ያደጉና የኖሩ መሆኑ በጀን እንጂ፤ በሥርዓቱ ከሚደርሰባቸው በደል ልክ ቢሆን ኖሮ ምን ሊመፈጠር እንደምችል መገመት አያቅትም ፡፡

በደርግ ጊዜ ከነበረው ከኢት/ያ ሠራዊትም እንዳየነው ከሆነ፤ ቢቸገር ቢቸገር እንኳ መሣሪያ ቢሸጥ ወይም ቢለምን እንጂ መሣሪያውንና ሙያውን ተጠቅመው በእኩይ ተግባር ላይ የማይሳተፍ ነው ፡፡ ይህ ከኢት/ዊ ጨዋነት፣ ከአስተዳደጋቸውና ከግላዊ ባሕርያቸው የሚመነጭ እንጂ ከሙሰኛው፤ ከጨቋኙ፤ ከዘረኛው እና እንዲተኩሱት ከሚያዘው ኃይል አስተሳሰብ የሚመነጭ አይደለም ፡፡ በርግጥ ከሠራዊቱ በኩል ወደ ሕዝቡ ይተኮስ የነበረው ጥይት ለምንና እንደት እንደሆነም አይጠፋብንም ፡፡ ከዚህ በኀላ ግን ሕዝቡም የሠራዊቱ፤ ሠራዊቱም የሕዝቡ ነው !!
በ2005 ዓም በአንዱ ጹሁፌ ላይ ርዕስም ትኩረትም ያደረኩት <ለፖሊስና ለመከላከያ ሠራዊቱ ማን አለላቸው?> የሚል ነበር ፡፡

የጠ/ሚ ኃ/ማርም ንግግር የሀገራችንን ነባራዊና ወቅታውዊ ሐቁን ያላገናዘበ፤ እውነታውን በደንብ ያልዳሰሰ ነበር ፡፡ ሰላም !!

Filed in: Amharic