>
5:13 pm - Wednesday April 19, 3093

''ኢ-ፍትሃዊው እስሬ! ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ መብታችን ትልቅ አደጋ ላይ ነው፡፡ እየፈሩ ጋዜጠኝነት የለም'' የዕንቁ መጽሔት ዋና ኣዘጋጅ ኤልያስ ገብሩ

አርብ ግንቦት 15 ቀን 2006 ዓ.ም ከወዳጄ ጋዜጠኛ ዳዊት ሠለሞን ጋር ቀጠሮ ነበረኝ፡፡ ረፋድ 5፡25 ሰዓት ላይ የሞባይል ስልኬ ጠራች፡፡ ከአምባሳደር ወደአራት ኪሎ በሚጓዝ ታክሲ ውስጥ ተሳፍሬ ነበር፡፡ የመስመር (የቢሮ) ስልክ መሆኑን አየሁትና “ሃሎ” አልኩኝ፡፡ ‹‹አቶ ኤልያስ፣ የዕንቁ መጽሔት ዋና አዘጋጅ?›› የሚል የሴት ድምጽ ተሰማኝ፡፡ ‹‹አዎን›› ስል መለስኩላት፡፡ ብዙ ጊዜ አንባቢዎች ስለሚደውሉ፣ ምን ዓይነት ግብረ-መልስ (feed back) ይኖራት ይሆን ነበር ሀሳቤ፡፡ ሳይሆን ቀረ፡፡ ‹‹የምደውለው ከፌዴራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ነው፣ በአንድ ጉዳይ ላይ ስለምንፈልግዎት ቃልዎትን መጥተው እንዲሰጡን ነበር፡፡›› …‹‹እሺ፣ ሰኞ ጥዋት ልምጣ?›› በማለት ጠየኳት፡፡ ‹‹ቆይ አንዴ?›› ብላኝ ባልደረቦቿን ካነጋገረች በኋላ ‹‹ይቻላል›› አለችኝ፡፡ ቀጭን የጌታ ትዕዛዝ፡፡ ከዚህ የስልክ ጥሪ በኋላ የመጽሔቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ፍቃዱ ማኅተመወርቅ (ፍቄ) ደውሎልኝ ስለጉዳዩ ሐሳብ ተለዋወጥን፡፡ ሰኞ በጥዋት ለመገናኘት ተቀጣጥረን ስልኩ ተዘጋ፡፡
ለምርመራ መጠራቴ በኢትዮጵያ የነጻ ፕሬስ ሕይወት ውስጥ የሚያጋጥም፣ የተለመደ ጉዳይ በመሆኑ ብዙ አልገረምኩኝም፡፡ በቀድሞ አውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ላይ እሰራ በነበረበት ወቅት አሸባሪ ተብሎ በፓርላማ በተሰየመው የ‹‹ግንቦት 7›› የፖለቲካ ድርጅት አመራሮች እና በአገር ውስጥ በነበሩ ከፍተኛ ጄኖራሎች፣ የመከላካለያ ሰራዊት አባላትና ሌሎች ዜጎች ላይ ከባድ ክስ ቀርቦ ነበር፡፡ የፍርድ ሂደቱን ተከታትዬ የምዘግበው እኔ ነበረኩ፡፡ እኔ ከሰራሁት ዘገባ ጋር በተያያዘ አቃቤ ሕግ ክስ አቅርቦ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ከባልደረባዬ ጋዜጠኛ ፍጹም ማሞ (ዋና አዘጋጅ የነበረ) ተጠርተን ቃል በመስጠት በ5000 ሺህ ብር ከወጣን በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበን ነበር፡፡ ፍ/ቤቱም ክሱን ተመልክቶ ለእኔ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ የሰጠኝ አጋጣሚ ስለነበረ ጉዳዩን አስታውሼ በአዕምሮዬ ለአፍታም ቢሆን ማሰላሰሌ አልቀረም ነበር፡፡
ሰኞ ግንቦት18 ቀን 2006 ዓ.ም ጥዋት ከባልደረባዬ ፍቃዱ ጋር ቀጠሮ ስለነበረን ወደ ቢሮ አመራሁ፡፡ በአጋጣሚ ፍቃዱ ያለወትሮው ቢሮ አልነበረም፡፡ ስልኩ ይጠራል፣ ግን አይነሳም፡፡ ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ገደማ ፍቃዱ ደወለልኝ፡፡ ሞባይል ስልኩን ያላነሳው ጓደኛው ቤት ረስቶት በመውጣቱ ምክንያት መሆኑን ነገረኝ፡፡ ከሰዓት የተጠራሁበት ቦታ ለመሄድ በድጋሚ ተቀጣጠርን፡፡ ከሰዓት በኋላ ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ እና ነብዩ ሐይሉ ተቀላቅለውን አራት ሆነን ወደማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ሄድን፡፡
ምርመራ ቢሮ ቁጥር – 76
እኔ እና ፍቃዱ ተፈትሸን እና ሞባይላችንን ጥበቃ ጋር አድርገን ወደቢሮ ቁጥር 76 አቀናን፡፡ እኔ አንኳኩቼ ወደ ቢሮዋ ገባሁ፡፡ ፍቃዱ ውጭ ቁጭ አለ፡፡ አንድ ወንድ እና ሴት የመ/ቤቱ ባልደረቦች ቢሮ ውስጥ ነበሩ፡፡ ከየት እንደመጣሁ ነገርኳቸው፡፡ ‹‹ቁጭ በል›› ተባልኩ፡፡ ‹‹ጥዋት ነበር እመጣለሁ እኮ ያልከው?›› ብሎ ወንዱ ፖሊስ ሀሳቡን ሰነዘረ፡፡ ‹‹አዎን›› ካልኩት በኋላ ጠዋት ያልመጣሁት በሁኔታዎች አለመመቻቸት መሆኑን አስረዳሁት፡፡ በምን ጉዳይ ልጠራ እንደቻልኩ መረጃው ካለኝ እንድነግረው ፈገግ እያለ ወዲያው እኔኑ ጠየቀኝ፡፡ መረጃው እንደሌለኝ ነገርኩት፡፡ አንድ የክስ መዝገብ ሲገልጥ የመጽሔታችንን ቁጥር 113ኛ ዕትም አየኋት፡፡ በመጽሔቱ ፊት ገጽ ላይ ‹‹በቃን! የጠባብ ብሔርተኝነት ዘመቻ›› በሚል ትልቅ ርዕስ ሥር የቀድሞ ጠ/ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊ፣ የቀድሞ ም/ ጠ/ሚንስትር አቶ ታምራት ላይኔ፣ የኤርትራ ፕሬዚዳንት አቶ ኢሳያስ አፈወርቂ፣ የኦነግ መስራች አቶ ሌንጮ ለታ፣ የቀድሞ ም/ ጠ/ሚንስትር እና የብአዴን ሊቀመንበር አቶ አዲሱ ለገሰ፣ የቀድሞ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር እና የብአዴን ሊቀመንበር አቶ ተፈራ ዋልዋና የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ምክትል ፕሬዚዳንት የሆኑት አቶ አለምነው መኮንን ፎቶግራፎች አለ፡፡ ይህ ጽሁፍ መጽሔቷ ዝግጅት ክፍል የተሰራ እና ከወራቶች በፊት አቶ አለምነው መኮንን የአማራን ሕዝብ ጸያፍ ስድቦች መሳደባቸውን ተከትሎ መሰል ድርጊቶች ሥርዓቱ ሥልጣን ከያዘ ጀምሮ በተለያዩ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት፣ በኤርትራው ፕሬዚዳንት እና በቀድሞ የኦነግ መስራች መደረጋቸውን በማስታወስ ጠባብ ብሄርተኝነትን የሚቃወም እና ለችግሩ መፍትሄ ጠቋሚ ጽሁፍ ነበር፡፡
በዚያን ዕለት ለፖሊስ ቃሌን እንድሰጥ የተጠራሁትም በዚሁ ጽሑፍ መስሎኝ ነበር፡፡ መርማሪ መሆን አለመሆኑን ያላረጋገጥኩት እያነጋገረኝ ያለው ወጣት ግን የተጠራሁት በቅርቡ በኦሮሚያ ክልሎች በተነሳው ግጭት እና ብጥብጥ ጋር በመሆኑ ላይ ጥቁምታ ሰጠኝ፡፡ በአጋጣሚ በእጅ ላይ ሁለት የዕንቁ መጽሔት ዕትሞችን ይዜ ገብቼ ነበር፡፡ ወጣቱ ልጅ ‹‹አንዴ ልመልከታቸው?›› ብሎኝ ግንቦት 20 በተመለከተ ባለፈው ቅዳሜ የወጣውን የመጽሔቱን ዕትም ሰጥቼው እያገላበጠ ተመለከታቸው፡፡ ከሌላ ክፍል የመጣ አንድ መርማሪም ክስ ያቀረበብኝን ዕትም ከፋይሉ ውስጥ ነጥሎ በመውሰድ የሆነ ጽሑፍን በተመስጦ አንብቦ ክፍሉን ለቅቆ ወጣ፡፡
ወጣቱ ልጅ፣ ‹‹ያው ጥዋት እመጣለሁ ብለህ እኛም ስንጠብቅህ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ እኛ በተራችን እናስጠብቅሃለን፡፡›› አለኝ – ፈገግ እያለ፡፡ ፈገግታው ከልብ የመነጨ ነው ለማለት ግን እቸገራለሁ፡፡
ከሰላሳ ደቂቃ በኋላ አንዲት ወፈር ያለች፣ የፖሊስ ማዕረግ ያለው የደንብ ልብስ የለበሰች ሴት ወደ ወዳለሁበት ክፍል መጣች፡፡ ‹‹ኤልያስ አንተ ነህ?›› አለችኝ፡፡
‹‹አዎን›› አልኳት፡፡
‹‹መጣሁ›› ብላኝ ከአፍታ ቆይታ በኋላ ተመልሳ በመምጣት እኔ የተቀመጥኩበት ወንበር ጋር ባለው ሰፋ ያለ ጠረጴዛ ትይዩ ተቀመጠች፡፡
‹‹ጥዋት ለምን አልመጣህም?›› የመጀመሪያ ጥያቄዋ ነበር፡፡
በአጋጣሚ በተፈጠረ ጉዳይ መምጣት አለመቻሌን አስረዳኋት፡፡ በዚህ ጊዜ ወጣቱ ልጅ አድራሻዬን፣ ዜግነቴን፣ የትውልድ ቦታዬን፣ የተማርኩባቸውን ትምህርት ቤቶች እና የከፍተኛ ትምህርት ተቋም፣ የሰራሁባቸውን የሚዲያ ድርጅቶች፣ የትዳር ሁኔታ …እየጠየቀኝ ፎርም ላይ እየሞላ ነበር፡፡
‹‹ብሔርህስ?›› አለኝ፡፡ ‹‹ኢትዮጵያዊ›› አልኩት፡፡
‹‹ያ’ማ ዜግነት ነው፣ መናገር አለብህ›› አለኝ፡፡ በግሌ የማልወደው ጥያቄ መሆኑን ነገርኩት፡፡ [የሰው ልጆች በሙሉ ምንጫችን አንድ ነው ብዬ አጥብቄ ስለማምን የዘር ጥያቄ ከልጅነቴ ጀምሮ የማይመቸኝ እና የማላምንበት የግል ጉዳይ ነው] ስለብሄር ሊያስዳኝ ሞከረ፡፡ መታወቂያዬ ላይ የተጻፈውን ነገርኩት፡፡
ወ/ሮ በላይነሽ የተባለችው ምርማሪዬ ፋይሉን ተቀብላ እና በመጽሔቱ የተከሰስኩበትን ጉዳይ ነገረችኝ፡፡ በታሪክ አምድ ሥር ‹‹የተገነቡት እና በመገንባት ላይ ያሉት የመታሰቢያ ሐውልቶች የእነማን እና ለእነማንስ ናቸው?›› በሚል ርዕስ ሰዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን የተባለው ጸሐፊ በጻፈው ጽሑፍ ውስጥ የኦሮሞን ብሔር የሚያጥላላ፣ ዘርን ከዘር የሚያጋጭ፣ የኦሮሞ ሕዝብ ከ16ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ የመጣ መሆኑን የሚጠቅስ፣ ለኢትዮጵያ እንግዳ ሕዝብ መሆኑን የሚናገር …ወዘተ በጣም ጥሩ ያልሆነ ጽሑፍ መሆኑን ነገረችኝ፡፡ አያይዛም ይህን ጽሑፍ ተከትሎ በጅማ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ላይ ቁጣ መቃስቀሱን፣ ተማሪዎች ጽሑፉን የጻፈው ግለሰብ ለሕግ እንዲቀርብ ሁለት ጊዜ ያህል ለዩኒቨርሲቲው የሚመለከተው አካል በደብዳቤ ቢያሳውቁም መልስ ሳይሰጣቸው በመቅረቱ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣታቸውን፣ መስታወቶች መሰባበራቸውን፣ ንብረቶች መውደማቸው፣ በሰዎች ላይ የአካል ጉዳት መድረሱን፣ ሆስፒታል ገብተው በሞት እና በሕይወት መካከል ያሉ ተማሪዎች መኖራቸውን፣ የመማር ማስተማር ሒደት መስተጓጎሉን …ወዘተ ዘርዝራ አስረዳችኝ፡፡
እኔም እኛ (የመጽሔቱ አዘጋጆች እና ባልደረቦች) ኢትዮጵያን አንድ የሚያደርግ እንጂ ዘርን ከዘር የሚከፋፍል ሥራ አለለመስራታችንን፣ በሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 29 መሰረት ሕግን በማክበር ጽሑፎችን መጻፋችንን እና የተለያዩ ግለሰቦችን ሐሳቦች ማስተናገዳችንን፣ ይህንንም መመልከት እንደሚቻል ከጠቀስኩላት በኋላ የተባለው ጽሑፍ የመጽሔቱ ሳይሆን የግለሰቡ የግል ግለ-ሀሳብ መሆኑን አሰረግጬ ነግሬያት ነበር፡፡
መርማሪዬም ‹‹ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በሕገ-መንግሥቱ ተደንግጓል ብላችሁ የመጣላችሁን ጽሑፍ በሙሉ ታትማላችሁ ማለት ነው?›› በማለት ቆጣ በማለት ለመናገር ሞከረች፡፡ የመጡልን ጽሑፎች ሁሉ እንደማይታተሙ፣ እንደዋና አዘጋጅነቴ መስተካከል ወይም መታረም ያለባቸውን ጽሑፎች በአግባቡ እንደምመለከት፣ ሌሎች የመጽሔቱ አዘጋቾችም መሰል ሥራዎችን ተጋግዘን እንደምንሰራ ረጋ ብዬ አስረዳኋት፡፡
በክፍሉ ውስጥ ያሉት ሶስቱም የፌዴራል ፖሊስ ባልደረቦች በጽሑፉ ምክንያት የጠፋ ንብረት እና የአካል ጉዳት መኖሩን አጽንኦት በመስጠት ‹‹አጥፍታችኋል›› በሚል ተቆጥተው ሊናገሩኝ ሞከሩ፡፡ የእኔም ስሜት በተወሰነ ደረጃ መቀየር ጀመረ፡፡ እመን አትመን ክርክር ውስጥ ለአፍታም ቢሆን ገባን፡፡ ‹‹እነዚህ ሰዎች የፍርድ ቤትንም ሥራ ደርበው ይሰራሉ ወይ?›› ስል ታዘብኩ፡፡
ንግግሬን ቀጥያለሁ፡፡ በቅድሚያ በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ተፈጠረ ለተባለው ነገር መጽሔታችን መነሻ መሆኑን ለመቀበል እንደምቸገር፣ መጋቢት ወር ላይ የወጣ ጽሁፍ አደረሰ የተባለውን ችግር ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት እዚህ ምርመራ ክፍል ውስጥ መሆኑን፣ በጽሑፉ የተቆጡ ተማሪዎች ቅሬታቸውን ለዝግጅት ክፍላችን አለመግለጻቸውን፣ ተማሪዎቹ ያቀረቡትን ቅሬታ ዩኒቨርስቲው መደበኛ በመሆነ መልኩ ለመጽሔታችን ዝግጅት ክፍል ምንም ነገር አለማቅረቡን፣ ቅሬታ ቀርቦ ቢሆን ኖሮ ተፈጠረ የተባለውን ችግር ለመፍታት እኛም የራሳችንን ሥራ መስራት እንችል እንደነበረ፣ ማስተባበያ ጽሁፍ ወይም ጽሑፉን የሚተች ሌላ ጽሑፍ ቢመጣ ኖሮ በተመሳሳይ ገጽ እና ይዘት እንደምናስተናግድ፣ ለዚህም ኃላፊነት እና ግዴታ እንዳለብን ተናገርኩ፡፡
በዚህም ብቻ አቆምኩም፣ በዚሁ መጽሔት ላይ የፖለቲካ አቀንቃኑ እና የኦሮሞ ጉዳዮች ዋነኛ ተማጋች መሆኑ የሚታወቀው ጃዋር መሐመድ የኦሮሞን ሕዝብ ጥያቄዎች ከነመፍትሄዎቹ በተመለከተ የሰጠንን ሰፊ ቃለ ምልልስ ማስተናገዳችንን፣ አቶ ኦባማ አንሰርሙ የተባሉ ጸሐፊም ስለኦሮሞ ሕዝብ ታሪክ ሰፊ ጽሁፍ አቅርበው በመጽሔታችን ላይ ማስተናገዳችንን ዋቢ በማድረግ አስረዳኋቸው፡፡ እኔም ብሆን በግሌ የትኛውም ዘር ከየትኛውም ዘር እንደማይበልጥ እና እንደማያንስ፣ የኦሮሞ ሕዝብ ረዥም ታሪክ ያለው ትልቅ ህዝብ መሆኑንና ከገዳ ሥርዓትም ዓለም ዴሞክራሲን እንደተማረ የግል ዕምነት እንዳለኝ ሀሳቤን ሰነዘርኩ፡፡
በቢሮው ውስጥ የፖሊስ ልብስ ለብሳ ኮምፒውተር ላይ ጽሑፍ በመተየብ ላይ ያለች አንዷ የተቋሙ ባልደረባ ጽሑፉ ግጭት ማስነሳቱን እና ጉዳት ማድረሱን ደጋግማ በመናገር ጥፋተኛ መሆናችንን ለመናገር ጥረት አድርጋ ነበር፡፡
እዚህ ጋር ለፖሊሷ ምሳሌ አነሳሁላት፣ አቶ መለስ ዜናዊ ‹‹የኢትዮጵያ ታሪክ የ100 ዓመት ነው›› ብለው ተናግረዋል በሚል በአንድ ወቅት መስማቴን በመጥቀስ ይህ የግላቸው ዕምነት መሆኑን፣ እኔ ደግሞ ኢትዮጵያ ከ3000 ዓመታት በላይ ታሪክ እንዳላት እንደማምን እና የሳቸውን ሀሳብ መቃወም ካለብኝ መስታወት በመስበር እና ብጥብት በማስነሳት ሳይሆን በሀሳብ ሞግት ብቻ መሆን እንዳለበት አስረዳኋት፡፡ ምሳሌዬ ባይወጥላትም ዝም አለች – ሌላም ምሳሌ አንስቼላት ነበር፡፡ አቶ መለስ ‹‹የአክሱም ሐውልት ለወላይታው ምኑ ነው›› ብለው ነበር፡፡ ስላት፡፡ ‹‹አዎን፣ ምኑ ነው›› ብላ በፈጥነት መለሰችልኝ፡፡ ግን ትሰማኛለች እንጂ አታዳምጠኝም፡፡ ምናልባት እርሷንም ያስከስሳት ይሆን ማድመጧ!
…ሰዓቱ ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ሆነ፡፡ መርማሪዬ ወደቤቷ ለመሄድ የቸኮለች መሰለኝ፡፡ ቃሌን ለመስጠት በነጋታው ከእሷ ጋር ተቃጣጠርን፡፡ በዋስ መውጣት እንደማልችል አረዳችኝ፡፡ እኔም በክፍሉ ውስጥ ካደረግነው ንግግር እና ፊታቸውን በማንበብ ቀድሜ ተረድቼ ነበር፡፡ ባልደረባዬ ፍቃዱን አስጠራሁት፡፡ ዋስትና መከልከሌንም ነገርኩት፡፡ ለእናቴ ስለጉዳዩ ነግሮ እንዲያረጋጋት ስልኳን በወረቀት ላይ ጽፌ ሰጠሁት፡፡ የቤቴን ቁልፍ ለአናንያ ሶሪ እንዲሰጥልኝ ነግሬም ቻው ተባብለን ተሰናበትኩት፡፡ እንግዲህ እንዲህ ነው እስር፣ በስልክ ጠርቶ ቡና ከበጋበዝ ይቀላል – ለመንግሥታችን፡፡
…ይቀጥላል!
Like ·  · 
Filed in: Amharic