>
5:13 pm - Sunday April 20, 8955

ኢህአዴግ እና አልቃይዳ መካከል ያለው ልዩነት “በአጥፍቶ መጥፋት” እና “በአዋጅ ማሸበር” ነው! (ስዩም ተሾመ)

ባለፈው በአሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ ከተማ በሚገኘው ¨The Brookings Institution” በዴሞክራሲ ዙሪያ በተካሄደው ስብሰባ ላይ ተሳትፌ ነበር። በዚህ ስብሰባ ላይ ንግግር እንዲያደርጉ ከተጋበዙት እንግዶች ውስጥ የቀድሞ የአሜሪካ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር “Madeleine Albright” ይገኙበታል። በንግግራቸው ወቅት ሽብርተኝነት ለዴሞክራሲ አደጋ እንደሆነ አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል። በውይይት ወቅት ለቀድሞዋ የአሜሪካ የውጪ ሚኒስትር ጉዳይ አንድ ጥያቄ አንስቼላቸው ነበር። እንደ ኢትዮጲያ ባሉ ሀገራት ዜጎች እየተሸበሩ ያሉት በአሸባሪዎች ሳይሆን በፀረ-ሽብር ሕጉ እንደሆነ በመግለፅ በአሸባሪዎች (terrorists) እና በጨቋኞች (Tyrants) መካከል ያለውን ልዩነት እንዲነግሩኝ ጠይቄያቸው ነበር።

በአሜሪካ መንግስት ፊት አውራሪነት የተጀመረው አለም-አቀፉ የፀረ-ሽብርተኝነት ትግል እንደ አልቃይዳ ባሉ የሽብር ድርጅቶች በምዕራባዊያን ሰላምና ዴሞክራሲ ላይ የጋረጡትን አደጋ ለማስወገድ ዓላማ ያደረገ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን፣ የአሜሪካኖች የፀረ-ሽብር ዘመቻ በተለይ በመካከለኛው ምስራቅ እና ደቡብ ምስራቅ ኢሲያ ላይ አሰቃቂ ጦርነት እና ዕልቂት አስከትሏል። እንደ ኢትዮጲያ ባሉ ሀገራት ደግሞ የፀረ-ሽብር ዘመቻው በቀጥታ ፀረ-ዴሞክራሲ ሆኗል። በፀረ-ሽብር ትግሉ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ ነው።

የኢህአዴግ መንግስት የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁን በማውጣት በፀረ-ሽብር ስም ሕዝቡ በማሸበር ላይ ይገኛል። የፀረ-ሸብርነት አወጁ ከአሸባሪዎች ጋር ፍፁም ተመሳሳይ የሆነ ዓላማና ግብ አለው። ከአሸባሪዎች የበለጠ ዜጎችን በፍርሃትና ስጋት የሚያርድ ነው። ይህ ሕግ የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ከመሸራረፍና ከሕገ-መንግስቱ መርሆች ጋር ተፃራሪ ከመሆኑም በተጨማሪ መሰረታዊ ዓላማው ህዝቡን ከሽብር ጥቃት ለመከላከል ሳይሆን ንቁ የሆነ የፖለቲካ እንቅስቃሴና ተሳትፎ እንዳይኖር ማድረግ ነው። የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ ከወጣ በኋላ ባሉት ጥቂት አመታት የፖለቲካ ነፃነት የሚባል ነገር ተሟጥጦ ጠፍቷል

በኢትዮጲያ የፀረ-ሽብር ሕግ መሰረት ማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ “በአሸባሪነት” ሊያስከስስ ይችላል። ለምሳሌ፤ “‘የፀረ-ሽብር ሕጉ ይሻሻል!’ የሚል መፈክር ይዛችሁ ውጡ” ማለት – “አመፅና ሁከትን በማነሳሳት – ‘inciting violence and protest’” በሚል ያስከስሳል፤ በሰላማዊ ሰልፍ መንገድ ከተዘጋ – “የሕዝብ አገልግሎትን በማቋረጥ – “disruption of public services’” በሚል አንቀፅ፤ ሰልፈኞቹን “አይዟችሁ በርቱ” ብሎ የተናገረ – “ለአሸባሪዎች የሞራል ድጋፍ በመስጠት – ‘providing moral support or …advice’”፤ “አግ7 ወይም ኦነግ በሰላማዊ መንገድ’ ለመታገል ቆርጧል” ማለት – “አሸባሪነትን በማበረታታት – ‘encouragement of terrorism’” በሚለው አንቀፅ ያስከስሳል።

በዚህ መሰረት የሀገራችን የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ የዜጎችን ነፃነት የሚገድብና የፍርሃትና  ስጋት ምንጭ እንደመሆኑ ከሽብርተኝነት ተለይቶ አይታይም። እንደ የቀድሞዋ የእንግሊዝ የሀገር ውስጥ ደህንነት ኃላፊ “Eliza Manningham Buller” አገላለፅ “…What terrorism does is frighten us through its random effect and deter us from behaving normally. But we compound the problem of terrorism if we use it as a reason to erode the freedom of us all.”

ሽብርን በሌላ የሽብር ለመከላከል የሚደረገው ጥረት በራሱ አሸባሪነት ነው። የሽብር ወንጀልን ለመከላከል በሚል የወጣው የኢትዮጲያ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብትና ነፃነት በመገደቡ የህዝብን ሰላምና ደህንነት ሳይሆን፣ የአሸባሪዎች ዓላማና ግብ ማስፈፀሚያ ሆኗል። በመሆኑም፣ የጨቋኞች ፀረ-ሽብርተኝነት በተግባር አሸባሪነት ነው።

የኢትዮጲያ የፀረ-ሸብርተኝነት አወጅ፤ የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚሸራርፍና የሕገ-መንግስቱ መርሆች የሚፃረር፤ በዚህም ከአሸባሪዎች ጥቃት የበለጠ ኢትዮጲያኖችን እያሸበረ ነው። በተለይ ለአዲሱ ትውልድ ትልቅ የፍርሃትና ስጋት ምንጭ ሆኗል። አብዛኞቹ በማዕከላዊ እስር ቤት የሚገኙ መከራና ግፍ እየተፈፀመባቸው ያሉት እስረኞች የዚህ “አሸባሪ ሕግ” ሰለባ ናቸው።

ለዚህ ደግሞ ethiotrailtracker.org የተሰኘው ድህረገፅ ያዘጋጀውን ዝርዝር እንደ ማሳያ መጥቀስ ይቻላል። ድረገፁ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ክሳቸውን በእስር ሆነው የሚከታተሉ እና ጉዳያቸው የተዘጋ በድምሩ የ1405 ዜጎችን ስም ዝርዝር እንደሚከተለው አጠናቅሮታል።

  • በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ክሳቸውን በእስር ሆነው የሚከታተሉ እስረኞች ዝርዝር  (ብዛት 879) ይህን ማያያዥ (Link) በመጫን በፒዲኤፍ ማግኘት ይችላሉ።
  • በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው የተፈረደባቸው [አሁንም በእስር የሚገኙ ወይም ፍርዳቸውን ጨርሰው የተፈቱ] ፣ ክሳቸው የተቋረጠ እና በነፃ የተለቀቁ እስረኞች ዝርዝር (ብዛት 526) ይህን ማያያዥ (Link) በመጫን በፒዲኤፍ ማግኘት ይችላሉ።
Filed in: Amharic