«ምን ነክቶሃል» አልሺኝ?
የመጣ መከራ ሳይነካኝ መች ያልፋል
ሌባን’ኳ ባቅሙ፥
ጎረቤቴን ትቶ – የኔን ቤት ይዘርፋል!
ጀማሪ ቀስተኛ
ቀሽም ተኳሽ ሁሉ፣
ኢላማ ለመማር፣
ወደኔ አነጣጥሮ ፣ ሲተኩስ እያየሽ
ይሄን ሁሉ ችዬ፥
ዝም ስል ብታይኝ “ምን ነካህ” ትያለሽ?
ምን ያልነካኝ አለ?
ሐገሬ ብቀመጥ ፣
የነካሁት ሁሉ፣ ፈጀኝ እንደረመጥ
ሰው ሐገር ብሰደድ፣ ሀዘኔን ለመርሳት
እየ …. ተሳለቁ ለኮሱብኝ እሳት!
የዳሰሰኝ ሁሉ፣
ሊሰቅለኝ ቋመጠ
መስቀል ይሰራ ዘንድ – እልፍ ዛፍ ቆረጠ
በሞቴ ይመስል – የምትድን ነፍሳቸው
በህይወት መኖሬ – ለምን አመማቸው?
አዎ!
ቃል ከአፌ ነጥፎ ዝም ስል ብታይኝ
ቢያስፈራም ፀጥታው ፥ “ምን ነካህ?” አትበይኝ!
ምን ያልነካኝ አለ?
ስቃዬን እንደስንቅ
መከራን እንደትጥቅ
በጀርባዬ ይዤ
ከሲኦል ሸሸሁ ስል – ሲኦል እወድቃለሁ
ሺህ ግዜ እየሞትኩ – ሺ ግዜ ‘ነቃለሁ
እንዳሳ ነባሪ – ውሃ ነው ህይወቴ
አፈር እየናፈቅሁ – ባህር ላይ ነው ሞቴ
ወዲያ ብሄድ መስቀል፣
ከዚያ ብሸሽ ጅራፍ – በአበባ ፈንታ፣
እዚህ የሾህ አክሊል ፣ እዚያ ጎለጎታ
የረገጥሁት ሁሉ፣
እሾህ እያወጣ ሲወጋኝ እያየሽ
“ምን ነካህ” ትያለሽ?
ምን ያልነካኝ አለ?