>

አርቲስት ጥላሁን ጉግሳ ምን ነካው? (ክንፉ አሰፋ)

 

betoch-yeqen-gebiከአጭር ግዜ እረፍት በኋላ፣ EBC ላይ ብቅ ያለው “ቤቶች” በተሰኘው ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ በክፍል185 እጅግ አስደምሞናል። ተመልካቹ ህዝብ በማህበራዊ ድረ-ገጾች ጥለሁን ጉግሳ ላይ እየወረደበት ያለው “አሽቃባጭ፣ የወያኔ አቃጣሪ…” ወዘተ ውግዘቶችና ስድቦችን ባልጋራም፣ ይህ አንጋፋ አርቲስት ጥበብን የፖለቲካ መደለያ ስለማድረጉ ግን ምስክር አያሻም።  በአንድ ወቅት እጅግ ተወዳጅ የነበረ ይህ ድራማ በመጠነኛ የህወሃት ልማታዊ ቅኝት እየተቃኘ መጥቶ አሁን ላይ ወገን የለየ ይመስላል።   ዶፍ ሲጥል ገሚሱ ይበሰብሳል፤ ሌላው ተጠልሎ ይመለከታል፣ ጥቂቱ  ደግሞ ይቀልዳል። ቀልደው ሞተዋል!

ይህንን ድራማ ስመለከት፣ ገሃዱን አለም ከምናቡ አለም በቅጡ ሳይለዩ፣  ሃያልነትዋን ያልተረዱ አርቲስቶች ጥበብን ለተልካሻ ጉዳይ ሲመነዝሩዋት አስተዋልኩ። ወዶ ይሁን ተገድዶ ብቻ፣ በህዝብ ላይ የተከፈተ ጦርነት ላይ ተሰልፎ ፣ በተለይ ለጥበብ ጥብቅና ቆሞ ሲገዘትላት ከኖረ ስው ማየቱ ደግሞ የበለጠ ያምማል።

“…ምን ፍትህ አለ እያልን እጃችንን አጣጥፈን እንቀመጣለን። ይህ ትክክል አይደለም።… “ይለናል አንጋፋው ጥላሁን ጉግሳ። ይህንን የስክሪፕት ረቂቅ ልቦናው ይንገረው ወይንም ድግሞ  ህወሃት እንጃ።  ነጋዴዎች ቅረታቸውን በአግባቡ ለሚመለከተው ክፍል እንዲያቀርቡ የሚመክረው የጥበብ ሰው  የመንግስት አካላትም ሲያጠፉ እንደሚከሰሱ በዚሁ ትወና አስረግጦልናል።  ግና እነዚህ ባለስልጣናት መች እና የት እንደተከሰሱ ጨምሮ ቢነግረን ኖሮ ከውግዘቱ ይድን ነበር።  “(የግብሩ) ትመና ፍትሃዊ ነው።”   በሚለው ላይ ጸንቶ ሲያበቃ፣  “አንዳንድ” ያላቸው ነጋዴዎች በማጭበርበር ላይ እንደተሰማሩም ይጠቁማል።

ከሕዝብ የምንሰማው ግን ሌላ ነው። ነጋዴዎች በመገኛኛ ብዙሃን እየቀረቡ፣ የተጣለብን ግብር አግባብ አይደለም ቅሬታችንን የሚሰማ አካል አጣን ነው የሚሉን። ጥበብ የገሃዱ አለም ነጸብራቅ እንጂ ተቃራኒ የሚለውን አስተምሮት ጥላሁን በዚህ ተውኔቱ አሳየን።

ለመሆኑ ለፍቶ አዳሪውን ነጋዴውን “አጭበርባሪ” እያሉ በአደባባይ መሳደብ ጥበብ ነውን?

“መረጃ  ደብቀውናል። ያለመረጃ ነው ውሳኔ የምሰጠው” እያሉ የሚያላዝኑት ሃይለማርያም ደሳለኝ እንኳን ደፍረው “በሃገሪቱ ፍትህ አለ” ብለው አይናገሩም።

“ወጣ ወጣና እንደሸምበቆ…” አለ ያገሬ ሰው። ቀጣዩ ስንኝ አያድርስ ነው። ከአጀማመሩ አምሮ ዝናው ሲገንን፣ ነገር አለሙን ወዲያ ሲል የሚወርድ ዱብዳ ነገር።  አያድርስ ነው። ሕዝብ “ስራህን ወደድነው።” ሲለው ድራማው የእስትንፋስ ያህል ያስፈልገው እየመሰለው የሚሳሳት ጥቂት አይደለም።

ወትሮውን በየመገናኛ ብዙሃን እየቀረቡ “ሃብታችን ሕዝብ ነው፣ …!” ሲሉ የሚደመጡ አርቲስቶቻችን ከግዚያዊ የግል ችግራቸው በዚህ መንገድ ያመልጡና፣  አንዳች ማዕበል ሲነሳ ደግሞ ከሕዝብ ሲላተሙ ማየት ሳያስተዛዝብ አልቀረም።

ወገን  በኢ-ፍትሃዊ የግብር ተመን ተወጥሮ እያለቀሰ ባለበት በዚህች ቀውጢ ወቅት፣  እንደ ሙሴ “ህዝቤን ልቀቅ!” ማለት እንኳን ባይገድደው ብሶቱን በዚያች ትንሽ ቀዳዳ ማሰማት ያባት ነበር። ነገሩ ተገበጠና ጭራሽ በዱብዳ የግብር አዋጅ እየተሰቃየ ያለውን ነጋዴ አብሮ መውጋት ጀመረ።

የቤቶች ድራማ ከጥበባዊ ይዘቱ ወደ ልማታዊ ይዘቱ ማጋደል የጀመረው መሃል መንገድ ላይ እንደነበር አስታውሳለሁ። ባልጠፋ የሙያ ሰው፣ ባልጠፋ የጥበብ አፍቃሪ፣ ጥላሁን ጉግሳ  እነ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ጠርቶ በአደባባይ ስራውን ሲያስገመግመው ነው ቤቶች የህወሃትን ጠረን ያያዘው። ከዚያን ግዜ ጀምሮ ኩምክናውና ጥበቡ ለዛውን አጥቶ፣ ልማት ተኮር ሆነ።

የጥበብ ሰው ለህብረተሰቡ ፍትህ የሚቆም።  ከፊትም ተስልፎ መስዋዕት የሚሆን እንጂ ሕዝብ አቤት ብሎ የሚተነፍስበት ቀዳዳ ባጣበት ግዜ፣ ይልቁንም በቁስሉ ላይ እንጨት የሚሰድድ አይደለም። የቤቶች ድራማም ቢሆን ከነጋዴው ትከሻ ላይ ተንጠልጥሎ ነጋዴውን መልሶ እንደ አጭበርባሪ አድርጎ ማቅረብ የጤና ነው?

በንግዱ ማህበረሰብ ላይ በመረጃ ሳይሆን በግምት የተቆለለው የገቢ ግብር ተገቢ አይደለም። ይህ  ደግሞ በሁሉም የህብረተሰብ ክፍል መወገዝ ያለበት ጉዳይ ነው።

“ህዝቡ አጎብዳጆች ይለናል።” ብላ ነበር አርቲስት አስቴር በዳኔ በአንድ ወቅት። ለጥበብ ሰው ከዚህ በላይ ሞት የለም። ከምንወድዳቸው የጥበብ ሰዎች እንዲህ አይነቱን ስናይ ደግሞ ያምማል!።

Filed in: Amharic