>

ሆድ ያባውን ቻርተር ያወጣዋል (መስከረም አበራ)

meskerem-aberaበሃገራችን መንግስዊ ስልጣን ላይ መሰየሙ ለኢህአዴግ ከሰጠው ጥቅም አንዱ የፈለገውን ፖለቲካዊ አጀንዳ ለእርሱ የፖለቲካ ትርፍ የሚጠቅመው በመሰለው ወቅት እና ሁኔታ አንስቶ ወደ ጠረጴዛ ማምጣቱ ነው፡፡ አለቅነቱ ያመጣለትን በጎ ሁኔታ በመጠቀም ኢህአዴግ እሩብ ምዕተ ዓመት ሙሉ ወደ መረሳት በተጠጋ መልኩ ሲያድበሰብሰው የኖረውን ለኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ የተሰጠ ህገ-መንግስታዊ መብት ጉዳይ ዛሬ ትኩስ አድርጎ እነሳው ይገኛል፡፡ የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ ሊኖረው ይገባል ተብሎ በህገ-መንግስት የተሰጠውን መብት አፈፃፀም አስመልክቶ መንግስት ያወጣውን ረቂቅ አዋጅ ከሰሞኑ ይፋ አድርጓል፡፡ዶክመንቱ በመንግስት ይፋ ከመደረጉ በፊት ጉዳዩን አስመልክቶ ማን እንዳወጣው ያልታወቀ ዝርዝር አንቀፆችን የያዘ ሰነድ በተለያዩ ድህረገፆች ተለቆ፣ በሰፊው ተነቦ፣ እጅግ ሲያነጋገር ሰንብቶ ነበር፡፡ዶክመንቱ በተለይ በውጭ ሃገር የከተሙ የኦሮሞ ምሁራንን ቀልብ የሳበ የመነጋገሪ አጀንዳ ሆኖ ከርሟል፡፡

ኢህአዴግ መራሹ የሃገራችን መንግስት ለእሩብ ምዕተ አመት ዝም ብሎት የቆየውን አጀንዳ ዛሬ ለምን ማንሳት ፈለገ? የሚለው ተገቢ ጥያቄ ነው፡፡ እርግጠኛውን መልስ የሚያውቀው መንግስት ራሱ ቢሆንም መላምቶችን መሰንዘር ግን ይቻላል፡፡ መንግስት የአዲስ አበባ መስተዳድርን ከኦሮሚያ አጎራባች ዞኖች ጋር አቀናጅቶ ለማልማት የሚያስችል እቅድ አውጥቼ ተግባራዊ አደርጋለሁ በማለቱ ባለፈው አመት ከኦሮሚያ ክልል ነዋሪዎች ከፍተኛ ተቃውሞ ስለገጠመው በቃ ትቼዋለሁ ማለቱ ይታወሳል፡፡ ሆኖም ኢህአዴግ ከሚታወቅበት ማድረግ የፈለገውን ሳይደርግ እንደቅልፍ ያለመተኛት ባህሪ አንፀር ነገሩን በአፉ እንዳወራው እርግፍ አድርጎ ይተወዋል ማለት ያስቸግራል፡፡ እናም ከአንድ አመት በኋላ ይህን ዶክመንት ይፋ ማድረጉ፣ በዶክመንቱ ውስጥ የተዘረዘሩ ሃሳቦች የኦሮሚያ አጎራባች ዞኖችን ከአዲስ አበባ ጋር በተለያዩ መሰረተ ልማቶች ለማቆራኘት የታለሙ አንቀፆች ከመኖራቸው፣ እንዲሁም የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ወሰን አሁንም በቁርጥ ያልተቀመጠ ከመሆኑ፣የአዲስ አበባ አጎራባች የኦሮሚያ ዞኖች የሚኖሩ አርሶ አደሮች መሬቱ ለልማት ከተፈለገ ካሳ ይከፈላቸዋል እንጅ መነሳታቸው አይቀርም ከሚለው የአዋጁ ክፍል ጋር ሲጣመር የአፈፃፀም አዋጁ ለረዥም ወራት ተቆጥቶ የነበረው የክልሉ ህዝብ ከአንድ አመት ገዘፍ ያለ እስር፣እጎራና እና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ካመጠው ድንጋጤ በኋላ በጉዳዩ ላይ ያለውን ስሜት ለመለካት ያለመ ትልቅ የግመታ ተልዕኮ ያነገበ ይመስላል፡፡

ሌላው መላምት አቶ ጌታቸው ረዳ ‘እሳት እና ጭድ የሆኑ ቡድኖች አንድነት ያሳዩት እኛ ስራችንን ስላልሰራን ነው’ ካሉት ንግግር ጋር ይቆራኛል፡፡ከአመት በፊት በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች ተነስቶ በነበረው ህዝባዊ እንቅስቃሴ የሁለቱ ክልል ህዝቦች ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ባልተለመደ ሁኔታ የትብብር ዝንባሌ ማሳየታቸውን ኢህአዴግ በበጎ ጎኑ እንዳልተመለከተው፤ይልቅስ የመንግስቱ ድክመት ያመጣው ክፉ ውጤት አድርጎ እንዳሰበው የአቶ ጌታቸው ንግግር ምስክር ነው፡፡ በዚህ ግንዛቤ ውስጥ የከረመው የኢህአዴግ መንግስት ታዲያ “የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም” የምትል ከዲሞክራሲያዊ አስተዳደር ጋር ክፉ ፀብ ያላት ሃረግ ያዘለ አዋጅ አስነግሯል፡፡ ልዩ ጥቅም የሚለው ቃልPrivilege የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል ይወክላል፡፡ ይህ ቃል ደግሞ የዲሞክራሲ ዋና ከሆነው የዜጎች እኩልነት መርህ ጋር በእጅጉ ይጣላል፡፡ዲሞክራሲ በሰፈነበትም ሆነ ወደ ዲሞክራሲ እያመራ ባለ ሃገር የአንድ ወገን ልዩ ጥቅም የሚባል ነገር ማንሳት ወደ ሰሜን ለመሄድ ተነስቶ ወደ ደቡብ እንደ መንጎድ ያለ አልተገናኝቶ ነገር ነው፡፡ ለኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ ልዩ ጥቅም የሚያስገኘው አዋጅ መነሾ አሁን በስራ ላይ ያለው ህገ-መንግስት ነው ሲባል የህገ-መንግስቱ ምንጭስ ማን ነው? ወደ ሚለው ወሳኝ ጥያቄ ይመራል፡፡

ህገ-መንግስቱ እርሾ የሆነው የሽግግር ዘመኑ ቻርተር በሻዕብያ፣በህወሃት እና በኦነግ ለተፈጠሩበት አላማ እንዲያገለግል ሆነኖ ተቦክቶ ተሰልቆ ካለቀ በኋላ፤ ሰፍቶ ተስፋፍቶ ህገመንግስት ይሆን ዘንድ በህገ-መንግስት አርቃቂ ኮሚሽኑ በኩል ለህዝብ ውይይት ይቅረብ የተባለው እንደው ለቡራኬ ያህል ብቻ እንደሆነ በወቅቱ የነበሩ እንደ አቶ አሰፋ ጫቦ ያሉ ፖለቲከኞች ይመሰክሩት የነበረ ሃቅ ነው፡፡ ህወሃት ኦነግ እና ሻዕብያ የሽግግር ዘመኑ አድራጊ ፈጣሪዎች እንደመሆናቸው ህገ-መንግስቱን ባዋለደው በዚህ ወሳኝ ወቅት እነዚህ “ሶስቱ ኃያላን” ያልወደዱት አካል ለምሳሌ የአማራው ብሄር እና የኢትዮጵያዊ ብሄርተኝት አቀንቃኝ ዜጎች ሃሳብ ፣እምነት እና ፍላጎት በቅጡ አልተወከለም፡፡ስለዚህ የህገ-መንግስቱ አረቃቅም ሆነ ኢትዮጵያ ከሽግግር መንግስት ወደ ተመራጭ መንግስት ተዘዋወረች የተባለበት ሂደት የኢትዮጵያን ህዝብ ሁሉ የወከለ አካሄድ አልነበረም፡፡ይህን የሂደቱ ዋና ተዋናይ የነበሩት ዶ/ር ነጋሶም ደግመው ደገግመው የሚመሰክሩት ብቻ ሳይሆን የሂደቱ አካል “በመሆኔም እፀፀታለሁ” ያሉበት ነው፡፡

ህገ-መንግስቱ የረቀቀበት መንገድ እንዲህ አንዱን ጥሎ አንዱን አንጠልጥሎ ቢሆንም ኢህዴግ ስህተት እንደሌለው መለኮታዊ መዝገብ ቆጥሮት የህገ-መንግስቱን ስም ስንቅ አድርጎ ወሳኝ የፖለቲካ ቁማሮችን በአሸናፊነት ይወጣበታል፡፡ራሱን ህጋዊ ባላንጦቹን ህገ-ወጥ አድርጎ ህግን በመናድ ከሶ ዘብጥያ ያወርድበታል፡፡ ያሰበውን ለማድረግ እንደ እጁ መዳፍ በሚያውቀው ህገ-መንግስት የተፃፈውን መጥቀስ ቀርቶ ከዛም በላይ የሚሄደው ኢህአዴግ በዚህ አዋጅም ያየነው የተለመደውን ማንነቱን ነውና እግዚኦ የሚያስብል ነገር የለውም፡፡የሚገርመው ነገር ያለው ሌላ ቦታ ነው- በአክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኝነት አቀንቃኝ ፖለቲከኞች መንደር፡፡

ከስራው አንድ አፍታ የማይዘናጋው፣ የሚያተርፍበት የመሰለውን የፖለቲካ ቁማር አጥብቆ በመያዝ የሚታወቀው ኢህአዴግ ለኦሮሚያ ክልል ከሃያ አምስት አመት በፊት የማለላትን በአዲስ አበባ ላይ የልዩ መብት ባለቤት የመሆን ቃል ለመፈፀም አዋጅ አውጥቻለሁ ሲል በገራገርነት ቃሉን ለማክበር አስቦ ብቻ አይመስልም፡፡እንደሚታወቀው መንግስት ይህን ረቂቅ አዋጅ ያወጣው ፓርላማው ለእረፍት በሚዘጋበት ወቅት ነው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት በአዋጁ ዙሪያ ከህዝቡ የሚነሱ አስተያቶችን፣ የፖለቲከኞችን አሰላለፍ በማጤን ራሱን የፖለቲካ ትርፍ በሚያጋብስበት መስመር ለማሰለፍ ነገሮችን የማጤኛ ጊዜ ለማግኘት ይመስለኛል፡፡ይህን ይበልጥ የሚያስረዳው አቶ ለማ መገርሳ ደግመው ደጋግመው አዋጁ ለውይይት ክፍት ነው እንጅ ያለቀለት አይደለም ሲሉ መሰንበታቸው ነው፡፡ በተጨማሪም መንግስት በቴሌቭዥኑ የአፈፃፀም አዋጁን ከማወጁ በፊት ቀደም ብሎ ባለቤቱ ያልታወቀ ዶክመንት በማህበረዊ ድህረገጾች እንዲከላወስ ሲደረግ፣ብዙ ሲያነጋግር መንግስት አለሁበትም የለሁበትምም ሳይል ድምጹን አጥፍቶ የነገሮችን አካሄድ ሲከታተል ሰነበተ፡፡ከርሞ ከርሞ በቴሌቭዥኑ ያስነገረው አዋጅ የወጣበት ጊዜም እንዲሁ በድንገት የተደረገ አይመስለኝም፡፡ በዚሁ ጊዜ ትቂት የማይባሉ የኦሮሞ ብሄር ፖለቲከኞች ሰተት ብለው ወደ ወጥመዱ ውስጥ ሲገቡ በሰነዱ ውስጥ እጅግ የተገለለው፣እንደሌላ ሊቆጠር ምንም ያልቀረው የኢትዮጵያ ብሄርተኝት አቀንቃኙ አካል ዝምታን መርጦ ከኢህአዴግ ጋር ካብ ለካብ መተያየቱን መረጠ፡፡አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኝነት ፖለቲካ አራማጆች ብቻ ሳይሆን ምሁራን ጭምር ባለቤቱ እንኳን በውል ባልታወቀ ሰነድ ዙሪያ አስደንጋጭ የክርክር ነጥቦች ያዘሉ ረዣዥ ክርክሮች አምጥተው ራሳቸውን ለግምት አደባባይ አሰጡ፡፡ምሁራን ተብየዎቹ በመገናኛ ብዙሃን(በኦ.ኤም.ኤን እና በቪኦኤ) ቀርበው ሲወያዩ በጆሮየ የሰማኋቸውን እና የገረሙኝን ብቻ ላንሳ፡፡

“የባለቤትነት” እና “የልዪ ጥቅም” እሳቤዎች ንትርክ

ባለቤቱ ያልታወቀው ሰነድ የአዲስ አበባ አደባባዮችን ለመጠቀም ሳይቀር የኦሮሞ ብሄር ተወላጆች በአዲስ አበባ ለሚጠይቁትን ነገር ቅድሚያ እንዲያገኙ ይደረጋል በሚሉ አንቀጾች ተሞላውን ሰነድ እየጠቀሱ ይህ እጅግ ትንሽ ነገር እንደሆነ እና በአዲስ አበባ ላይ ባለቤት የሆነውን የኦሮሞ ህዝብ እንደ እንግዳ ቆጥሮ በገዛ ቤቱ ሊያስተናግድ እንደሞከረ ደፋር እንግዳ ቆጥረው አብጠልጥለውታል፡፡መሆን ያለበትን ሲያወሱም ከዶክመንቱ ስያሜ ጀምሮ መሆን ያለበት የባለቤትነት አዋጅ እንጅ የልዩ ጥቅም አዋጅ መሆን እንደሌለበት ነው፡፡ተከራካሪዎቹ ሲያክሉም በአዲስ አበባ የሚኖር ማንኛውም ከኦሮሚያ ክልል ውጭ የሆነ ተቋምም ሆነ ሌላ አካል የሚኖረው በኦሮሚያ ምድር መሆኑን እንዲያስታውስ፣ትንሽም ብትሆን አመታዊ ግብር ለኦሮሚያ ክልል መክፈል አለበት፣ ቀረጥ እና ግብር በሚከፈልባቸው የጉምሩክ ጣቢዎች ላይም በርከት ያሉ ኦሮሞ ተወላጆች ሊታዩ ያስፈልጋል፣ አዲስ አበባ ራሷም መተዳደር ያለባት በኦሮሚያ ክልል ስር እንጅ በፌደራል መንግስቱ ስር መሆን የለበትም ይላሉ፡፡ ሌላው አስገራሚም አስቂኝም የሆነው የክርክር ነጥብ ጭብጥ ደግሞ ይህን ይላል፤ ‘አሁን አዲስ አበባ የሚኖረው አብዛኛው ሰው የከተሜነት ዲሲፕሊን የሚያንሰው፣በሌሎች ዓለማት ያሉ የከተማ ነዋሪዎች የተላበሱት ትህትና የሚጎድለው፤ ለኦሮሞ ባህል እና ማንነት ክብር ለማሳየት የሚለግም ነው፡፡ ይህ ዝንባሌ መስተካከል አለበት፡፡በአዲስ አበባ መኖር የሚቻለው ባለቤቱን የኦሮሞ ህዝብ እስካበሩ ብቻ ነው፡፡ ይህን እስካደረገ ድረስ መኖር ይችላል ካልሆነ ግን አዲስ አበባን ለባለቤቶቿ ለቆ ሌላ ሰፊ ቦታ ፈልጎ አዲስ ዋና ከተማ መመስረት ነው፤አዲስ ሚመሰረተውን ዋና ከተማ ኦሮሚያ ላይ ማድረግም ይቻላል፡፡’ ይሄ ኦነግን አደቁኖ ካቀሰሰው ‘የውጡልኝ ከሃገሬ’ ፖለቲካዊ ፈሊጥ የተቀዳ ነው፡፡ ወንድም ህዝብን ማግለልን እንደ ፖለቲካ ስኬት ዳርቻ የሚቆጥረው የኦነግ መናኛ ፖለቲካዊ አካሄድ ፓርቲውን እድሜ ብቻ አድርጎት እንደቀረ ተረድቶ ራመድ ማለት ፖለቲካዊ ብስለትን ይጠይቃል፡፡ ኦነግ እንኳን ብሎት ብሎት አልሆን ሲለው የተወውን ውራጅ ፖለቲካ ትርክት አንግቦ መንገታገት ራስን የፖለቲካ ማስፈራሪያ ከማድረግ፤ ቆምኩለት የሚሉትን ህዝብም በጥርጣሬ ከማሳየት ያለፈ ጥቅሙ አይታየኝም፡፡

የዚህ ሁሉ ምንጭ የሆነውን ‘አዲስ አበባ የኦሮሞ ህዝብ የብቻ ታሪካዊ እርስት ነች’ የሚለውን አስገራሚ እሳቤ ብንቀበል እንኳን ቀደምት የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ናቸው የተባሉት ኦሮሞዎች መኖሪያ የነበረችው አዲስ አበባ እና የአሁኗ አዲስ አበባ የተለየች መሆኗን ማገናዘብ ይህን ያህል ከባድ ነገር አይደለም፡፡ ከባዱ ነገር ከላይ ባሉት ተከራካሪዎች መጤ ይሁን ሰፋሪ እየተባሉ ያሉት ኦሮሞ ያልሆኑ ህዝቦች ላባቸውንም እድሜያቸውንም ጨርሰው ያቀኗትን አዲስ አበባን ጥለው ወደ መድረሻቸው ይድረሱ፤ ወይም ሌላ ረባዳ መሬት ፈልገው የሃገራቸውን ዋና ከተማ ይመስርቱ የሚለው ሃሳብ ይሰምርልኛል ብሎ ወደ አደባባይ ይዞ መቅረቡ ነው፡፡ከሰሞኑ በቪኦኤ ቀርበው የሚከራከሩ ዶ/ር ኃ/መስቀል የተባሉ ሌላ የኦሮሞ ምሁር ደግሞ ሌላ ክርክር ያመጣሉ፡፡ ሰውየው ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በሃረርም፣ በድሬዳዋም፣በሞያሌም ላይ ኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ሊከበርላት ይገባል ሲሉ በህገ-መንግስቱም ያልተጠቀሰ ሰፋ ያለ ፍላጎት ያለው ጥያቄ ያነሳሉ፡፡ የሰውየው ክርክር መነሾው እነዚህ ከተሞች ኦሮሚያ ክልል መሃል ላይ ያሉ መሆናቸው ነው፡፡ ሐምሌ 8/2009 ከወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ቃል-ምልልስ ያደረጉት ዶ/ር ነጋሶ ሃረርም በኦሮሚያ መሃከል ስለምትገኝ በሚል ኦነግ በሽግግሩ ወቅት የኦሮሚያ ክልል በከተማዋ ላይ ልዩ መብት እንዲኖረው ጥያቄ አቅርቦ ምክንያቱን በማላውቀው ነገር ህገመንግስቱ ውስጥ ሳይካተት ቀርቷል ይላሉ፡፡፣

ከላይ የተነሱት የኦሮሞ ብሄርተኛ ፖለቲከኞች እና ምሁራን የክርክር ነጥቦች ሲጠቃለሉ አሁን ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ያላትን መብት የባለቤትነት እንጅ የልዩ ጥቅም ጉዳይ መሆን የለበትም፡፡የኦሮሚያን ህገመንግስታዊ ልዩ መብት ለመተግበር ወጣ የተባለው ረቂቅ አዋጅም መቃኘት ያለበት ከዚሁ አንፃር ነው የሚል ነው፡፡ ከዚህ በተቃራው የቆመው፤ የአዲስ አበባ ነዋሪም ሆነ ከተማዋን እንደ የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት አንድያ መገለጫ ምድር አድርጎ የሚያስበው ዜጋ ይህን የኦሮሞ ብሄርተኛ ፖለቲከኞችን እና ምሁራን ክርክር ትዝብትም፣ጥርጣሬም፣ድንጋጤም ባጠላበት ዝምታ ነው ያስተዋለው፡፡እንደውም ከነዚህ አይነት የኦሮሞ ብሄርተኞች ይልቅ ቢያስ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በአዲስ አበባ እንዲኖር የፈቀደው ኢህአዴግ እጅግ የተሻለ እንደሆነ ቢታሰብ የሚገርም ነገር የለውም፡፡ የኢህአዴግ እቅድም ይኽው ነው – ለመገመት የተዘጋጀን ማስገመት፤ በዚህ ውስጥ ራሱን የተሻለ መድህን አድርጎ ማሳየት! ሲቀጥልም ለአንድ ሰሞን ሲሰማ የነበረውን የአማራ እና የኦሮሞ ህዝቦችን የትብብር ድምፅ በነዚህ የኦሮሞ ምሁራን እና ፖለቲከኞች ድምፅ በመተካት ሃያ አምስት አመት ሲሰበክ የኖረውን የጥርጣሬ እና የመፈራራት መንፈስ መልሶ በቦታው እንዲተካ ማድረግ ነው፡፡አቶ ጌታቸው ረዳ ኢህአዴግ ቸል አለው ያሉት የቤት ስራም ይሄው ሳይሆን አይቀርም፡፡

አንድም አፍታ ከስራው መዘናጋትን የማያውቀው ኢህአዴግ ይህን ቻርተር ይዞ ብቅ ሲል የኦሮሞ ምሁራንም ቻርተሩ ይስመር አይስመር እንኳን በውል ሳያጤኑ ሆዳቸው ያባውን ሁሉ ትዝብትን ሳይፈሩ አውጥውታል፡፡ ጭራሽ የኦሮሞ ህዝብ አንድ አመት ሙሉ ሲሞትለት የኖረው ጥያቄ አዲስ አበባን በባለቤትነት የማስተዳደር ጉዳይ ብቻ እንደሆነ ለማድረግም ይቃጣዋል ክርክራቸው፡፡ባለፈው አመት የኦሮሞ ህዝብ አምርሮ ሲያነሳው የኖረው አንገብጋቢ ጥያቄ ከኖረበት ቀየው በድንገት ባዶ እጁን ወይም እፍኝ በማትሞላ ካሳ መፈናቀሉን በመቃወም እንጅ አዲስ አበባን ለኦሮሞ ቤት ለሌላው የሰው ቤት ለማድረግ አልነበረም፡፡የልሂቃኑ ክርክር እና የአገሬው ኦሮሞ ችግር እና ፍላጎት ይህን ያህል አልተገናኝቶ መሆኑ ግር ያሰኛል፡፡ከሃገር ርቀው እንደመኖራቸው ሃገርቤት ያለውን ኦሮሞ መሰረታዊ ጥያቄ ለማወቅ ይቸገራሉ ቢባል እንኳን ቆምኩለት ከሚሉት” ህዝብ የልብ ርትታ እንዲህ እጅግ መራራቁ ጤናማ አይመስልም፡፡

አክራሪ የኦሮሞ ብሄረተኝነት ፖለቲከኞች ደጋግመው የሚያነሱት ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ሊኖራት ይገባል የሚሉት የባለቤትነት መብት ጥያቄ ማስረጃ አድርገው የሚያነሷቸው ነጥቦች ወደ ሶስት ማጠቃለል ይቻላል፡፡ አንደኛው እና ለተቀሩት መከራከሪያ ነጥቦች መሰረት የሚሆነው ኦሮሞዎች የአዲስ አበባ ቀደምት ህዝቦች ናቸው የሚለው ትርክት ነው፡፡ለዚህ ትርክት ከማለት ባለፈ በበቂ ታሪካዊ መዛግብት የተደገፈ ማስረጃ ከተከራካሪዎች ሲቀርብ አላጋጠመኝም፡፡ ይልቅስ ከዚህ እሳቤ በተቃራኒው የቆሙ ተከራካሪዎች የተሻለ የታሪክ ማስረጃ አቅርበው ይከራከራሉ፡፡ሁለተኛው የሃገራችን ህገ-መንግስት ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ልዩ መብት እንዲኖራት ስለሚያዝ ነው የሚሉ ናቸው፡፡ሶስተኛው የክርክሩ ማስረጃ አዲስ አበባ(ሐረር፣ድሬዳው፣ሞያሌ ጭምር የሚሉ ተከራካሪዎችም አሉ)በኦሮሚያ ክልል መሃል የምትገኝ በመሆኗ ከኦሮሚያ የተለያዩ የተፈጥሮ ሃብቶችን ስለምትጠቀም፣ከተማዋ ለውጋጆቿ መዳረሻም አጎራባች የኦሮሚያ ዞኖችን ስለምትጠቀም ኦሮሚያ በከተማዋ ላይ ልዩ ጥቅም ያስፈልጋታል የሚል ነው፡፡ እነዚህ የክርክር ማስረጃዎች ተደርገው የቀረቡ እሳቤዎች ራሳቸው ሊጠየቁ የሚገቡ በመሆናቸው በሚቀጥለው እትም እመለስባቸዋለሁ፡፡

Filed in: Amharic