>

ጄኔራል ክንፈ ሊታሰሩ ይችላሉ የሚል ጭምጭምታ አይሏል! [ዋዜማ ሬዲዮ]

ጄኔራል ክንፈ ሊታሰሩ ይችላሉ የሚል ጭምጭምታ አይሏል!

Wazema Radio– ከረፈደ የተጀመረው የኢህአዴግ የፀረ-ሙስና ዘመቻ የሜቴኩን ጄኔራል ክንፈ ዳኜን ሊነካ ይችላል የሚል ጭምጭምታ ከሜቴክ ሠራተኞች ከራሳቸው መስተጋባት ከጀመረ ሳምንታት ተቆጥረዋል፡፡ ከወር በፊት  ታይቶ በማይታወቅ ድፍረት በተወካዮች ምክር ቤት አባላት  ክፉኛ የተተቹት ጄኔራል ክንፈ ‹‹‹በግሌ የማምነው ለዚህ አገር ልማት እየወደቅንና እየተሰዋን እንደምንሠራ ነው፡፡ መጠየቅ ካለብኝ እኔ ልጠየቅ፡፡›› ካሉባት ዕለት ጀምሮ ሰውየው በደኅንነቶች ሊደፈሩ ይችላሉ የሚለው ጭምጭምታ ሲራገብ ቆይቶ ነበር፡፡
ከሰሞኑ የጸረ ሙስና ዘመቻ ጋር ተያይዞ ይኸው ጭምጭምታ እያደገ መጥቷል፡፡ በተለይም የርሳቸው ጽሕፈት ቤት የሚገኝበትና ከሜክሲኮ ወደ ሳርቤት የሚወስደው ዋና መንገድ ላይ በስተቀኝ የሚገኘው የመከላከያ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ግቢ ሠራተኞች በክበባቸው ሻይ ቡና እያሉ የሚያወሩት ይህንኑ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ትልቁ አለቃቸው ከዛሬ ነገ ችግር ውስጥ ሊገቡ እንደሚችሉ መጠርጠር የጀመሩት በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የደኅንነት ሰዎች በመሥሪያ ቤቶቻቸው በስፋት ማንዣበባቸውን ተከትሎ ነው፡፡
ቶቶት አካባቢና ኤምፔሪያል አሞራው ሕንጻ ዉስጥ የተጠለሉ የሜቴክ ሠራተኞችም ቢሆን ትልቁ አለቃቸው የማይደፈሩ እንደሆኑ ቢያውቁም ሊታሰሩ ይችላሉ የሚለው ሀሜት በስፋት መወራቱ አሳስቧቸዋል፡፡ ዘመቻውን በሚመራው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ጽኅፈት ቤትና አቶ ጌታቸው አሰፋ በሚመራው የመረጃና ደኅንነት ቢሮ መካከል የጄኔራል ክንፈ ጉዳይ አለመግባባት መፍጠር የጀመረው ዛሬ አይደለም ይላሉ፣ ነገሩን እናውቃለን የሚሉ ወገኖች፡፡
ጄኔራሉ ከፍ ያለ የአገር ፍቅር ያለው፣ ቀንተሌት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል የሚሠራ፣ በ‹‹ይቻላል›› ጥልቅ መንፈስ የተሞላ መሆኑ በስፋት በከፍተኛ አመራሩ ዘንድ ስለሚታወቅለት ብዙዎች ይሳሱለታል፡፡ በአንጻሩ ጥብቅ የመንግሥት የፋይናንስ አሠራርን  ቸል ብሎ በዘፈቀደና በየዋህነት አንዳንዴም በማንአለብኝነት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ለማስፈጸም በወታደራዊ አስተሳሰብ የሚታትትር መሆኑ ‹‹የዋህና ደፋር ጄኔራል ነው›› ያደርገዋል ይላል አንድ የቀድሞ የሜቴክ ባልደረባ፡፡ ይህ ባህሪው ደግሞ አገሪቷን በቢሊዮን የሚቆጠር ዋጋ እንድትከፍል አድርጓታል ሲል ሐሳቡን ይቋጫል፡፡
ዞሮ ዞሮ የርሱ በሕግ ፊት መቆምና አለመቆም ስለሕወሓትና ስለ ጠቅላላው የኢህአዴግ አሰላለፍ የሚነግረን ብዙ ነገር ይኖራል፡፡

የልማት ባንኩ ሰው የት ጠፉ?

– የልማት ባንኩ የቀድሞ አለቃ አቶ ኢሳያስ ባህረ ሌላው በሐሜት ደረጃ የሚጠበቁ ታሳሪ ናቸው፡፡
በሰፋፊ እርሻዎች ብድር በቢሊዮን የሚቆጠር ብር መባከኑን ተከትሎ ጠዋት ከጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ተሰብስበው ከሰዓት ከኃላፊነታቸው የተሰናበቱት  አቶ ኢሳያስ በአሁኑ ወቅት የት እንዳሉ አውቃለሁ የሚል የለም፡፡ ሆኖም ከኃላፊነታቸው ከመሰናበታቸው ቀደም ብሎ ረፋዱን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በመሩት ስብሰባ አቶ ኢሳያስ በፋይናንስ አማካሪዎችና የፓርቲው ሰዎች ክፉኛ ተብጠልጥለው እንደነበር ይነገራል፡፡ በስብሰባው አቶ ፍጹም አረጋ፣ አቶ አበራ ሙላት፣ አቶ በቃሉ ዘለቀና ሌሎች ኃያል ባለሥልጣናት ተገኝተው ነበር፡፡ ከኦህዴድና ከብአዴን የተወከሉ የፓርቲው ሰዎች ብድር በብሔር እየተሰጠ እስኪመስለን ድረስ ነው በልማት ባንክ እየተሰደብን ያለነው ብለው አስተያየት መስጠታቸው ድንጋጤን ፈጥሮ ነበር፡፡ የልማት ባንክ ለአንድ ብሔር ሰዎች የማድላትን ጉዳይ በድፍረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፊት ከተናገሩት ውስጥ ከሰሞኑ ወደ አርብቶ አደር ጉዳዮች ሚኒስትርነት ዙውውር ያካሄዱት አቶ ከበደ ጫኔ ናቸው፡፡ ከፍ ያለ ውጥረት ሰፍኖበት ነበር የተባለው ይህ ስብሰባ መርገብ የቻለው አቶ ኢሳያስ ራሳቸው በሰጡት የማጠቃለያ ሀሳብ ነበር፤ ‹‹እዚህ የምትተቹኝ ሁላችሁም እየደወላችሁ እከሌን አስተናግደው እያላችሁ ባለሐብት ስትልኩብኝ የነበራችሁ ናችሁ፣ እኔን ለመተቸት ሞራል አላችሁ ብዬ አላምንም፡፡››

አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ስልጠና እየሰጡ ነው

-ለሌላ ዙር ሹመት ታጭተዋል ተብሎ ግምት የተሰጣቸው የአይርላንዱ አምባሳደራችን አቶ ሬድዋን ሁሴን ‹‹ለመካከለኛ ዲፕሎማቶች ስልጠና ለመስጠት ነው የመጣሁት፣ ስለ ሹመት የማውቀው ነገር የለም›› ሲሉ ራቅ ላለ አንድ የቤተሰብ አባል መናገራቸውን የዋዜማ ዘጋቢ በሰው ሰው ሰምታለች፡፡ ምናልባት ከመስከረሙ የኢህአዴግ ጉባኤ በኋላ ጎልቶ ከሚወጣው ቡድን ጋር እዚሁ ቆይተው ቁልፍ ሥልጣን ሊይዙ እንደሚችሉ ግን አሁንም ይጠረጠራል፡፡ በፓርቲው ውስጥ ብዙ ሊጠቅሙ እየቻሉ ነው ያለጊዜያቸው ገለል የተደረጉት ይላሉ ውስጥ አዋቂዎች፡፡

የካሳ መጨረሻ ዋሺንግተን መሆኑ እርግጥ ሆኗል

-የዉጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ምንጮች የሰቆጣው ሰው አቶ ካሳ ተክለብርሃን ወደ ዋሺንግተን ቢሮ መላካቸውን አረጋግጠናል ብለዋል፡፡ ለስላሳ አንደበትና ከኢህአዴግ ሹሞች በተለየ አብዝቶ የማዳመጥ ተሰጥኦ ያላቸው አቶ ካሳ ከወረዳ የጽሕፈት ቤት ኃላፊነት እስከ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤነት፣ ከሲቪል ሰርቪስ ዲግሪ እስከ እስከ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቦርድ ሰብሳቢነት የደረሱት ታጋሽና ቻይ በመሆናቸው ነው ይባላል፡፡  ከአቶ በረከት ስምኦን ጋር በቅራኔ ዉስጥ የቆዩት አቶ ካሳ በስልጣን መሰላል ብዙ መራመድ ያስቡ ስለነበር በአምባሳደርነቱ መሾማቸው ብዙም ደስተኛ እንዳላደረጋቸው ይነገራል፡፡
በተያያዘ ወሬ ወደ ካናዳ ተጉዘው በአቅም ማነስ የሚወረፉትን ወይዘሮ ብርቱካንን ይተካሉ የተባሉት የአቶ እውነቱ ብላታ መጨረሻ ቶሮንቶ ሳይሆን ብራስልስ ነው ብለዋል እነዚሁ ምንጮች፡፡

Filed in: Amharic