(ለሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን
ማስታወሻ ትሆን ዘንድ የተፃፈች)
አላጋጩ አይኔ፣
ከታሪክ ገፅ ላይ ስላቅ እያሰሰ
ፌዘኛው መዳፌ፣
ከትናንት ድርሳን ላይ አሽሙር እያፈሰ
ባባቱ ሲቀልድ፣
ባያቶቹ ሲያሾፍ ፣
ተጉዞ ….. ተጉዞ «አድዋ» ደረሰ!
አድዋ!
ፊደላቱ ሁሉ ስእል እየሆኑ
ያሳዩኝ ጀመረ ታሪኬን አጉልተው
“ሎሬቱ” በብእር፣
ትናንቴን አምጥቶ ፣ ዛሬ ላይ ጎለተው!
አድዋ!
ባባቶቹ ሩጫ፥
መሳቅ የለመደው ፥ ዘመንኛው ጥርሴ
በከንፈሮቼ ስር ፥ መሸሸግን ሲሻ ፥ ገረመኝ ለራሴ!
ሳቅ ይፈጥራል ያልኩት ፥ ያያቶቼ ጀብዱ
ለፌዘኛ አይሆንም፣
በደም ተቀብቷል ፣ ተጋርዷል መንገዱ!
አድዋ!
ሎሬቱ ይፅፋል ፣
ይፅፋል ፣ ይፅፋል
ያባቶቹን ወኔ ፥
በጥበብ ለማስፈር ፥ ብቻውን ይለፋል
ከፊደል ሲታገል ፥
ግዜም እንደነፋስ ፥ በፍጥነት ይከንፋል!
ሱሌኦ ያ ሱሉ ሱሌኦ
«እምቢ አለ ፥ ምኒሊክ እምቢ አለ
ብረት እያማታ፣
ብረት እያጋጨ፣ ጦሩን በሳት ሳለ!
እምቢ አለ!
ምኒሊክ አልታለል አለ
ዳኘው አባ ጎራ
የደጀን ተራራ
አፍሪካን ፣
ኢትዮጲያን ፣ እስከሰሜን ጣራ
በአለም ሊያኮራ
እምቢ አለ ምኒሊክ
ሱሌኦ ያ ሱሉ ሱሌኦ!»
ከነጭም የነጣ ፥
ብራና ጨብጦ ፥ ሎሬቱ ተቆጣ
በላዩ ደርቦ ፥ ያባቶቹን እልህ ፣ ያባቶቹን ቁጣ!
ለሳቅ አይመችም ፥ የገለጥኩት ዶሴ
እንደመሸገ ነው ፥ አልስቅ አለኝ ጥርሴ!
ያዝናናኛል ያልኩት ያያቶቼ ጀብዱ
ፌዘኛ አያስኬድም፥
በአጥንት ታጥሯል ፣ ተጋርዷል መንገዱ!
«በቃ!»
አለች ጣይቱ
አንቶሎኒን አይታ
ብርቅ አይደለም ለኛ
መውጣት ቀራኒዮ መውረድ ጎለጎታ
በቃ!
የነጩን ድንፋታ ፥ በወኔዋ ካደች
የነጩን ከፍታ ፥ በኩራቷ ናደች
እንደእሳት ነድዳ ፥ ጣይቱ ፎከረች
«እግሩን ለሹል እሾህ ፣ ደረቱንም ለጦር
ለሀገሩ ማይይሰጥ፣
አንድም ኢትዮጲያዊ ፣ እዚህ እንደማይኖር
እወቅ አንቶሎኒ
ስማችሁ ራሱ ፥ ውል የለሽ ፥ ውል አልባ
ምኒ ምኒ ምኒ!»
ለካስ እቺ ሐገር
በተረት ላይ ብቻ ፥ ፀንታ አልቆመችም
ጎበዝ ምን ይሻላል?
የአድዋ ታሪክ ፥ ለሳቅ አይመችም!
ሳቅ ይፈጥራል ፥ ያልኩት ያያቶቼ ጀብዱ
ፌዘኛ አያስኬድም፥
በአጥንት ታጥሯል ፥ ተጋርዷል መንገዱ!
አድዋ!
ያለእግር ጠፈር፣
ነጠላ አጣፍቶ ፥ ሊሞት ቤቱን ለቅቆ
የሐበሻ ሬሳ ፥ ይታያል ፈራርሶ ፥ እዚያም-እዚም ወድቆ
አዋራው ይቦንናል ፥ በደም ተቀይጦ ፥ ከደም ተደባልቆ!
ያስፈራል አድዋ!
የፈረሱ ኮቴ ፥ የብረቱ ፍጭት ፥ የቁስለኛው ዋይታ
ሐበሻ ባንድ ላይ፥
ተሰቅሏል ላገሩ ፥ ይኸው ቀራኒዮ ፥ ይኸው ጎለጎታ!
ይኸው የሾህ አክሊል ፥ እነሆ ሚስማሩ
እልፍ ጀግና ወድቋል ፥ ተሰቅሏል፣ ለክብሩ!
እየተፃፈ ነው ፥ በኢትዮጲያ ሰማይ ፥ የሐበሻ ጀብዱ
ለፌዘኛ አይሆንም ፥ በደም ተለቅልቋል ተጋርዷል መንገዱ!
እዚም-እዚያም ፥ ወድቋል የሀበሻ ገላ
ወደፊት ነው እንጂ፣
ማፈግፈግ ነውር ነው ፣ መሸሽ ወደኋላ!
ገበየሁ ወደቀ ፥ ጀግናው ክንዱ ዛለ
ደሙን ሚመልሰው፥ ያ ባልቻ የታለ?
«ባልቻ ሳፎ ኢርጋና
አባ ነፍሶ ያባ ጤና
አካና ታሲፍ ቲካ አካና
ገበየሁ ወድቋል ቶሎ ና!»
«እንዲህ ነች ሐገርህ»
ብሎ ተረከልኝ ፥ሎሬቱ በመንፈስ
ቀለም ደፍቶ አሳየኝ ፥
ሐበሻ ሲታረድ ፥ ላ’ገር ደሙን ሲያፈስ!
ለክብሩ ሲዋደቅ፥
እንደበግ ሲሸለት ፥ ለነፍሱ ሳይሳሳ
ይህ ሁሉ ለኔ ነው ፥
ይህ ሁሉ ግብ-ግብ ፥ ይህ ሁሉ አበሳ
ደልቶኝ እንድራመድ ፥ እርጥብ አፈር ሆኗል ፥ ያያቶቼ ሬሳ!
ይፅፋል ሎሬቱ ያባቶቹን ወኔ
ታሪክን ያትማል ፣ ያስቀምጣል ለኔ!
ለሳቅ አይመችም ፥ የገለጥሁት ዶሴ
እንደመሸገ ነው ፥ አልስቅ አለኝ ጥርሴ!
ወደኋላ ዞሬ ፥
አንድ ሁለት እያልኩኝ ፥ ጀግኖቹን ስቆጥር
ከሩቅ አይሃለሁ!
ፊደላትን ቀርፀህ ፥ ልቤ ላይ ለመትከል ፥ ብቻህን ስትጥር!
እልፍ ህይወት ተከፍሎ ፥
ሐበሻም ድል አርጎ ፥ ጦርነቱ አልቋል
ከድል ባሻገር ግን፥
ከፊደል ሲታገል ፥ አንድ ጀግና ወድቋል!