>

ይኸኛው ሳምንት! [አስፋ ጫቦ]

የማይዘጋ በር

Ato Assefa Chaboባለፈው ሳምንት”የሳምንቴ ትዝብትና ትንግርት! የሚል ጽፌ ነበር። መዝጊያው ላይ ‘የተሻለ ሳምንት ይጠብቀን!” ብዬ ነበር። አሁንም መጠበቅ ሊኖርብን ነው።ወይስ የመጥፎ ጥረን ሲያሸት የኖረው አንቴናየና ሲያይ የኖረው አይኔ ጥሩው እዚያው ቁጭ ብሎ አላይ ብሎ ይሆን? ማን ይመራመር!

አሁንም የምጀምረው “በፕሬዚዳንታቸው!”( የእኔ ፕሬዚዳንት አይድደለም! He is Not My President!) የሚሉት ውስጥ ነኝና በዶናልድ ትራምፕ ልጀመር።

***

ትራምፕ በተሾመ በአምስተኛው ቀን ምርጥ ወታደሮች (Navy Seal) የሚባለውን የአረብ አገር አልቄዳ ለማውደም ወደሶሪያ ላከ። ውጤቱ እነደተለምደው ሕጻናትና ሴቶች አለቁ።ቤቶችም ፈራረሱ1 አንድ የአሜሪካን ወታደር ሞተ። ሌላም ቆሰለ።አንድ አውሮጵላንም ተቃጠለ። ትራምፕ “ድል- በድል ነው! ወደፊት!” አለ።

ትራምፕ በማግስቱ የሟቹን ወታደረ አስከሬን በክብር ለመቀበል አውሮጵላን ማረፊያ ወርዶ ነበር። የወታደሩ አባት ፕረዚዳንት ትራምፕን አልጨብጥም/ አላነጋግርም አለ። አድሮ ዉሎ ‘ምነው/’ ሲሉት አባትዬው “ለልጄ ባልተጠና፣ባልተረጋገጠ ነገር ልከው ያስገዱልብኝ እንማን እንደሆኑ የሚያጣራ አካል የቋቋምልኝ!” አለ።

ይህ ዜና ናኜ! ትላንትና “ዐለምሽ ዛሬ ነው ዛሬ…!” ብሎእንዳልፎከረ ሁሉ “ታዲያ እኔ ምን አውቃላለሁ!ይህንን ፕላን አዘጋጅቶ ትቶልኝ የሔደው ባራክ ኦባማ ነው!” ለ። በነጋታው ደግሞ ለወጥ አደርገው።“እኔ ምን ላድርግ? የስለላና(Intellegence0 የወታደር አለቃ ጀነራሎች ጥሩ ነ ው አሉኝ!ከሆነ ግፉበት!ቀጥሉበት! አልኩኝ!” አለ።

ትላንት ማታ ደግሞ ለአሜሪካ ምክር ቤት ያጋራ ስበሰባ ባደረገው ንግግር የሟቹን ሚስት እዚያ አስቀምጦ “ኦወን (ወታደሩ) ዘለዓለም ሲታሰብ የሚኖር የአሜሪካ ሰማእት ነው!” አለ።

እኔ የማውቀው “ባንድ ራስ ሁለት ምላስ!” ሲባልነው። ይህኛው “ከሁለት ምላስ”ም በላይ የሆነ መሰለኝ!ለቆጣሪ ሳያስቸግር ይቀራል!

ፕሬዚዳንት ሃሪይ ትሩማን(Harry Truman) ጠረጴዛ ላይ“The Buck Stops Here”

የሚል ምልክት ነበራቸው።”በኔ ፕሬዚዳንትነት ስር ለተሠራው ማንኛቸውም ተጠያቄ እኔ ብቻ ነኝ!” ለማለት ነው።

****

አንዴ የካቲት 1966 ጸደይ መጽሔት ላይ ወጥቶ የነበር የሽሙጥ ምስል (Cartoon)አስታወሰኝ። በክብ ጠረጴዛ ዙርያ የቆሙ ሰዎች ሁሉም ጣታቸውን የሚቀጥለው ሰው ላይ ሰትረው “እሱ ነው!” “እሱ ነው!” ይባባላሉ። ደርግ ያቋቋመው የመርማሪ ኮሚሽን የሚባል ነበርና የኃይለ ሥላሴ መንግስት ሚኒስተሮች ሲጠየቁ የሚሰጡትን መልስ መሠረት አድርጎ የተሠራ ምስል ነበር። ይባስ ብለው ጠቅላይ ሚኒስቴር የነበሩት አክሊሉ ሀብተውልድ “ጠቅላይ ሚኒስትሯ ልዕልት ተናኘ ወርቅ ኃይለስላሴ ናቸው” ብለው አረፉ። “ታዲያ የርስዎ ሥራ ምን ነበር?” ብለው የጠየቋቸው አለመስለኝም። ይህ ሁሉ በራዲዮን በተሌቪዥን ሲተላለፍለን ነበር።

ደግሞ አንድ ሌላ ነገር አስታወ ሰኝ። በ2001 ይመስለኛል ከምብሪጅ፣ ማሳቹሰትስ (Cambrige Massachussettes) እያለሁ ገነት አየለ የጻፈችውን “የመንግስቱ ኃይለማርያም ትዝታዎች” አነበብኩ። ገርመኝ! መንግስቱ የሚለው፤አሁን ትንሽ ትንሽ ትዝ እንደሚለኝ፤”ኢትዮጵያ ለደረሰው ችግር፤ ለመሸነፋችንም ተጠያቂዎቹ የጦሩ አዛዦች ናቸው”’ ነው። ገነትወዳጄና የደህንነት ሚኒስቴር የነበረውን ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደሥላሴንም አነጋግራው ነበረ። “መንግስቱ ያለው በወታደር ሥነሥርአት ነውርና ጽያፊ ነው። አዛዥ ያጠፋውን ወታደር ይቀጠል!። ሐላፊነቱ ግን ሙሉ ለሙሉ የሚወድቀው አዛዡ ትከሻ ላይ ነው!” አለ። “ The Buck Stops Here” ማለቱ ነበር።

ንዴቴን ለመወጣት ነው መሰለኝ አንድ በጣም ረዥም ደብዳቤ ለኮሎኔል ተስፋዬ ወልደሥላሴ ጻፍኩለት። እመቤት አስፋ ወስዳ ሰጠችው።ሀላፊነት ስለመቀበል የሰጠው አስተያይት አርክቶኝ ነው። “ሁለተኛ እንዳትጽፍልኝ! ለአንተ ጥሩ አይደለም!” የሚል መልስ ላከለኝ።

ያኔ ወህኒ ለነበሩ የደርግ አባላት፤ለፍቅሬ ሥላሴ ወግደረስ፤ለኮሎኔል ደባላ ዲነሳ፤ለሻለቃ ካሣዬ አራጋው እጽፍ ነበር። እስረኞች አይደሉ! እኔም እስረኛ ነበርኩ አይደል! “እናንተው ናችህና ያሰራችሁኝ የእጃችሁን አገኛችሁ!” አላልኩም። አልልም! ያ ጎሜ ነው ብዬ የማስብ ይመስለኛል።

ትራምፕ ከገባበት አጣቢቂኞች ሁለት ልጥቀስና ይብቃ መስለኝ።

አንደኛው ፤ የተለያየ የሕዝብ ክፍል በየግዛቶቹ ይስለፋል። የሚሉትና የዘው የሚወጡት መፈከር ታይቶም ተስምቶም አይታወቅም የሚሉት አይነት ነው። የሕዝብ መገናኛውን በአብዛኛው ጠላቴ፤የአሜሪካ ሕዝብ ጠላትም ነው ስለአሌለ መስለኝ እነሱም አጸፋ ምት በሚመስል መልኩ ይህንኑ ዜና ይናኙለታል።”የኔ ፕሬዚዳንት አይደለህም! You are not My Presiden! የሚለው ቋሚ ነው። በቀደም አንድ አንደበት ርቱእና ፍቱህ የሆነች ሴት ወይዘሮ “የህ አሜሪካ ነው! ራሽያ አይደለም!” ትልና” ነይት(Neyt)!” ትለዋለች። “ራሽያ አይደለም!” ለማለት በሩሲያ ቋንቋ መገለጽዋ ነው።

ሁለተኛው ፤ የአሜሪካ የመንደር ዲሞክራሲ ከሚገለጽበት መንገድ አንዱ የማዘጋጃ ቤትአዳራሽ ስበሰባ (Town Hall)የሚሉት ነው። የምክር ቤት አባላት በተለምዶ በእረፍታቸው ጊዜ ወደየተመርጡበት መንደር ሲሔዱ እዚያ ስበሰባ ይገኙን ምን ሲሰሩ እንደነበረ፣ምን ሊሰሩ እንደፈለጉ ያስረዳሉ። ሕዝቡም ጥያቄ፤አስተያየት ትችትም ያቀርባል።የኸው ሕዝብ ነውና ነገ መልሶ የሚመረጠው ተመራጮቹ በጥንቃቀ የሚያዳምጡት መደረክ ነው።

የዘንድሮው ለየት ያለ ነው። አንደኛ ተፈላጊዎቹና ተጠያቂዎቹ የትራምፕ ፓርቲ አባላት የሆኑት ሬፑብሊካኖቹ ነበሩር።አደራሹ ከአፉ እስከገደፉ ይሞላል። ሕዝቡ ጠያቂ እንጂ አደማጭ አልሆን አለ። “ለመሆኑ ከትራምፕ ጋር ያለህ ጉንኝነት ምን ድነው? አገራችንን አሳልፎ ሲስጥ አንተ ምን አልክ? ምን አደርክ? ምን ማድረግ አሰብክ? የጤና ዋስትናችንን(Obama Care) እደመስሳለህ ሲል አንተ ምን አልክ? ከሥልጣን እንዲወርድ (Impeachment)የምታደርገው ጥረት ምንድነው?” የሚለን የመሳሰለው ነበር።

የምክር ቤት አባሎቹ “እሽ የኸው የምትሉትን ሁሉ ማስታወሻ ይዣለሁ! ከጓደኞቼ ጋር እነወያይበታለን!” የሚል ነው። ብዙዎቹ “የመጣ ይምጣ! እንጅ እዚህ አዳራሽ ዝር አንልም” ብለው ቀሩ።

ለዚህ ሁሉ የትራምፕ መልስ ቀለል ያለች ነበረች። “ይህንን ሁሉ የሚያሳድምብኝና የሚያሰልፍብኝ ባራክ ኦባም ነው!” አለ።አውጣኝ! ከእውነት ለመሸሽ የሚደርግ ጥረት!

****

የዚህ የትራምፕና የሩሲያ ነገር እንደጠ.ብ.ጠ.ብ ተጀምሮ አሁን ጎርፍ ሆነ። ጎርፉ ማንንና ምን ይዞ እንደሚሔድ ገና በቅጡ አልተረጋጋጠም። የተረጋጠ ነገር ቢኖር በቋፍ ላይ ያሉት ቁጥር መብዛቱ ይመስለኛናል።

እስከ አሁን የብሔራዊ ጸጥታ አማካሪ የነበረውን ጀነራል ማይክል ፍልኒን(General Michel Flnn) ወስደታል።እጩዎች ቁጥራቸው ጠርቶ አለወጣም። ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ ጀፍ ሰሲዮን(Jef Sessions) በቋፍ ላይ ካሉት ውስጥ ይመስለኛል። የትራምፕ አማችና አማካሪ ሆኖ የተሾመው ያሬድ ኩሽነር(Jared Kushner) ከዚሁ ከጠቅላይ አቃቤ ሕጉ ጋር ሆኖ የሩሲያን አምባሳደር አነጋግሯል የሚል ትላትናና ዛሬ ወጥቷል። እጩ መንገደኛ መስለኝ።ልጁ ዶናልድ ትራምፕ ትንሹ(Donald Trumt Jr.) ባለፈው ወር መስለኝ ራሱያኖቹ ባዘጋጁት ስብሰባ ላይ ፈረንሳይ፣ፓሪስ $50,000 ተክፍሎት ተናጋሪ እንግዳ ነበር ተብሏል።

ይበልጥ የሚገርመው የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤ላቫሮቭ፤ የተነገረው ነው። “ይህ ሩሲያን ምክንያት አድርጎ ትራምፕ ላይ የሚደርገው ዘመቻ የፈጠራ ወሬና(fake News) ሰይጣናዊይ ዘመቻ (Witch Hunt)ነው አለ። ቃል በቃል ትራምፕ ያለውን ጠቅሶ ነው። “አንድ አካል አንድ አምሳል” መሆናቸውን በአደባባይ አረጋገጠ ማለት ነው።

“ነው አንዴም?” ያሰኛል። ላቫሮቭ ዲፕሎማት ነውና የዲፕሎማት ቋንቋ አንድምታስ ይኖረው ይሆን? አሜሪካ አሁን በተለይ በአለም አቀፍ ጉዳይ መንግስት የላትም እንደማለት ነው። በዚህ ክፍተት ሩሲያ በሶሪያም ሆነ ዩክርኒ ስራዋ “ሰከን በሉ” ብሉ የሚላት የላትም ማለት ነው። በዚህ መካከል “እኛና ትርምፕ አንድ አካል አንድ አምሳል” የሚል መግለጫ ሲሰጥ “ይኸውና ራስዋ ሩሲያ መስከረች!” በሚል የአሜሪካ መንግስትና ሕዝብ የበለጠ ሲወዛገብ ጊዘ ይወስዳል ማለት ነው። በዚህ ጊዜ ሩሲያ “ሰከን” ሳይሆን “ፋታ” አገኝታ የፈለገችውን ተሰራለች ማለት ነው። እንዲህ አድርጎ መመልከትም ክፋት የለውም ለማለትነው!

በዚህ መካከል ብሩክ ኦባማና ሚሸል “አለምህ/ሽ ዛሬን ዛሬ!” ውስጥ ያሉ ይመስላል። ባለፈው ሳምንት ገና ላልተጻፈው መጽሐፋቸው ታይቶና ተስምቶ በማያውቅ ዋጋ ያውም በጨረታ ሸጠውታል። በዚህ ወር Former president Barack Obama will be the 2017 recipient of the Profile in Courage Award,. የሚለውን ሊሸለም ነው። ፈርንሳይ በሚደርገው የፕሬዚደንት ምርጫ ፓሪስ መንገድና ሌላም ቦታ “ናና ፕሬረዚደንታችን ሁን!” የሚል መፈክር ያያዙና የኦቦምና ምስል ጭምብል(Mask) ያጠለቁ ይዘምራሉ ። ከተሰስላፊዎቹ አንዷ “አዎን ይቻላል! Yes We Can!” ነ የሚለውን መፈክር አንግባለች።

ነገር አለሙ አይገርምም! በእንግሊዝና በሌሎችም አገሮች “ዶናል ትርምፕ የሚባል ሰው እዚች አገር ድርሽ አይላትም!” የሚል ፊርማ ያሰባስባሉ። ኦባማን ደግሞ እዚያው አውሮጳ ናና ፕሬዚዳንችን ሁን ይላሉ። በአደባባይ !ወይ ስምንተኛው ሽ!

****

አገር ቤት

ከአንድ ወዳጄ ጋር በስልክ ስንነጋግር” ኢያሱ አለማየሁ ቃለመጥይቅ አድርጓልና አድምጠው” አለኝ። “ለምን?”” ብቻ አድምጠው!” አለኝ። ስለ እያሱ አለማየሁ የማውቀውን ያክል ነገርኩት። አንዴ ኢትዮጵ መጽሔት ላይ እንዳልሸጥ እንዳልለውጥ አድርጎ ዘልፎኛል። እያሱ ላይ ደርሸበት ሳይሆን የዘሩ ክሸንን ዜና እርፍት ምክንያት አድርጌ በጻፍኩት ምክንያት ነው። “የውሻን ጥርስ ማየት አጥንት ሲገጥ ነው!” እንደሚባለው መሆኑ መስለኝ።” ወንጄል” ብሎ ያቀረበብኝ ክስ ደግሞ” ይህ አሰፋ ጫቦየሚባል ሰው በሚጽፈው ሁሉ ሰውን ወይ “ወዳጄ” ወይ “ጓደኛዬ” ይላል” የሚል ነበር። “ወይ ጉድ!” ብዬ አለፍኩት።

አሁን አድምጠው ስለኝ አደመጥኩት። እድሜ ገፋ ሲል “ለንስሐ ሞት አብቃኝ!” ብሎ መናዘዙ ይሆናል ብዬ ተሰፋ አድርጌ ነበር። የኢሕአፓ መሪዎች ከነበሩት የቀሩ ሁለት፤እያሱና ክፍሉታደስ ናቸው። ወንድምዬው ሳሙኤል አለማየሁ ያው ሳይናዘዝ ሞተ።

ተስፋ ያደርኩት:-

እንዴትና በነማንን በኩል ተቀነባብሮ በሻአቢያ መሪነት የኢትዮጵያን አየር መንገድ አውሮጵላን ጠልፎ ሱዳን አንደገባ!ፍሉ ታደሰ “ያ ትውልድ” በሚለው መጽሐፍ አምስቱንም የኢትዮጵያ አየርመንገድ አውሮፕላን ጠለፋ የተቀነባበረውና የተመረው በሻአቢያ ነው ብሏልና።
እንዴትና ማን፤በማን በኩል አግናኝቷቸው ኢትዮጵያን ለማጠፋት እስከ አፍንጫው ከታጠቀው ከሶማሊያ ፕሬዚዳንት ከነበረው ከሲአድ ባሬ ጋር እንደትተዋዋሉ! ያው Wikileak ባወጣው የሚስጠር ሰነድ ውስጥ የኸው የኢሕአፓና የሲአድባሬ ነገር በዝረዝር ተቀምጧልና።
ከወያኔ ጋር አብሮ ለመስራት አምስት ጊዜ ድርድር ተቀምጠው ድርድሩን አልቀበልም ያለው ወያኔ ነበር። ክፍሉ ታደስ ይህንኑ “ያ ትውልድ” መጽሐፍ ውስጥ ገልጦታል። ምን ነበር የድርድሩ ጭብጥ? ይህንንም ያነገረናል የሚል ተስፋ ነበረኝ።
ትላንት መሬት ላራሹ ስትሉ የነበረችህ፤ወይም የምትሉ የመሰላችሁቱ፤ እንዴት የገጠር መሬት አዋጅ የተወውጀ ለታ፤የካቲት25,1966 የሻቢያ መሳሪያ ታጥቀው ፤በሻአቢያ መንገድ መሪነት ኢትዮጵያን ለመውጋት አሲምባ ኣሸምቀው እንደነበረ።
ዛሬ ሥልጣን ላይ የለው የወያኔ መንግስት፤ኢ ሕ አ ደግ ተብሎ የሚጠራው የኢሕ አፓም ጥምረት መንግስት ነው። ታምራት ላይኔ ፣ማለትም ኢሕአፓ ነበር የመጀመሪያው ጠቅላይ ሚኒስቴር!ይህንን፣ደርግን አዳክሞ፣ኤርትራ እንድተገነጠል ማድረግ ባቻ ሳይሆን ወያኔ ለምንሊክ ግቢ እንደበቃ ማድረጋቸውን ያስረዳ ይሆናል የሚልና የመሳሰለውተስፋ ነበረኝ።
ሌላው ክፍሉ ታደስ በዚያው መጽሐፍ ውስጥ፤እያሱ አለማየሁና ሳሙኤል አለማየህ የፓርቲውን ገነዘብ እንዳለ ዘርፈው፤የሚበተነውን ወጣት እዚያው ጣጥለው ፈረጠጡ ነው ያለው። ሌቦች ናቸው! ማለቱነው።ያዚያንም መልስ አልሰጠም።
ከሁሉ የሚገረመኝ ኢሕአፓ ዛሬም እንዳለ፤ነፍስ ያለው ድርጀት አድርጎ ነው የሚያወጋው። አለቅየው ክፍሉ ታደሰ ኢሕ አፓ የሚባል ድርጀት ከ30 አመት በፊት እንደተቀበረ እዚያ መጽሐፉ ላይ ገልጿል።
በነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎችና እዚህ ባልተነሱ ዙሪያ ዞርም አላለባቸውም።አገር፤ቀይ ሽበር፣ ነጭ ሽበርና ሌላም ስም ተሰጥቶ የተፈጁ ቤተሰብና ዘመድ አዝማድ ማውቅ የሚፈልገው ይህንን ነው።እያሱ አለማየህ ደግሞ ለዚህ ሁሉ ዋና ከሚሆኑት ምንጮቹ አንዱ ነው።ዞርም አላለበትም! “የሞኝ ለቅሶ መልሶ መልሶ!” እንዲሉ እዚያው የዛሬ 50 አመት በፊት የነበረ ተረት- ተረት አይነት ነገር ሊያድስ ፍለጋ ሆነበኝ። ቀልቡን ሰልበው ለመጥፊያችን መሣሪያ ያደርጉትን የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ሊዘክርልንይፈልጋል።

ብቻ ሰውዬው ምኑን አዳምጠው እንዳለኝ አልጋባኝም። ተዝካርና ወይም ኑዛዜ አለመሆኑን ሳየው ግን ገርሞኛል። ጅብኮ “ቁርበት አንጥፉልኝ!” የሚለው የማያውቁት አገርሔዶነው።”አሟሟቴን አሳምርልኝ!” የሚለውን ያልሰማን ወይ ያላጤነው ብዙ ሰዎች አለን ማለት ይሆን?

ክፍሉ ታደሰና እያሱ አለማየሁ የጸጋዬ ገብረመድኅንን “እንዳይነግርህ አንዳች እውነት” ግጥም ያሰታውሰኛል።እነሆ የግጥሙ መጨርሻው ሶስት መስመር:-

ኡ ኡ ታ ህ መንኮራኩርክን እስኪያሰመጠው አጓራበት፤

ጭንቅላትክን ግዘፍበት፤ውቀጥበት፤ውገርበት፤

ዝግ ብሎ ያሰበ እንደህ ይነግርሐል አንዳች እውነት።

*****

ከሁለት ወር በፊት ጀምሮ ይሆናል፤ሲያከራከር፤ሲያጨቃቅ ወይም ሲያዘላልለፍ የሰነበተው ዶክተር ፍቅሬ ቶሎሳ የጻፈው“የኦሮሞ እና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ”የሚለው መጽሐፍ ነበር። ዶከተር ጌታቸው ኃይሌ የሰጠውን ግምገማ አነበብኩ።የሚቀጥለውን የተሰትዋለና በማስረጃ የተደገፈ ድጋፍ ወይም ነቀፋ እጠብቅ ነንበር።የመከባበርና የጨዋነት ግድቡ ፍርሶ የመዘላልፍ ጎርፍ ወረደ።መጽሐፉም ነበረኝ። መዘላለፉንም ጥቂት አነበብኩ። ከዚያ መዘላለፉንም መጽሐፉንም ማንበብ አቆምኩ። እኔ የስሜቴ ጠባቂ ነኝና አለአግባብ እንዲነካብኝ አልፈልግም።

የዚህ መዘላለፍ ምንጩ፤ወይም ከምንጮቹ አንዱ መሪራስ አማን በላይ “አገኝተዋል” የተባለው ታሪካዊ ሠነድ ነው።መሪራስ የሚል የቤተክህነት የማዕረግ ስም ከዚህ በፊት አለሰማሁም።

“መሪራስ ሰጡ” የሚል መልስ በዶክተር ፍቅሬ በኩል ተለጥፎ ነው መስለኝ ድረገጽ ላይ አነበኩ።ደነገጥኩ። መሪራስነታቸው የቤተክህነት ሰው ያደርጋቸዋልና ነው የደነገጥኩት። ወንጌሉ ውስጥ “ቀኝህን ቢመታህ ግራህን ስጥ!” የሚል ሁሉ አለበት። መልሳቸው ያንን መለኪያ የሰማ አልመስለኝም።

ሰሞኑን ከአንድ ወዳጄ ጋር በስልክ ስናወራ መሪራስ አማን በላይ አረፉ አለኝ። ሎሰ አንጀለስ፤ ካሊፎርኒያ ነው። ታዋቂ ናቸው ብዬ ስለገመትኩ ታውቃቸዋለህ ስለው ብዙ ሰው የሚያውቃቸው አይደሉም። ትላንት ቤተክርስቲያን ነው የተገረን አለኝ።

መሪራስ አማን ሎሰ አንጀለስ ሲኖሩ ከአገሩም ማለትም እዚያ ከሚኖረው ኢትዮጵያውያንም ሆነ ከቤተክርስቲያናቱ ጋር የቀረበ ግንኙነት የነበራቸውም አይመስልም። የሚያውቃቸው ሰው ቢኖር ጥቂት ሊሆን ነው።

መሪራስ የዚህ የጦፍ ክርክር ልበለው ውዝግብ አካልና አምሳል ነበሩ።”አገኘሁ!” ስለአሉት “ታሪካዊ ሠነድ” ጉዳይ በሰጡት መልስ ላይ የሰጡት ጥርት ያለ መልስ የነበር አይመስለኝም። አሁን ደግሞ መልስ ሊጠየቁ የማይችሉበት ተጉዘዋል።አንግዲህ “መሪራስ ምን አሉ? ምን አላሉ?” የሚለውን ከዶከተር ፍቅሬ ቶሎሳ ልንሰማ ነው ማለት ነው። አደባባይ ያወጣቸው ፍቅሬ ነውና።

****

ስለ አገር ቤት ሌላ የሚያዝናና፣የሚገርም፣ የማይታመንም የሚያሳፍርም የሚመስልየያነበብኩት ስለ አለቃ ጸጋዬ በርሄ ነው። “ጎልጉል” የሚባል ጋዜጣ መጽሔት ጎልጉሎ ያወጣው ነበር። እንዲህ ብሏል:-

አለቃ ጸጋዬ በርሄ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ባይጀምርም ዛሬ ላይ በቢዝነስ አድሚስትሬሽን (MBA) የሁለተኛ ዲግሪ “ባለቤት” ነዉ፡፡ ጸጋዬ በርሄ ከትምህርት አኳያ ልክ እንደ ነጭ ወረቀት ንጹህ ነዉ፡፡ ከሴራ ፖለቲካ አኳያ ግን የሚናቅ ሰዉ አይደለም፡፡ እዚህ ላይ መዘንጋት የሌለበት ጉዳይ አለቃ ጸጋዬ በርሄ የሽማግሌዉ ስብሃት ነጋ ዋርሳ መሆኑ ነዉ፡፡ የስብሃት ነጋ እህት ቅዱሳን ነጋን አግብቷል፡፡ ተንኮሉም ቢሆን ከአምቻ ጋብቻ ዉህድ የተገኘ ይመስላል፡፡

ካለ በኋላ ስለእንግሊዚኛ ቋንቋ እውቀቱ መለስ ዜናው ብሏል የተባለውን ጎልጉል እንዲህ ያቀርብልናል

ድንቁርናዉም እንደዛዉ፡፡ ጸጋዬ ላይ የተቀለዱ ቀልዶች ግነት ቢታይባቸዉም ከእዉነታዉ ብዙ የራቁ ግን አይደሉም፡፡ ለአብነት አለቃ ጸጋዬ በርሄ የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት እያለ ዮሃንስ ቤተመንግስት ዉስጥ መለስ በሚመራዉ ስብስባ ላይ ጣልቃ እየገባ ሲያስቸግር መለስ በቁጣ ስሜት “አለቃ ጸጋዬ የስብሰባዉን ህግ ታከብር እንደሆነ አክብር ካልሆነ ግን ይሄን ስብሰባ በእንግሊዝኛ ነዉ የማደርገዉ” ብሎ አሸማቀቀዉ እየተባለ የሚወራዉ ቀልድ የሰዉዬዉን ነጭ ወረቀትነት ለማመላከት ነዉ፡፡

ይህንን Facebook ላይ ለጠፍኩት።ይህ በሆነ በስንተኛው ቀን አለቃ ጸጋዬ በርሄ አምባሳደር ሆነው የተሾሙበተ አገር፤እስራኤል ፤ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ። በእንግሊዚኛ ነበር የተናገረው ። “ንግሥስት ሳባ የአኩሱም ንጉስ ነበረ አለ። ይህንንም ከነምስሉ Facebook ላይ ለጠፍኩት፡፡ ይህ የእንግሊዚኛ ጥያቄአይመስለኝ።ብቻ አይመስለኝም! የጤንነትም፤የእውቀትም፤ያለበትን የኃላፊነት ደርጃ አለመረዳትም ይሆን ?አልኩኝ። በአለቃ ጸጋየ ምክንያት መልሰ ዜናው ብሏል የሚል ጎልጉል ጽፎ ነበር።መለስ ምን ያክል ልክ ነበር የሚያሰኝ ይሆን?

የሚያስፍር ያሰኘኝ ይህ ሁሉ የሚደረገው በሀገራችን በኢትዮጵያ ስም መሆኑ ነው። የኢትዮጵያ አምባሳደር ነውና! የተናገረው በኢትዮጵያስም ነውና!

የተሻለ ሣምንት ይጠብቀን!

Filed in: Amharic