>
5:13 pm - Monday April 19, 2438

የአቦይ ስብሃት ነጋ የሙስና ወጎች [ክንፉ አሰፋ]

sibhat-negaበአሜሪካ ሃገር፤ አንድ ባለስልጣን በሙስና ሲባልግ እስር ቤት ይገባል።  በፊሊፒንስ ሃገር አንድ ባልስልጣን የሙስና ወንጀል ቢፈጽም አሜሪካ ይገባል።  የኛ ሃገር ባለግዜ ግን ሙስና ሲሰራ አሜሪካ እየተመላለሰ ይነግዳል። ለግዜው ልዩነቱ የዚህን ያህል ነው። ገለልተኛ የፍትህ አካል  ባለበት ሃገር፤  ሙስና አፍ አውጥቶ አይናገርም፣  እግር አውጥቶም አይራመድም።

አዲሱ ቀልድ፤  “ሙስና አለ፣ ማስረጃ የለም!”

በያዝነው “ጥልቅ ተሃድሶ” ዘመን ሙስና ለሁለት ተከፍሎ እንዲታይ ተደርጓል። ማስረጃ ያለው ዘረፋ እና ማስረጃ የሌለው ዘረፋ። ልክ እንደ ግብር አከፋፈል። ግብር ከፋይ “ሀ” እና ግብር ከፋይ “ለ”። ምድቡ በዘረፋው መጠን እና በባለስልጣኑ ጉልበት ይወሰናል።  የዘረፋው መጠን ከአስር ሺህ በር በታች ከሆነ እና ዘራፊው የድል አጥቢያ ታጋይ ከሆነ ማስረጃ ያለው፣  ሙስና ምድብ “ሀ” ይሆናል። መጠኑ ከአስር ሚሊዮን በላይ ከሆነ ደግሞ ሙስና ምድብ “ለ” ተብሏል።  ይህ አይነኬው ምድብ  “ማስራጃ የሌለው ዘረፋ” መሆኑ ነው።  አቅመ-ቢሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በብሄራዊ ቴሌቪዥን ቀርበው የነገሩን ከዚህ እውነታ የተለየ አልነበረም። የህወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፣ የፖሊት ቢሮ እና ምክትል ሚኒስትሮች ከአይነኬዎቹ ጎራ ይመደባሉ። የ4 ሺ ብር ደሞዝተኛ፤  ጀነራል የ10 ሚሊየን ብር ቪላ አሰርቶ ሲያከራይ በግላጭ እየታየ፣ “ማስረጃ የለም” ብሎ ማለፍ የሚያሳምን አይሆንም።  የእያንዳንዱ ዘረፋ ማስረጃ፤ እዚያው አፍንጫቸው ላይ ነው ያለው። ግና የሚወሰነው በባለስልጣኑ ጉልበት መጠን ነው።  ምድብ “ለ”ዎችን ለመድፈር መሞከር ራሱ በሙስና ያስቀፈድዳል።  ጸረ-ሙስና የሚባለውም ድርጀት የተፈጠረው ለእነሱ እና በእነሱው በመሆኑ የሚበየነውም የተገመደለ ፍርድ ነው።

ከ83 ሚሊዮን ብር በላይ የዘረፉትን ባለስልጣን ያጋለጡት አቶ ተስፋዬ ኢሬሣ፤  እስካሁን በተሰወሩ ባለ ግዜዎች ተገድለዋል። አቶ ተስፋዬ ከመገደላቸው በፊት ለጸረ-ሙስና  ኮሚሽን የምስክርነት ቃላቸውን ለመስጠት ከኮሚሽነሩ አሊ ሱሌማን ጋር ቀጠሮ ይዘው ነበር።ገዳዮቹ እኝህን ባለ ሃቅ፣ አሊ ሱሌማን ጋር እንኳን እንዲነጋገሩ እድል አልሰጧቸውም።  የምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁም፣ በመንበረ ፓትሪያርክ ቅድስት ማርያም ገዳም ላይ የነበረውን  የገንዘብና የንብረት ሙስና  የሚያጋልጥ ዜና በመስራቱ  በከባድ የስም ማጥፋት ተወንጅሎ እስር ቤት ተወርውሯል።…  አያሌ ጌታቸው ወርቁዎች፣ ብዙ ሳይታወቁ የተገደሉ ተስፋዬዎች አሉ።

ስር የሰደደው የህወሃት ሙስና፣ ዛሬ  ከዜጎች ንብረት እና ከመሬት ዝርፍያ አልፎ በቤተ-ጸሎት ውስጥም ዘው ብሎ ገብቷል።   ከሚጓዝበት ከፍተኛ ፍጥነት አንጻር በዓአብያተ-ክርስትያናት  እየተስፋፋ መሄዱ ብዙ አያስደንቅም።  “ኃይለኛ” የሚል ስያሜ የተሰጠው የቁሉቢ ገብርኤል ዘረፋ እንደ ምሳሌ የሚጠቀስ ነው።   ከመዕመናን በተደጋጋሚ የቀረበው የ30 ሚሊዮን የሙስና አቤቱታ ተለባብሶ እንዲያልፍ  የጸረ-ሙስናው ቢሮ ትልቁን ስራ  ሚና ተጫውቷል።

ለፖለቲካው ትኩሳት ማባረጃ ሰሞኑን የተሞከረው የሃይለማርያም ደሳለኝ የሙስና ተረት-ተረት ምላሹ ዝምታ መሆኑም፤  ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዝም ብለው ጉንጭ አልፋ ቃላት እንዳባከኑ መገመት አያድግትም ።  በዝምታ ውስጥ ያለው ጩሀት ግን ሳያስፈራ አልቀረም። እየተካሄደ ስላለው ነገር ሁሉ ብቸኛው  መንገድ ዝምታ ነውና ያስፈራል። ጸጥ ባለ በዚህ ባህር ውስጥ ትናንሽ እና ትላልቅ አሳዎች እንደልባቸው ይዋኛሉ።

የቀድሞ የህወሃት አመራር አባል የነበሩት አቶ ገብሩ አሥራት “ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ” በሚለው መፅሐፋቸው ስለ ሙስናው ሲጠቅሱ፤ “…መርማሪ አቋቁመን ሥር ሰዷል የተባለውን ሙስና ስንመረምር የት እንደገባ የማይታወቅ 5 ሚሊዮን ብር ተገኘ።  ለዝርፍያው ተጠያቂዎቹም ግርማይ ካህሳይ የሚባል ሒሳብ ሰራተኛ እና ተክለ ወይኒ ነበሩ። …ይህ በሆነ ግዜ ተክለ ወይኒ ተነስቶ ‘ይህ ኮራፕሽን እያላችሁ የምታደርጉት ምርመራ ትክክል አይደለም፤ የተከሰተው ችግር የአሰራር ግድፈት እንጂ ሙስና አይደለም፤ እያንዳንዱ የህወሀት አመራር አባል ቢፈተሽ ተመሳሳይ ግድፈት ሊገኝበት ይችላል። …ዓባይ ፀሐዬ ደግሞ ከሁሉም የባሰ ሙሰኛ እንጂ ሙስናን ሊታገል የሚችል ሰው አይደለም’”  ማለቱን ጠቅሰዋል።

በኢሃዲግኛ ቋንቋ የሚሊዮኖች ዘረፋ፤ ሲተረጎም የአስተዳደር ብልሹነት ሳይሆን ይልቁንም አነስተኛ የአሰራር ጉድፈት ነው።  ይህንን ጥቂት ጉድፈት ደግሞ የማይሰራው የህወሃት ሰው የለም ነው እያሉን ያሉት። ለዚህ “ከገለባ የቀለለ” ጥፋት ታዲያ ከሳሽም፣ ተከሳሽም ሆነ ዳኛው አንድ አካል ነው።

ታላቁ መጽሃፍ እንዲህ ይለናል፤

“…ጻፎችና ፈሪሳውያንም በምንዝር የተያዘችን ሴት ወደ እርሱ አመጡ። በመካከልም እርሱዋን አቁመው።  ‘መምህር ሆይ፥ ይህች ሴት ስታመነዝር ተገኝታ ተያዘች። ሙሴም እንደነዚህ ያሉት እንዲወገሩ በሕግ አዘዘን፤ አንተስ ስለ እርስዋ ምን ትላለህ?’  አሉት። …. መላልሰው በጠየቁት ጊዜ ግን ቀና ብሎ። ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ በድንጋይ ይውገራት አላቸው።”

እነሆ አቦይ ስብሃት ነጋ ስለ ሙስና ይነግሩናል። ደጋግመው ይነግሩናል። ሙሰኞች መጥፋት አለባቸውም ይሉናል። ሙሴ በአዖሪት እንዳዘዘው ሁሉ ‘ታላቁ መሪ’ ስኳር ያሉትን የኪራይ ሰብሳቢነት ቫይረስ ለማጥፋት – የሌባው እጅ ይቆረጥ በለዋል።  ትእዛዙ ተፈጻሚ አይሆንም እንጂ፣ ቢሆንማ ኖሮ የመጀመርያዋ ሰለባ  “ቀዳሚዋ እምቤት” ነበሩ።  ፉከራው ካንገት በላይ በይሆን ኖሮ የሁሉም ህወሃት ሰዎቸ እጅ  ዱሽ በሆነ ነበር።

ታዲያ ከሃጥያቱ ያልጸዳ ከየት ተገኝቶ የመጀመርያ ድንጋዩን ይወርውር?

“ዝምታ ወርቅ ነው”  እንዲሉ አቦይ ስብሃት ከአንገት በላይ ከሚቀባጥሩ ይልቅ እንደው ዝም ቢሉ ያምርባቸዋል።

የአቶ ስብሀት ነጋ ልጅ ተከስተ ስብሀት ነጋ፤  ግዙፉን የጎተራ አደባባይ ለአምሰት አመት ኮንትራት በ600 ሺህ ብር እንደወሰደው ፎርቹን ጋዜጣ ይፋ አድርጎታል።  የ’አክሊል ክሬቲቭ ኤጄንሲ’ ባለቤት የሆነው ተከስተ ስብሀት ነጋ፤ በአካባቢው ያለን  4000 ስኩዌር ኪሎ ሜትር፣ በቢሊየኖች የሚገመት መሬት እንደ ስጦታ ነው የወሰደው።  ልጃቸው X-5  (አሁን ኤክስ አሙሽተ ተብሏል) ለወዳጆቹ በስሶጣ  እያበረከተ፣ አባቱ ሙሰኞችን እናጥፋ ሲሉ ይቀልዱብናል።  “አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ!…”

አቦይ ስብሃት ነጋ ደርሶ፣ አይኑን በጨው አጥቦ ኢትዮጵያ እንዴት በሙስና እንደምትፈራርስ ጋዜጣዊ መግለጫም ይሰጣል። ከጥፋቱ ድፍረቱ።  የዚህን አዛውንት የሙስና መረብ ያጋለጠ አንድ ጥናታዊ ጽህፍ ስለ ስብሃት ነጋ ዘረፋ ሌላም የሚነግረን ነገር አለ። ህልቆ መሳፍርት ከሆኑት ዘረፋዎች ጥቂቶቹን ብቻ ለመጥቀስ፤

አድማስ ዩኒቨርስቲ ኮለጅ ባለቤት አቶ ይብራህ፣ የአቶ ስብሃት የአክስት ልጅ ነው። ይህ ሰው ያለ አንድ መነሻ ካፒታል በአዲስ አበባ በሁለት ቦታዎች አድማስ በሚል 16 ካምፓሶች ያሉት ኮሌጅ ከፍቷል።   ኮ/ል በላይ ነጋ ደግሞ የአቶ ስብሃት ወንድም ናቸው ። እኝህ ሰው ከወንድማቸው ባገኙት የህዝብ ገንዘብ በአዲስ አበባ፣ በመቀሌ እና በዓድዋ የዘመናዊ ፎቅ ባለቤት ለመሆን በቅተዋል። ከዜሮ ተነስተው በብርሃን ፍጥነት የመጠቁት የኮ/ል በላይ ነጋ ሃብት በዚህ አያበቃም። በጋምቤላም የሰፊ እርሻ ቦታ “ኢንቨስተር” በመሆን የሜካናይዝድ ግብርና ኩባንያ ባለሃብት ሆነዋል።  እኚህ ቢሊዮነር በቃሊቲም ግዙፍ ኩባንያ ገንብተው ነበር። ግን ምን ያደርጋል ዘረፋውን ገና ሳያጣትሙት ሞት ነጠቃቸው። ነብስ ይማር! አቶ በላይ ነጋ ሲሞቱ፣ ወይዘሮ ቅዱሳን ነጋ ሃብቱን በውርስ ተረክባዋለች። … እንዲህ እያልን ስንዘረዝር ብንወል የዘረፋው ተሳታፊዎች ቁጥር አንድ መጽሃፍ ይሞላል።

ድንቅ ነው። «ኢህአዴግ ሙሰኞችን ካልከሰሰ አገሪቷ ወደ ብተና ማምራቷ አይቀርም!» ይላሉ  ስብሃት ነጋ ምንም ሳይሳቀቁ። በልባቸው ግን እየሳቁ!  እኚህ ሰው ስለ ሙስና አስከፊነት የመናገሩን ሞራል ከየት እንዳመጡት እንጃ።  ያንን ሁሉ ጉድ በአናታቸው ላይ ተሸክመው እንደው ዝም ቢሉስ ምን አለበት? አበው እንዲህ ይመክራሉ “የምታወጣቸው ቃላት ከዝምታ የተሻሉ መሆናቸውን ስታውቅ ብቻ ተናገር።” አቶ ስብሀት ነጋ በአንድ ወቅት፤ “በኢትዮጵያ  በተጨባጭ ያለው ሙስናን  ለማጥፋት ፍላጎት እንጂ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ብሎ ነገር የለም።”ብለውም ነበር።  ይህ  አባባል ግምሽ እውነታ አለው። በእርግጥ ፍላጎቱም ቁርጠኝነቱም ቢኖር ኖሮ አቦይ ስብሃት ከአይቴ ነጋ ገብረ-እግዚአብሔር ጋር መኖርያቸው በከርቸሌ ይሆን ነበር ።  አንዳንዴ ጸረ-ሙስና የሚሉት ድርጅታቸውን አፈንጋጮችን (ትናንሽ አሳዎችን) ለመምቻ ይጠቀሙበታል።

“ዶክተር” አቦይ ስብሃት አድባባይ እየወጡ በተናገሩ ቁጥር ፣ በሳቸው ሳምባ የሚተነፍሱት ሃይለማርያም ደሳለኝም በ “አይቅርብኝ” አፋቸውን ሞልተው ስለሙስና  ይናገራሉ።

እርግጥ ነው። የመንግስታዊ ሌብነቱ ደረጃ ጥግ ላይ ደርሷል። እየዘረፉ ደግሞ ህዝብን ባይገድሉ ምን ነበረበት?  ከዘረፋው የከፋ ሌላ ትልቅ ወንጀል አለ። ከህዝቡ ህሊና ከቶውንም ሊጠፋ የማይችል ወንጀል።  በቀን እስከ አምስት መቶ ህዝብ የሚገደልበት ወንጀል። በመቶ ሺህ የሚጠጉ ዜጎች በፈረቃ የሚታሰሩበት እና የሚሰቃዩበት ወንጀል።  ዘርፈውም፣ ገድለውም፣ አስረውም መዝለቅ እንደሚችሉ የተማመኑ ይመስላል። ግን ለውጥ የተፈጥሮ ህግ ነውና መምጣቱ አይቀሬ ነው።  የግዜ ጉዳይ እንጂ ከፍትህ አያመልጡም።

ግዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል ነውና፣  ግዜው ደርሶ እስኪወድቁ ድረስ እነሆ በ”ማስረጃ የለም!” ዘፈን ይጨፍራሉ።

Filed in: Amharic