>

ከፍተን ብናየው? ሻአቢያና ኦነግ መስተፋቅር! [አስፋ ጫቦ Dallas Texas USA]

እንደመግቢያ
Ato Assefa Chaboዛሬ ትንሽ መጻፍ የፈለኩት በኦሮሞ ነፃነት ግንባርና (ኦነግ) በኢሳይያስ አፈወርቂ መካከል ያለውን የቆየ ጥብቅ ትስስር በመጠኑ ለመፈተሽ ነው። መነሻ የሆነኝ እንግሊዝ አገር ሎንዶንና አሜሪካ፤ አትላንታ፣ ጆርጂያ የኦሮሞ “ምሁራንና ብሔርተኞች” ያደርጉት ስብሰባና የሰጡት መግለጫ ነው። ያ ራሱን ችሎ መነገር ያለበት ስለሚመስለኝ እመለስበታለሁ። የዚህኛው አላማ እዚያ ሰበሰባ ላይ ተካፋይ ከነበሩት “ነፃ አውጭዎች” አንዱን ኦነግን በጨረፍታ ለመታዘብ ነው።
እዚያ ከመዝለቄ በፊት ኢሳይያስ አፈወርቂን ለመግባቢያ ያክል በመጠኑ መዳሰስ፤ ማየትና ማሳየት እሞክራለህ::

ብዙ የአፍሪቃ መሪዎች (ፕሬዝዳንቶች) “የእድሜ ልክ ፕሬዚዳንት” (President for Life) የሚል ማእረግ ነበራቸው። እኔ ወድጅዋለሁ! በየአራት ወይ ስድስት ዓመቱ ምርጫ እየተባለ ጊዜም ገንዘብም ከሚባክን “ወደዳችህ ጠላችሁ የራሳችህ ጉዳይ” ብሎ እቅጩን መናገርን የመሰለ ነገር የለም። ከዚያ ውስጥ አንዱ፤ ጂን ቤዴል ቦካሳ (Jean-Bédel Bokassa)፤ የመካከለኛ አፍሪቃ ሬፐብሊክ “ንጉሠ ነገሥስት! (Emperor) ሆኖ አረፈው። እሱም እውነቱን መናገሩ ነበር። አንድምታውን ወዲያ ትተን “የእድሜ ልክ ፕሬዚዳንትም ማለት ያው ንጉሠ ነገሥት ማለት አይደል!?” ማለቱ መሰለኝ።
ይህ ነገር የኛው የነበረውን ፣ አሁን የጎሮቤት “አገር” “ፕሬዚዳንት” የሆነውን ኢሳይያስ አፈወርቂን አስታወሰኝ። “የኛው የነበረውን” ያሰኘኝ የደሴ ልጅ መሆኑ፤ የቀደማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ ተማሪ የነበረ መሆኑ፤ ከሁሉም በላይ ጣሊያን ኤርትራ ብሎ የሰየማት የባህረ ነጋሽ ልጅ መሆኑ ነው። የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ተረት፣ ትንግርት (Mythology) ተብሎ የሚነገረው አብዛኛው የተሸመነው ባሕረ ነጋሽ ነውና። የዚህ፣ ጣሊያን ኢትዮጵያን የወረራት ዘመን፣ 1928 ዓም፣ የተመሠረተው የ“ጥቁር አንበሳ” ጦር ጠቅላይ አዛዥ ሌታና ኮሎኔል በላይ ኃይሌለአብም ኤርትራዊ ነበር። የጥቁር አንበሳ ሕገመንግሥት አንቀጽ አንድ “ሕዝበ ኢትዮጵያ ንሰአ ወልታ ወኩናት ወተንስእ ውስተ ረደትየ“ ይላል። የአቶ ታደሰ ሜጫን “ጥቁር

Page 2 of 11
አንበሳ” መጽሐፍ ያነቧል። የአቶ ሐዲስ አለማየሁን ትዝታ ማንበበም ስለሌታና ኮሎኔል በላይ ኃይሌለአብም ያለንን የበለጠ ያጠነክረዋል:: የትዝታ ፈለግ በሚለው መጽሐፌ ውስጥ በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስቴር ለነበረው መለስ ዜናዊ የጻፍኩትን ግልጽ ደብዳቤ ማንበቡም የተሻለ የሚያብራራው ይመስለኛል። (ይኸ እግረ መንገዴን መጽሐፍ ማሻሻጤ ይሆን?) አባቱ፣ አቶ አፈውርቂም የመቀሌ ማዘጋጃ ቤት ሠራተኛ አልነበሩም? በልጃቸው ምክንያት ተጠርጥረው ታስረው ኖሮ፤ ”አባት በልጁ ምክንያት አይተሰርም!” ብሎ፣ ለመንግሥቱ ኃይለ ማርያም ነግሮ ያስፈታው የደኅንነት ሚኒስቴር የነበረው ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደ ሥላሴ አልነበረም? የግንኙነታችንን ጥልቀት ለማስታወስ ያክል ነው። ያ ጥልቀት የማታ-ማታ አጓጉል ሆኖ አረፈ ለማለትም ነው!
ኢሳይያስ አፈወርቂን ያክል ለረዥም ዘመናት ንጉሰ ነገስት ሁኖ የቆየ መሪ አፍሪቃ ውስጥ አሁን ያለ አይመስለኝም። ኃይለ ሥላሴ ነበሩ። እሳቸውም ባልጠበቁት መንገድ “ነበሩ!” ሆኑ።
ኢሳይያስ የዩኒቨርስቲ ትምህርቱን አቋርጦ በረሀ ገባ። ሸፈተ። ከ50 አመት በፊት ነው። ጀበሐ ErItrean Liberation Front (ELF) ሆነ። ጀበሀን በላ! ሻአቢያን (EPLF) ፈጠረ! ከዚያ በኋላ ያልሆነው ነገር የለም። የሆነው ሁሉ እንኳን እኔ እሱም ሳይጠፋው አይቀርም።
****
ከፍተን ብናየው!

ኢሳይያስ አፈወርቂን በአካል ያየሁት ነሐሴ 1981 አፍሪቃ አዳራሽ ወያኔና ሻንጣ ተሸካሚዎቹ አዲስ አበባ ገብተው ባዘጋጁት “የሰለምና ዲሞክራሲ ጉባዔ” ላይ አፍሪቃ አዳራሽ ነበር። ነገሩ፣ ማለትም ስብሰባው ሠላምንም ዲሞክራሲንም ለመቅበር መሆኑ አሁን ቁልጭ ብሎ ይታየኛል። ያኔ ጥርጣሬ ብቻ ነበረኝ።
ያዘጋጁት፣ ወይም ከመጋረጃው ጀርባ ሆነው ያዘጋጁት ፖል ሔንዝና (Paul Hanze) ሔርማን ኮኸን (Herman Cohn) ይመስሉኛል። ፖል ሔንዝ የዝነኛ የሲ.አይ.ኤ (CIA) ሰላይ ነበር። የነመለስ ዜናዊ የነፍስ አባት (Godfather) ነኝ ብሎ የጻፈውን አንብቢያለህ። ኮኸን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር (State Department) የአፍሪቃ ጉዳይ ሚኒስቴር ነበር። አሁን ደሞ ሰለኢትዮጵያ ሲያላዝን ሰማሁት። አዲሱ ጭምብል (Mask) መሆኑ መሰለኝ።
ሁለቱም የረዥም ጊዜ የሥራ ውጤታቸውን ለመመረቅ አዲስ አበባ መጥተው ነበር። ፖል ሔንዝ ሊያገኘኝ ፈልጎ ሰው ቢልክብኝ “ይቅርብኝ! አልኩት። ኮኸንን ግን ብሔራዊ ቤተመንግስት (ኢዩቨልዪ ይባል
Page 3 of 11
የነበረው) ግቢ ከመለስ ዜናዊ ጋር ለብቻቸው ፈንጠር ብለው ሲነጋገሩ ጣልቃ ገብቼ አነጋገርኩት። መለሰ ዜናው በዐይኑ ሊገስጸኝ ሞክሮ ነበር። አንዳንድ ሰዎች ተግሳጽም አይገባቸውም መሰለኝ። እዚያ ውስጥ ሳልመደብ የምቀር አይመስለኝም።
ሌላ ስለ ፖል ሔንዝ ትዝ የሚለኝ አሜሪካ የመጣሁ ሰሞን ካላገኘሁት ብሎ የሕግ ትምህርት ቤቱ መሥራችና የዩንቨሪስቲው አካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት በነበሩት በዲን ፓል በኩል ቢጨቀጭቀኝ፤ እሳቸውም “ሊረዳህ የሚችል ሰውኮ ነው! ብቻ ጠንቀቅ በል!” ብለውኝ ላገኘው ቢሮው ተቀጣጠርን። ሔንዝ ሥራው ዋሽንግተን ዲ.ሲ Rand Corporation የሚባለው ግዙፍ የስለላ ማቀነባበሪያ ኩባኒያ ውስጥ ነበር። ምሳ ሊጋብዘኝ እምድር ቤት ይዞኝ ወርዶ የመጀመሪያ ጥያቄ “ከየተኛው ጎሳ (Tribe) ነህ?” የሚል ነበር። ገርሞኝ “አልገባኝም!” አልኩት። “እነደምታውቀው ኢትዮጵያ ሁሉም ጎሳ አለውና …” ሲለኝ “ያንተስ?” አልኩት “እኔማ አሜሪካዊ ነኝ! አለኝ “እኔም እትዮጵያዊ …!” በዚህ ፈግጠው! ፈግጠው! ተባብለን ምሳዬንም ሳልበላ ተለያየን። የነፍስ አባቴ (Godfather) ሊሆን ፈልጎ ይመስለኛል። ይኸው ሳልጠመቅ ተለያየን!
ይኸኛው ነገርን ነገር ያነሳዋል መሆኑ ነው።
***
በዚህ “የሰላምና ዲሞክራሲ” የአፍሪቃ አዳራሽ ስበሰባ የኢትዮጵያ ጉዳይ በሶስት ቀን ተጠናቀቀና አራተኛው ቀን ለኤርትራ ተመደበ። ይህ ከመሆኑ አንድ ቀን በፊት ለቡና እረፍት ተደርጎ የነበረ ጊዜ የቢ.ቢ.ሲ (BBC) ተወካይ የነበረ ላስት(Last) የሚባል ጋዜጠኛ አገኘኝና “ምስኪን አስፋ እንዴት ታሳዝናለህ” (Poor Assefa I pity You!) አለኝ። ከአንድ ወር በፊት Ominibus በሚባል የቢ.ቢ.ሲ ፕሮግራም ለተላለፈ ቃለ መጠይቅ አድርጎ “ምስኪን እስረኛ!” ብሎ ገንዘብ ብጤም ሰጥቶኝ የነበረ ነው። “ምን ሆኜ ነው የማሳዝነው?” አልኩት። “ይህንን ሶስት ቀን ሙሉ የኦሮሞ ነጻ አውጭ ድርጅት (ኦነግ) ከእናንተ ጋር ያሉ መስሎህ ስትዳክር!” አለኝ:: “ታዲይስ?” ስለው “ሎንዶን ለተዘጋጀው ስበሰባ ከመሔዳቸው በፊት ወያኔ ሻአቢያና ኦነግ ኤርትራ፤ ተሰነይ ከተማ ተሰብስበው የመጨረሻውን ውሳኔ ሁሉ ተስማምተው ነው የመጡት። ከእናነተ ጋር ሳይሆን ኦነግ ከወያኔና ከሻቢያ ጋር ነው የወገነው!” አለኝ። ጨስኩ! ሌሎችም ለሶሰት ቀን ግራ አጋብተውኝ የነበሩት ጭብጦች ፍንተው ብለው ታዩኝ። ስበሰባው እንደገና እንደተጀመረ በኦነግ ተወካዮች፣ በማውቃቸው ወዳጆቼና በኔ ሰር ሆነው ይሰሩ በነበሩት ላይ ፈነዳሁ። ከኔ ፍንዳታ ይልቅ ጎልቶ ትዝ የሚለኝ የሲዳማው የአቶ ወልደ አማኑኤል ዱባለ ነበር። ጣቱን ኦነግ መቀመጫ ላይ ሰትሮ “ትላንት ለምንሊክ ዛሬ ደግሞ ለትግሬዎች ሸጣችሁን!” አለ። ይህ ሁሉ በውቅቱ በድምጽም በምስልም የተቀረጸ ስለሆነ አጥኝዎች ቢፈልጉት ሊያገኙት የሚችሉ ይመስለኛል።
ይህ ኢሳይያስ አፈወርቂን በተጨማሪ መነጽር እንድምለከተው ሌላ ቀዳዳ ከፈተልኝ!
*
ከዚያም የስብሰባው ሊቀመንበር የነበረው አቶ መለስ ዜናዊ የኢሳይያስ አፈወርቂን ንግግር በጥሞና እንድናዳምጥ መመሪያ ሰጠንና ተዘጋጅቼ ማዳመጥም መመልከትም ጀመርኩ። መጀመሪያ ልብ ያልኩት የኢሳይያስን አቀማመጡንና የሰውነቱ አያያዝ (Body Language) ነበር። የተቀመጠው በቀኝ በግራው በሰዎች ተከቦ ወጣና ጎላ ያለ ወንበር ላይ ነበር። የተኮፈሰና የሚኮፈስ (Preposterous and pompous)
Page 4 of 11
መስለኝ። ፊታቻውን አኮሳትረው፣ “ትንፍሽ ትይና ወዮሊሽ!” የሚል መልክ ይዘው ክፍል የሚገቡ አንዳንድ አስተማሪዎችን አስታወሰኝ። ከዚያ ንግግሩን በትግሪኛ ጀመረ።
የመጀመሪያው ወደ አማርኛ አስተርጓሚ ዶክተር በረከት ሐብተሥላሴ ነበር። ዶክተር በረከት ሐብተሥላሴን አውቀዋለህ። በንጉሱ ዘመን እዚሁ አፍሪቃ አደራሽ የቀደሞሙ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ማህበር (Alumni Association) ያዘጋጁት ስብሰባ በረከት ተናጋሪ እኔ አዋኪ ሆነን ተለያይተናል። ሕግ ትምህርት ቤት ነበርኩ። ከትላንትና ወዲያ ሲያገኘኝ “አስፋ እንደገና አፍሪቃ አዳራሽ ተገናኘን!” አለኝ። “ልክ ነው! ሆኖም በተለያየ በር ነው የመጣነው!” አልኩትና ተሳሳቅን። የመጀመሪያ አስተርጓሚው በረከት ነበር ብያለሁ። አንድ አምስት ደቂቃ አንዳስተረጎመ ኢሳይያስ “አልቻልክም!” ብሎ አስወገደውና በሌላ አጠር ባለ ሰውዬ ተካው። ይህ አጠር ያለ ሰው አንድ 7 ደቂቃ አስተረጎመና “አልቻልክም!” ተብሎ ተወገደ። የዚያን ጊዜ መለስ ዜናዊ፣ ከወዲያ ማዶ ከሊቀ መንበርነቱ ወንበር እጁን አውጥቶ “እኔ አስተረጉማለሁ!” አለና ተፈቅዶለት! ቀጠለ! አንድ አራት ደቂቃ እንዳስተረጎመ “አልቻልክምና!” ተብሎ ተወገደ።። አራተኛ ሌላ ሰው መጣና የኢሳይያስ ንግግር ተፈጸመ። የተጨበጨበ መስለኝ። ልብ አላልኩም! እኔ ልቤም ማስተዋሌም ያተኮረው ኢሳይያስ አፈወርቂና እዚህ አሳዛኝና አስቂኝ ቲያትር (Tragic Comedy) ላይ ነበር። ከይዘቱ ይልቅ ቅርጹ ላይ!
አስቂኝነቱ ቀርቶ አሳዛኝነቱ ጎልቶ የሚወጣው ይህ ሁሉ የሚደረገው “ያጋራ ቤታችን!” ላይ መሆኑ ነው!
የኔ የማሕበራዊ ገፆች (Facebook etc) ወዳጆቼ (Friends) በአብዛኛው ወጣቶች ስለሆኑ ዶክተረ በረከት ሐብተሥላሴን ላያውቁት ይችላሉ። በረከት የሐረር ልጅ፤ የግእዝ ሊቁ የአለቃ ሐብተሥላሴ ልጅ ነው። ስለዚህም የቤተክህነት ትምህርትም አለው። እንደአለቃ ለማ እንደመንግሥቱ ለማ! ማለት ነው። ዶክተርነቱ በሕግ ከእንግሊዝ አገር ነው። እንግሊዝ ልከው እንዲማር ያደርጉት ኃይለ ሥላሴ ነበሩ ተብሏል። የሐረር ልጅ ናቸውና! አባቱንም ያውቃሉና!
በረከት በንጉሱ ዘመን የኢትዮጵያ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ነበር። ሕግ ትምህርት ቤትም ያስተምር ነበር። መጀመሪያ ያየሁት ለአለም አቀፍ ዝምታ ፍርድ ቤት ( International Moot Court Competition) የሕግ ተማሪዎች የማጣሪያ ወድድር ስናደርግ ከፈረንጆች ጋር ዳኛ ሁኖ የመጣ ጊዜ ነበር። በደርግ ዘመን ደግሞ የመርማሪ ኮሚሽን ሊቀ መንበርም ሆኖ ነበር። ሊቀ መንበር እያለ ነው ሻቢያን የተቀላቀውና አማካሪ የሆነው። ስለሻቢያም ስለኢትዮጵያም መጽሐፍት ጽፏል። ከዚያ ሁሉ በኋላ ኢሳይያስ ሌላው ይቅርና ለአስተርጓሚነት እንኳን አትበቃም ብሎ እዳሪ ጣለው።
በረከት ሐብተስላሴ ተምሳሊት (Template) የሚሆን ይመስለኛል። የአስቆሮቱን ይሁዳንም ያስታውሰኛል። ወንጌሉ እንደሚለው ይሁዳ ጌታውን የሸጠበትን ሰላሳ ብር አልበላባትም! አልጠጣባትም! ይልቁንም ራሱን ሰቀለ! ገንዘቡም “ራሱን የገደለ ገንዘብ ለሌላ ጉዳይ አይሆንም ብለው የመቃበር ቦታ ገዙበት። “አልቄዳ” የሚባለው ነው። የደም መሬት! ወያኔ ይህንን “የደም መሬት!” ትእይንት አድርጎት አቅርቦታል ልበል? ጎበዝ! ጠንቀቀ ነው ደጉ!
Page 5 of 11
እንዳልኩት በረከት አገርን ለከዱ፤ ለሚከዱ ሁሉ ተምሳሊት (Template) የሚሆን ይመስለኛል!!
ለመሆኑ ኢሳይያስ አፈወርቂ ያንን ሁሉ አስተርጓሚ “አልቻላችሁም!” የሚለው ምኑን ነበር? ትግርኛውን አይመስለኝም! ወይም በኔ ደርጃ ያለ ትግሪኛ አትረዱም ማለት ይሆን? አማርኛ አትችሉም ነው? ይህን ማለት ደግሞ ኢሳይያስ አማርኛ ማወቅ ብቻ ሳይሆን እስኪያርም ጠንቆቆ ያውቃል ማለት ይሆናል። ወይም “ማን አለኝ ከልካይ!” መሆኑን በዚህ መድረክ ለመላው ኢትዮጵያ ህዝብ ላስመስክር ይሆን? ወይም ይህ መሪያችሁ ነኝ የሚለውን መለስ ዜናዊን እንኳን እነደመሪ ከመጤፍም አልቆጥረውም የሚል መልእከት ለኢትዮጵያ ሕዝብ መላኩ ይሆን? ወይም ማንንም ምንንም በአደባባይ ለማዋረድ ብቃትና እወቅት ያለኝ ሰው ነኝ እውቅሉኝ ይሆን? በዚያም በዚህ ብትሉ የኔን ያክል አዋቂ ቀርቶ እኔ የምለውን፤የምናገረውን መረዳት የሚችል እንደሌለ እይሉኝ ነው?
የሥነልቡና አዋቂዎች (Psychaitrists) ምን ይሉ ይሆን? በሽተኛ መሆኑን ይቀበላሉ! የበሽታውን አይነት ምን ይሉት ይሆን? አንዳንዱ የአንጎል፣ የአእምሮ፣ የህሊና ህመመ ታክሞ የማይድን ነው ይሉታል። ለምሳሌ Sciopath የሚሉት! “እቡይ!” እንደማለት! “እቡየ ዐይን ወስሱሀ ልብ ኢይትሀወር ምስለየ” ይለዋል ዳዊት።
በኢሳይያስ ንግግር ወቅት በኔ ጭንቅላት፣ በኔ ህሊና፣ በኔ አእምሮ የሚተራመሱት ይህንና ይህንን የመሳሰሉ ጥያቄዎች ነበሩ።
Page 6 of 11
****
አሁን የኢሳይያስንና የኦነግን የቆየና “የፀና” ግንኙነት በዘመን ረድፍ ለማስቀመጥ እሞክራለሁ::
በዘመነ ደርግ በድርቅ ከተጠቁ የሰሜን ኢትዮጵያ አካባቢዎች በተለየም ከወሎ ሠፋሪዎች አሶሳ ሰፈረው ነበር። አንድ ምሸት የሰፈሩበት መንደርም፣ ሠፋሪዎች ጭምር በጥይትና በዕሳት ጋዩ። ይህንን ያደረገው የሻአቢያና ኦነግ ሕብረት ነበር። መንገድ መሪ ኦነግ መሆኑ በወቅቱ በሕዝብ መገናኛዎች እስኪሰቀጥጥ ተነግሯል። የሚገርም ሌላም ነገር አለ። አሶሳ ወለጋ ክፍለ አገር ውስጥ ይሁን እንጅ ኦሮሞም የኦሮሞ መሬትም አልነበረም! አይደለምም! “ነፃ አውጭ” ነን ቢሉ እንኳን ኦሮሞን እንጅ ቤኒሻንጎልን አይደለም። ሌላው የሚገርመው በወቅቱ የኦነግ መሥራችና መሪ ባሮ ቱሙሳ ምንሊክ ግቢ ከደርግ ጋር እየሰራ ነበር። ከምእራብ ኢትዮጵያ ወለጋ ነፍሰ ገዳይ ፍለጋ ኤርትራ በረሀ ድርስ ምን ወሰዳቸው? የሐሳቡ አመንጭ ኦነግ ነው ወይስ ሻአቢያ? ጭካኔ የነፃ አውጭነት አንደኛው ባሕርይ ነው?
 የሚቀጥለው የተሰነይ ስብሰባ ነው። መለሰ ዜናዊ፣ ኢሳይያስ አፈወርቂና ሌንጮ (ዮሐንስ) ለታ በአንድ ግንባር ስር ለንዶን ለመጓዝ እነደተሰማሙ የሚያሳይ የሚጨባበጡበት ፎቶግራፍ በድሕረገጾች ታይቷል። ምን ነበር የመገናኛና የአንድነት መሠረቱ (Point of Convergance)? ነጥባቸው? ኢትዮጵያን በሚመለከት ማለቴ ነው!
 የሎንዶኑን ስብሰባ ያዘጋጀው የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር (State Department) ነበር። ሔርማን ኮኸን እዚያው ነበር። የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ ተስፋዬ ዲንቃ ጠቅላይ አቃቤ ሕጉን ቢልልኝ ማንደፍሮንና ዶክተር ግርማ ወልደስላሴን ጨምሮ ለንዶን ደርሰዋል።
 ስለኢትዮጵያ መልእከተኞች ጉዳይ የአቶ ተፈራ ኃይለሥላሴን The Ethiopian Revolution መጽሐፍ ማንበቡ ጥሩ ነው። አቶ ተፈራ በወቅቱ በእንግሊዝ የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለነበር የታዘበውን ጽፏል። “ለስደት ቤተሰቦቻቸውን ይዘው መጡ እንጅ ለውይይት አልነበረምም! አይመስልምም” ይላል። እንዳለውም አቶ ተስፋዬና ቢልልኝ ቤተሰቦቻቸውን ይዘው ወደ አሜሪካ አመሩ። እዚያም ሲደርሱ እነ ዶከተር ግርማን ጣጥለው ወደሚሔዱበት ሔዱ። እኔ መጀመሪያ ዋሺንግተን ዲ.ሲ ያገኘሁት ዶክተር ግርማን ነበር። “አሰፋ እኔ ያደረጉኝን ያድርጉኝ እንጂ ወደኢትዮጵያ እመለሳለሁ!” እንዳለው ተመለሰ። ከንክኖኝ አንዳንድ ነገር ለመጠየቅ የሚሠራበት የዓለም ባንክ ቢሮ ሔጄ አቶ ተስፋዬ ዲንቃን አነጋገርኩ። ጸሐፊው ቡና አመጣችልኝና ጠጥቼ ብዙም ሳልጠይቅ ወጣሁ። “ለመሆኑ ምንና ምኑ ይጠየቃል?” ብዬ መሆን አለበት!
 የሎንዶኑ ስብሰባ፣ ስብሰባ ካልነው፣ የአሜሪካን መንግስት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ከፈጸመው ታላላቅ ደባዎች ውስጥ ቀዳሚነት የሚኖረው ነው። ሌላው ሶማሌ ወራ ድሬዳዋ ልትገባ ስትገሰግስ የጦር መሣሪያ ማእቀብ በኢትዮጵያ ላይ መጣሉ ነው።
Page 7 of 11
 የሎንዶኑ ስብሰባ ሌላ ትልቅ ምስልም ነበረው። መንግስቱ ኃይለማርያም ከነቤተሰቡ ዚምባቢዌ እንዲሰደድ፣ ጄነራል ተስፋዬ ገብረ ኪዳን ፕሬዚዳንት እንዲሆንን የኢትዮጵያን ጦር ሠራዊት “እጅህን ለወያኔ ስጥ!” እንዲል፣ መለሰ ዜናዊ፣ ሥዩም መስፍንና ጓደኞቹ በሱዳን የጸጥታ ጉዳይ ሚኒስቴር ጀነራል አልፋቲህ አርዋ በሚነዳ አውሮፕላን አዲስ አበባ እንዲገባ፣ እነሌንጮም የተሰጣቸው “የቤት ሥራ” በትክክል እንዲወጡ ማድረግ የአሜሪካን መንግስት የተቀነባበረ ሥራ ነበር። የረዥም ጊዜ ሴራ ውጤት ነበር!!
በትክክል ሥራ ላይ ማዋሉን ለመከታተል አዲስ አምባሳደር ባስን (Baas) አዲስ አበባ በአስቸኳይ ላኩ። የነፍስ አባቲየው (The Godfather) ሔርማን ኮኸንም የድል ምሸቱ ላይ ለመገኘት አዲስ አበባ መጣ። አምባሳደር ባስም ኢትዮጵያን እስክለቅ ድረስ ብርቱ ወዳጄ ሁኖ ሰንብቷል። ሁለት የአሜሪካን ሴናተሮች ለጉብኘት መጥተው ኖሮ ለነጻነታቸው በዓል July 4th 1991 አሜሪካን ኤምባሲ የጋበዘው ኢትዮጵያዊ እኔና ባለቤቴን ብቻ መሆኑን አስታውሳለሁ። የፖል ሔንዝ ተልእኮ አይነት የሚያጣ አይመስለኝም!
 ለዚህ የሰላምና ዲሞክራሲ ስብሰባ የመጣም፣ ያመጡትም፣ ደጅጠኝውም፣ የድል አጥቢያ አርበኛ ለመሆን ያኮፈክነውም መናሐሪያችን አዲስ አበባ ሒልተን ሆቴል ነበር። ከወያኔና ሻአቢያ በስተቀር! የወያኔ ጭፍሮቹ የት እነደሰፈሩ አላውቅም። ሻአቢያ የሰፈረው የጄኔራል ተፈሪ በንቲ መኖሪያ የነበረው ነው ተባልኩ። ግራ የገባኝ የኦነግ አባሎች የት ደረሱ? የሚል ነበር። ስብሰባ ላይ ሳገኛቸው “እነዚህ ሰዎች ከኛ ነጠሏችህ!” እላለሁ። በዚያ በሰብሰባው መካከል የደቡብ ሕብረት ለመመሥረት ማታ ማታ እንነጋር ስለነበር እንዲገቡበት ፈልጌ ነበር። በኋላ የቢ.ቢ.ሲው ላስት ተሰነይን ሲነግረኝ ግልጽ ሆነልኝ። የኦነግ አባሎች፣ ሌላው ቀርቶ ከኔው ጋር ማእከላዊ የነበሩት ጭምር ሰፈራቸው ከሻአቢያ ጋር ጄነራል ተፈሪ በንቲ መኖሪያ የነበረው ሆኖ ተገኘ። እንዲህ አንድ ጡት ጠብቶ ያደጉ የሚያስመስለው ፍቅር፣ ሌሎቻችንን እንዲሸሹ ያደርገው ፍቅር፣ ከየትወረደ? የሚያሰኝ ነበር። ምን ይሆን? የኢትዮጵያስ ይቅር እውነት የኦሮሞ መሠረታዊ ጥቅም ነው? ጫወታው ሌላ መሆኑ በጥቂት ወራት ታዬ! እመለስበታለሁ!
Page 8 of 11
 ከአፍሪቃ አዳራሹ ስብሰባ በኋላ የሽግግር መንግስሥትና የሽግግር ምክር ቤት ተቋቋመ። ለጥቂት ወራቶች የሽግግሩ ምክር ቤት አባል ነበርኩ። ኦነግ 8 መቀመጫዎች ነበሩት። በ ኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች መጠን ማለት ነው! አራት ሚኒስትሮችም ተሾሙ። ከዚህ ውስጥ ጎልቶ የሚታውሰኝ ምክር ቤቱ ውስጥ ሁለት የኦነግ ተወካዮች፣ ሌንጮ ለታና አብዩ ገለታ ሥራ ነበር። የኢትዮጵያን ብሔራዊ ሠራዊት አፍራሽ ኮሚቴ ሊቃነ መናብርት ሆኑ። የኢትዮጵያ ሠራዊት አይሉትም። “የደርግ ወታደር!” ይሉታል። ለማስረዳት ሞከርኩ። “ደርግ መንግስት ነው። መንግስት ሠራዊት የለውም። አገር ነው ሠራዊት ያለው። ከዚህም ሌላ ወንጀለኞች ቢኖሩ በማስረጃ ማረጋጋጥና መጠየቅ እንጅ የአገር ሠራዊት ይፍረስ ተብሎ አይታወቅም!” ከንቱ ጩኸት ሆነ።
 ቢቸግረኝ አንድ ቀን ሌንጮንና አብዩን ቡና ጋብዤ “ይህ ይፍረስ! ይፍረስ! የምትሉት ሠራዊት ኦሮሞኮ ነው። አሁን በደመወዝ መተዳደር የለመደ፤ ከግብርናውም የተፋታውን በትነን በጭፍን እስር ቤት መክተትና ለማኝ ማደርግ…” አልኩኝ። ”ማነው ኦሮሞ ነው ያለህ?” “ይህማ ግልጽ ነው! አንደኛ ሥራዊቱ አብዛኛው የተመለመለው ከደቡብ ነው። ከዚህም ሌላ በኢትዮጵያ ኦሮሞ አብላጫ ቁጥር አለውና…” አልሰሙኝም! ሊሰሙኝም አልፈለጉም! አይችሉምም! እነሱ የወያኔ ጉዳይ አስፈጻሚ እንጅ ባለጉዳይ አልነበሩም! ብቻ የኢትዮጵያ ሠራዊት ፈርሶ ወደ ልመናና ወደስደት ተዳረገ! መፍረሱ አይቀሬረ ነበር! ባለጉዳዩ ቢያፈርሰው! የዚያን ዘመን የምክር ቤት ውይይት ያዳመጠ አፍራሹ ኦነግ መሆኑን ያያል። ተመዝግቦ የተቀመጠ ነው!
 የትምህርት ሚኒስቴር ሁኖ የተሾመው ኢብሳ ጉተማ ነበር። ሀ ብሎ ያረቀቀው አዋጅ ኦርሚኛ በላቲን ፊደል እንዲጻፍ ነበር። ወዳጄ ስለነበረ ቢሮው ሔጄ “ኢብሳ አብደሀል እንዴ! ኦሮሞን ወደቅኝ ግዛትነት ልተመልሰው ነው!?” አልኩኝ “እንዴት?” ቢለኝ “ቅኝ ግዛት የነበሩት ሁሉ የሚጽፉት በላቲን ፊደልና የሚናገሩትም እሱኑ ነው!” አልኩኝ። የሆነ የነፍጠኛ ደጋፊ የሚል ቀልድ ሲያመጣ “ይህ የአማርኛ ፊደል የአማራ ፊደል አይደለም! የመጀመሪያውና ብቸኛው የጥቁር ሕዝብ ፊደል ነው! ልንኮራበት ይገባል …” አልኩት። አልሆነምና የሆነው ሆነ!
 ምክር ቤቱ ውስጥ የኢሕአድግ አባል የሆነ “የኢትዮጵያ መኮንኖች ግምባር” የሚባል ባለ 8 መቀመጫ ድርጀት ነበር። ምርኮኛ የነበሩ መኮንኖች ማለት ነው። አንድ ሁለት ሶስት ቀን ያክል ምክር ቤቱ ውስጥ አላያቸውም። አንድ ጥዋት ቡና እረፍት ላይ ሥዩም መስፍንን “ሥዩም እነዚህ መኮንኖቻችን አላያቸውምሳ?” አልኩት። ከት ብሎ ስቆ “አቶ አስፋ ሚናቸውን ጨርሰው ተሽኝተዋል!” አለኝ። “ታዲያ 8ቱ መቀመጫ ምን ይሆናል?” አልኩት። ”ወያኔ ወስዶታል!” አለኝ። ሌላ ጥያቄ ከመጠየቄ በፊት ሔደብኝ።
 የኦሮሞ ነጻነት ግንባርም ልክ የመኮንኖቹ ደረሰባቸው። ታህሳሳ ይሆን ጥር 1982 መመሪያ ተሰጣቸው። “ከዛሬ ጀምሮ ምክር ቤቱ ውስጥ ያላችሁን ድርሻ ፈጽማችኋል! ከዛሬ ጀምሮ ከኢትዮጵያ ምድር እንድትወጡ! ካልወጣችህ ወህኒ ቤት ትወረዳላችህ! ምርጫውን ለእናንተው እንተዋለን!” ተባሉ። ከተሰጣቸው ሁለት ምርጫ ኢትዮጵያን ለቀው መውጣትን መረጡ። አህያ የተጫነችውን ታደርሳለች እንጅ አትበላውም! እንዲሉ።
 ከወያኔ ጋር አዲስ አበባ እንደገቡ አሁን “የኦነግ ተዋጊ ኃይል ነው የምትሉትን ሁሉ ከነመሣሪያው ጦር ካምፕ አስገቡ!” ተባሉ። በታዘዙት መሠረት አስገቡ። ከአገር ቤት መውጣት ወይ እስር ቤት ምርጫ ሲሰጥ እነዚህ ጦር ካምፕ ውስጥ በቁም እስረኝነት ያስረከቡት ተዋጊዎች ደረጃ ወደሙሉ እስረኝነት ተሸጋገር። እጃቸውን ራሳቸው ላይ አድርገው በሴት ወያኔ ወታደሮች እየተነዱ እስር ቤት ወረዱ። እስከዛሬ እጣ ፈንታቸው ምን እንደሆነ፣ ከምን እንደደረስ የጠየቀም፣ ያስረዳም የለም!
Page 9 of 11
**
ኦነግ፣ ኢሳይያስ አፈወርቂና የአትላንታ ስብሰባ

 የአትላንታ፣ ጆርጂያ የኦሮሞ “ምሁራንና ብሔርተኞች” ስብሰባ አንድ ግብ አስቀምጧል። “የኦሮሞ ሕዝብ ትግል ለነጻነት የሚበቃ፤ እነደኤርትራ፤ ትግሬና ደቡብ ሱዳን መሆን አለበት!” ይላል። ጎበዝ! “ቸር ተመኝ! ቸር እንድታገኝ!” ይባላል። ፈረንጅ ደግሞ “ለከዋክብቱ አነጣጥር ብትስት እንኳን የባህር ዛፉን አናት ትመታለህ!” (Aim to the Stars! If you miss, You Will Hit the Top of the Tree! ይላል። ኢሳይያስ መላው አለም ማእቀብ አድርጎበት፣ ከዛሬ ነገ የአለም ጦር ፍርድ ቤት ይቀረባል እየተባለ የሚባንን ጉድ ነው። ወያኔ እንደሚታየው ጣእረሞት ላይ ነው። የደቡብ ሱዳን የሚባለው አገር የከሸፈ አገር (failed State) ነው ወይስ አገር ነው? እየተባለ ነው። በቃላት እንኳን ቢሆን ለዚህ ለታላቁና ገራ-ገሩ የኦሮሞ ሕዝብ ከዚህ የተሻለ አድማስ መቅረጹ በተገባ ነበር። የአትላንታውን ስብስብ አድማስ መፈለጊያ መነጥር መሰለኝ። የተሻለ መነጽር ባይኖር ወይ መግዛት ወይም መዋስ በተገባ ነበር።
 ወያኔ “ከኢትዮጵያ ጥፉ!” ብሎ ካባረረ ከ1982 ጀምሮ ኦነግ ብዙ የውስጥ ትርምስ የገጠመው ይመስለኛል። አንዴ ስለታዘብኳቸው ዝርዝሩን ብዙም አልከታተልም። “ወትሮም የኦሮሞ ሳይሆን የአንድ መንደር ሥልጣን ፈላጊዎች ጥርቅም ነበር!” በሚል ማን ይምራ ማን የሚል ትርምስ የተፈጠረ ይመስለኛል። አብዩ ገለታ ዋሽንግቶን ዲስ የነበሩትን የኦነግ ልጆች ቢሮ ነጥቆ “እኔን ሹም!” አለ። አንድ ቀን በአካባቢው ነበርኩና ልጠይቀው ቢሮ ሔድኩ። ልክ ለኢሳይያስ እንዳልኩት ተኮፍሶ ጠበቀኝ። የዚህ የምክር ቤቱንና የማባረሩን ጉድ ያነሳብናል በሚል ፍርሐት በሩን መዝጋቱ መስለኝ። ሥራ የበዛበት ለማስመስል ብዙ አስጠበቀኝ። በኋላ ቢሮው ስገባ የጄነራል ታደስ ብሩን ፎትግራፍ በትልቁ ግርግዳው ላይ አየሁና፣ ፈገግ አልኩኝና “እኒህ ደግሞ ማናቸው?” አልኩት። ገርሞት “አታውቅቸውም እንዴ? ጄነራል ታደስ ብሩ ናቸው!” አለኝ። ”ኦነግ ነበሩ እንዴ?” አልኩት ጄነራል ታደስ ብሩ ኦሮሞን ለማስተማርና ንቃተ ህሊናውን ከፍ ለማድረግ የጀመሩት ጥረት ተጣሞ ተተርጉሞ የታሰሩ፣ በኋላም በአሳሳሾች ለአጉል ወሬ የተዳረጉ፤ ጀግና ኢትዮጵያዊ ነበሩ።በስም መነገድ የሚባለው የዚህ አይነቱ ይሆን?
 ሌላው የኦነግ ቅርንጫፍ የተከፈተው ኤርትራ፣ አስመራ ነበር። መሪዎች ነን የሚባባሉት የተፈራረቁ ይመስለኛልና በሙሉ አላውቃቸውም። አሁን ካሉት፣ ወይም አለን ከሚሉት አንዱ ኦቦ ዳውድ ኢብሳ ነው። በኢትዮጵያ የተቀጣጠለውን የኦሮሞ ሕዝብ አመጽ የምመራው እኔ ነኝ የሚል መግለጫ ባለፈው ወር ሰጥቶ አንብቤ ድፍረቱን አደነኩ። ዳውድ ኢብሳ እነደአንዳርጋቸው ጽጌ ኢሳይያስ የማይጠረጥረው የኢሳይያስ ታማኝ ነው። ታማኝ መሳሪያ ነው አላለልኩም! አሁን ለመሳሪያነት ብቁ ሆኖ አልተገኘም! በንግድ ስራ ተሠማርቶ መካካለኛው ምስራቅ ይመላለሳል። አሥመራ ውስጥ ቆንጆ መኪና ከሚነዱት ውስጥ አንዱ ተስፋዬ ገብረአብ ነው። ያችን መኪና ለተስፋዬ የሸጠው ዳውድ ነው።
 የአትላንታው ስብሰባ ለዳውድ ልክ በወያኔ ቋንቋ አንድ “ኮማንድ ፖስት” ሰቶታል። የምእራብና የምስራቅ ኮማንድ ፖስት ይለዋል።
 ሌላው የደቡብ ኮማንድ ፖስት፣ ቦረናን፣ ባሌንና አርሲን የሚያጠቃልለው ኮማንድ ፖስት አዛዥ ጀነራል ከማል ገልቹ ነው። ከማል ገልቹ በምርኮኝነት ተይዞ፣ ኦፕዲኦ የሆነ የወያኔ ሰው ነበር። እስከ ዛሬ ሶስቴ ከድቷል ማለት ነው! ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ በሽ- በሽ የሆነ ነገር ቢኖር ዶክተር መሆንና
Page 10 of 11
ጀነራል መሆን ዋንኛ ይመስለኛል። ከማል ገልቹም “ጀነራል ሁን ተባለ ጀነራልም ሆነ!” የምንለው ነው። “ብርሐን ይሁን አለ ብርሐንም ሆነ!” መጽሐፍ እንዲል። የአርሲ ልጅ ነው።
 ከማል ገልቹ አሁን አምባሳደር ነው። የኢሳይያስ አፈወርቂ አምባሳደር ሁኖ ለተልእኮውምሥራቅ አፍሪቃ ከተላከ ሰንብቷል። በአርሲ አካባቢ እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ነው የተላከው። ይህ የአትላንታው ጉባዔ የሰጠውን ኮማንድ ፖስት ማጠቃለሉን እርግጠኛ አይደለሁምና አጣራለሁ።
 ከማል ገልቹ ዩጋንዳ ከመላኩ በፊት ታመኝነቱን ለማረጋገጠም፣ አንድ የበላይ አካል ተቆጣጣሪም ስለሚያስፈለገው ኢሳይያስ አንድ የሻቢያ ጄናራል ልጅ ድሮለት ሚስቱም አብራው ሔዳለች። ለተጨማሪ ጥንቃቄ ሲባል፣ ከማል ገልቹ ሳያውቅ፣ የከማል ገልቹን አንድ ልጅ ከኢትዮጵያ አስመጥቶ በመያዥነት አስቀምጦታል። ልጁ መያዣ መሆኑን ከማል ገልቹ አይውቅም ነበር። አሁን ማወቅ አለማወቁን እርግጠኛ አይደለሁምና አጣራለሁ።
 እንግዲህ ከዚህ ተነስተን የግድ መድረስ ያለብን ድምዳሜ ያለ ይመስለኛል። ሁሌም 2+2=4 ነውና! ይህም፣ ከማል ገልቹና የአትላንታ ስብስብ በአንድ “ኮማንድ ፖስት” ይመራሉ ማለት ነው። ያ ከሆነ ደግሞ “የኮማንድ ፖስቱ” ጀነራል ሳሞራ ዩኑስ ሳይሆን ጀነራል ኢሳይያስ አፈወርቂ መሆኑ ነው። ከዚህም ሌላ የአትላንታውሰብሰባኢሳይያስ አፈወርቂን እንደፈርቀዳጅየትግል ተምሳሌት (Role Model) አድርጎተቀብሎታልና! ይህ በጽሁፍ ማስረጃ የተደገፈ ነው ማለት ነው። ይሰውረን!
 ከዚህ ሌላ ኢሳይያስ አፈወርቂ በኢትዮጵያ ላይ ካደረጋቸው ደባዎች ጥቂቶችን፤ የምታውቋቸውን ልጠቃቅስ። የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)ን መሠረተ እንኳን ማለት ባይቻል የኢትዮጵያን አየር መንገድ አውሮፕላን አምስት ጊዜ አስጠልፏል። አለቃቸው የነበረው ክፍሉ ታደሰ ያ ትውልድ በሚለው መጽሐፍ ገልጾታል።
 በብርሀነ መስቀል ረዳ የሚመራው የኢሕአፓ ሠራዊት ከሻቢያ ጋር በመሆን ለሁለት አመት የኢትዮጵያን ጦር ወግቷል። ይድረስ ለባለታሪኩ የሚለውን እዚያው የነበረውን፣ የተስፋዬ መኮንንን መጽሐፍ ማንበበ ነው።
 ብርሐነ መስቀልንና ጓደኞቹን አሲምባ ያስገባው የካቲቲ 25፣ 1967 የኢትዮጵያ የገጠር መሬት የታወጀ ለት ነው። ስላቁ ደግሞ እነብርሐነ መስቀል መሬት ላራሹ እያሉ ወይም እያስመሰሉ ሲዘምሩና ስሲማሩ የነበሩ መሆናቸውና መሬት ለአራሹ የሆነ ለት አሲምባ መግባታቸው ነበር።
ለማጠቃለል
 ይህ ነገር የራሱ እግር አውጥቶ አልጠቃለል ብሎኛልና በግድም ቢሆን መቆም ያለበት ይመስለኛል። ከፈለኩት በላይ ረዘመብኝ።
 ኢሳይያስ ይህንን ለምን ያደርጋል? ነው። ከህመሙ ሌላ፣ በረከት ሐብተ ሥላሴን አስተርጓሚ አትሆንም ይበለው እንጅ ምክሩን ተቀብሎታል። የዶከተር በረከት ምክር፣ መጽሐፍ የጻፈበትም፣ኢትዮጵያ የምትባል አገር በሰላም ከኖረች ኤርትራ ጠንካራና ታይዋን አይነት ልትሆን አትችልም ነው። አሁን ያንን ወያኔ ወደማሳካቱ ተቃርቧል። ከማል ገልቹ አምባሳደርም የሆነው ለዚሁ እቡይ ተልእኮ ነው።
 ዋናው ዋናው፤ በጣምም የሚያሳዝነኝ የኦነግ ጉዳይ ነው። ኦሮሞ “ኦሮሚያ” የሚባል አገር መሥርቶ “መንግስትይሁን!” እንኳን ቢባል ከራያና አዘቦ አንስቶ እስከባምባሲ መሬት ወይም መሬታቸው ያደረጉት አላቸው። አኩሪና ዝነኛ ታሪክ ያለው ላለፈው 600 አመታት ብዙ ዝነኛ የኢትዮጵያ ነገሥታትም የጦር መሪዎችም ያፈራ ታላቅ ሕዝብ ነው። ይህንን፣ የዚህን ሕዝብ ስምና ዝና አንግቦ
Page 11 of 11
ሻንጣ ተሸካሚ፤ ደጋግሞ ሻንጫ ተሸካሚ መሆን፣ ሕዝቡን የሻንጫ ተሸካሚነቱ አካል፣ አምሳል ማድረግ የሕዝቡን ክበር ዝቅ ማድረግ ወይም የራስን የታመመ የሥልጣን ጥማት ቅድሚያ መስጠት ይመስለኛል።
 መውደድን፣ ማፈርን፣ መናደድን፣ መኩራትን፣ መደሰትን ተፈጥሮ በተፈጥሮ ለሰው ልጅ የለገሰችው ስሜቶች ናቸው። እነዚህ የኦነግ መሪዎች ነን የሚሉት ይህ ጸጋ በተለየም ማፈር የሚሉት እንደተሰጣቸው እርግጠኛ ነኝ። ሊያስተውሉትና ሊፈልጉት ተግባራዊ ማድረግም የገባቸዋል እላለሁ! ይገባልም!
 ይህንን የምናገረው እነደሰው ነው። ማንም ሰው ደሴት አይደለም No Man is an Island የሚለው የ John Donne ግጥም የምውደውና የማምንበትም ነው

Filed in: Amharic