* የሰሜኑ ኮከብ አብርሃ ደስታ እንኳንም ተፈታህ !
* ከአብርሃም ደስታ እስከ ሃብታሙ አያሌው
የሰሜኑ ኮከብ ወንድም አብርሃም ደስታ ከእስር እንደሚፈታ ቢገመትም ዘንድሮ ሲሆን እንጅ ሲባል ለማመን ተቸግሬያለሁና ዛሬን መቆየት ነበረብኝ ። እናማ የሰሜኑ ኮከብ ደፋሩና ለእውነት ግንባሩን የማያጥፈው የመቀሌው አብርሃም ደስታ ” እውነት ተፈታ ” ሲባል ሰማሁ ፣ ደስ አለኝ ! አብርሽ
እንኳንም ከቤተሰብ ፣ ከዘመድ አዝማድና ወዳጅ አፍቃሪ ወገንህ ጋር ተቀላቀልክ እልሃለሁ ፣ አብርሽ :)
በእኛ ሐገር ዲሞክራሲያዊ የበቀል ፖለቲካ ሰለባዎችን አሰብኩና በደስታየ መካከል ከፍቶኝ ቆዘምኩ 🙁 ስለ ፍትሃዊ ፣ ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር እየተለፈፈና እየተደሰኮረ መሬት ላይ ያለው እውነታ ሌላ ነው ። ባሳለፍናቸው ሁለት አስርት ቅርብ አመታት በስደቱ የሆነውን እውነት ስለተናገርን ብቻ ” አይናችሁን ላፈር ” ከተባሉት መካከል አንዱና ቀዳሚው ብሆንም ነገር ላለመቀላቀል ብቻ የእኛ ነገር ልተወው ፣ መነሻየ ስለሆነው በሐገር ውስጥ እየሆነ ስላለው ፣ በዴሞክራሲያዊ በቀል ፖለቲካው ዳፋ ተጠቂ ስለሆኑት ትንታግ ወጣት ጎልማሳዎቹ ጥቃት ጥቂት ላውሳ ..
የሰሜኑ ኮከብ የምንለው አብርሃም ደስታና መሰክ ወንድሞች በሰላማዊ መንገድ ” ሐገር አለን! ” ብለው ሀሳባቸውን በተለያየ መንገድ ሲገልጹ የገዥው አካል የጥቃት ኢላማ መሆናቸውን አስታወስኩት … እርግጥ ነው ብዙዎች በሐገር ወገናቸው ድጋፍ ከፍተኛ ትምህርት ተምረው ፣ ለሐገር ወገናቸው የድርሻቸውን ማድረግ እንዳይችሉ መስራት የሚችሉበት እድሜያቸው ወህኒ እየበላው ነው … ለሃገራቸው ቀናኢ ሆነው ድምጻቸውን ባሰሙ በቀጥታና በስውር ተንኮል ፣ በበቀል ፖለቲካ እየተጠለፉ ነው … ቤተሰብና ቀሪ ዘመናቸው በፖለቲካ አረንቋ ውስጥ ተዘፍቆ በበቀል ሲገለሉና ሲሰቃዩ ለመገኘቱ እውነት ማሳያ ታይተው የጠፉ ፖለቲከኞች ፣ ጋዜጠኞችና ልሂቃን ሞልተውናል !…
በዜጋው ላይ የዘር መድልኦ ነግሶ ፣ ግፍ ልኩን አጥቶ ፣ ፍትህ ሲዛባ ፣ የወጣው ሐገር መመለስ ሞት መስሎት ፣ ሐገር ያለው ነፍሱ በሬ ሃገሩን ጥሎ መውጣት ሲሆን ሕልሙ ማየት የሚያመውን ያህል ህመም አለ አልልም! ዲሞክራሲያዊው የበቀል ፖለቲካ አካሄድ ሃገሬውን ሐገር አልባ ስሜት አውርሶ ተስፋ ቢስ እያደረገው ነው ! በተለይ እንደ ምክያታዊው ወጣት ፖለቲከኛ እንደ አብርሃ ደስታ ያሉት ወንድሞች ጥፋተኛ ተብለው ያሳሰራቸው ጉዳይ አላሳምን ብሎን ፣ መታሰርን ስንቃወም ብንከርምም ፣ ሲፈቱ የምንደሰተው ከቤተሰቦቻቸው ጋር ስለተቀላቀሉ እንጅ የታሰሩበት ምክንያት አሳማኝ መረጃ ቀርቦና አሳምኖን አይደለም !
በእኛ ሐገር ፖለቲካ ቁማር ነው … ዘባተሎው ፖለቲካ ስልጡን መሪ አጥቷል ! … ከሐገር እና ለወገን ጥቅም “ያገባናል ” ያሉ ይጮሃሉ ፣ መንግስት ሰበብ አስባብ ፈልጎ ቀና ያሉትን አንገት ለመስበር ያሳድዳል ፣ ያስራል … ” ያገባናል ” ያሉት ጩኸት ላንዳፍታ ይነሳና ተራግቦ ይረሳል … ያነሱት የህዝብና የሐገር ጉዳይ ይረሳና ጀግኖቻችን “ፍቱልን” ፣ ” አሳክሙልን! ” ብለን እንድንጮህ ያደርጉናል ፣ ሲፈልጉና ሲፈቅዱ አንገላተው ይፈቷቸዋል ፣ የታመሙትንም ቢሆን ህመሙ በልቶ ሊጨርሳቸው ሲል ፈጣሪን ከፈሩ ህክምና ይሰጧቸዋል ፣ ፈጣሪን ካልፈሩ በበቀል አሽተው ይወረውሯቸውና እያለቀስን እንኖራለን 🙁
የሰሜኑ ኮከብ አብርሃም ደስታ ከዚህ መሰሉ የእኛ ፖለቲካ አዙሪት ገብተህ ከወህኒ በመውጣትህ ደስ ብሎኛል ፣ ደስ ብሎናል ! እነሱም የሚፈልጉት የታሰርክበት ጉዳይ አስረስቶ ” እንኳንም ተፈታህ ” እንድንል ቢሆንም ርቀህባቸው ስለተጎዱ ቤተሰቦች ፣ ስለዘመድ አዝማድና ወገን አፍቃሪዎችህ ሲባል እንኳንም ተፈታህ !
ወዳጅ የሐገር ልጅ አብርሽ አሽቃባጭ ሆነህ ከተደላደለው ወንበር እንዳሻህ መሆን ሲቻልህ ፣ ስለ እውነት ለወገኖችህ የከፈልከውን መስዋዕትነት ግን ማንም አይረሳውም !
እንወድሃለን !
ነቢዩ ሲራክ
ሐምሌ 2 ቀን 2008 ዓም