ጠቅላይ ሚኒስትሩና ለጓደኞቻቸው በሙሉ
ሰላምታዬን አቀርብላችኋለሁ፡፡
የእግዚአብሔር ጊዜ የተለየ ነው፤ ትእግስቱ ስለሚያረዝመው የተረሳ ያስመስለዋል፤ እግዚአብሔር ግፍን አይረሳም፤ እግዚአብሔር ሁሌም ለአቅመ-ቢሶች ጉልበት የሚሆንበት መንገድ አላው፤ ግፍ በእግዚአብሔር በር ላይ እንደተጣለ ግም ቆሻሻ ነው፤ እግዚአብሔር ሲፈቅድ ይጠርገዋል፤ ወይም ያስጠርገዋል፡፡
እግዚአብሔር መንገዱ ብዙ ነው፤ ግፍን የሚያስከፍለው በተለያየ መንገድ ነው፤ በግፈኛው ቤተሰብ ላይ ሁሉ የግፈኛነት ጠባሳን ያሳርፍበታል፤ ሰዎች ለሥልጣናቸው ባላቸው ቅናት የእግዚአብሔርን ሥልጣን ይጋፋሉ፤ የእግዚአብሔርን ሥልጣን መጋፋት የግፍ ግፍ ነው፤ታሞ በእግዚአብሔር እጅ ባለ ሰው ላይ ጉልበተኛ መሆን በእግዚአብሔር ሥልጣን መግባት ነው፤ የግፍ ግፍ ይሆናል፤ ለእናንተም፣ ለቤተሰቦቻችሁም፣ ለአገሪቱም፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብም የሚበጅ አይደለም፡፡
ሀብታሙ አያሌው በእግዚአብሔር እጅ ነው፤ እግዚአብሔርን አትፈታተኑ፡፡
ደጉን ያስመልከታችሁ!
የግዛታችሁ ነዋሪ
መስፍን ወልደ ማርያም
ጠቅላይ ሚኒስትሩና ለጓደኞቻቸው በሙሉ [መስፍን ወልደማርያም/ፕሮፌሰር]
Filed in: Amharic