>

መንግሥቱ ሐይለማሪያም አልሸሸም!!!!!! [ኤርሚያስ ቶኩማ]

Mengistu Hailemariam 28052016ሰሞኑን የመንግስቱ ሐይለማሪያም ስም በሰፊው እየተብጠለጠለ ይገኛል መነሻው ራዲዮ ፋና መሆኑን ግንዛቤ ውስጥ መክተት ያቃታቸው የተወሰኑ ደህና የምላቸውም ሰዎች መንግሥቱ ኃይለማርያም አውሮፕላን ጠልፎ ነው ከሀገር የወጣው የሚል ፅሁፍ በመፃፍ እንደአዋቂ ሲያደርጋቸው እየተመለከትኩኝ ነው። እነዚህ ሰዎች ራዲዮ ፋና ግንቦት 20 ሲደርስ ለምን መንግሥቱ ኃይለማርያም አውሮፕላን ጠልፎ ነው የሄደው አስባለ የሚል ማገናዘብ የሚችል አእምሮ እንደሌላቸው ሳውቅ ጓደኞቼ እንደነበሩ አስቤ ስለእነርሱ የማገናዘብ አቅም አፈርኩኝ ለማንኛውም እውነታው ይህ ነው።

ራዲዮ ፋና የቀረቡት ረዳት ካፒቴን ያሬድ ተፈራ ለጋዜጠኛው መንግሥቱ ኃይለማርያም አውሮፕላን ጠልፎ ነው ኬንያ የገባው ቢሉም አልቀየምም ምክንያቱም ሰውዬው የቀረቡት ራዲዮ ፋና ላይ ነው። ራዲዮ ፋና ረዳት ካፒቴን ያሬድ ተፈራን በጣቢያው ያቀረበው መንግሥቱ ኃይለማርያም ፈሪ ነው የሐገር ፍቅር የለውም ለማስባል እንጂ በወቅቱ የደህንነት ቢሮውን የተቆጣጠረው ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደሥላሴ ከሲአይኤ ጋር ተመሳጥሮ መንግሥቱ ኃይለማርያምን ከኢትዮጵያ አስወጣው ለማለት አይደለም። ለማንኛውም ራዲዮ ፋና ይህንን ፕሮግራም ለምን አቀረበ የሚለውን ወደጎን ብለን ስለመንግሥቱ ኃይለማርያም ከኢትዮጵያ አወጣጥ ልፃፍላቹህ።

አዲስ አበባ እያለሁ በአባቴ ምክንያት ከበርካታ የቀድሞ ባለሥልጣናት የመገናኘት እና በጊዜው ስለነበረው ጉዳይ የማውራት እድሉ ነበረኝ በዚህ ወቅት ካገኘዃቸው ሰዎች መካከል የመንግሰቱ ዋና አጃቢ የነበረው ኮማንዶ አበራ አንዱ ነው። አበራ መንግሥቱ ኃይለማርያም ኬንያ ሲገባም አብሮ ኬንያ ድረስ የሄደ ነው እርሱ ያጫወተኝን ልንገራችሁ።

ግንቦት 13 መንግሥቱ ከሐገር ከመውጣቱ ከሰአታት በፊት የሚኒስትሮች ስብሰባ እየተካሄደ ነበር ይህ ስብሰባ በመንግስቱ መሪነት እየተካሄደ የነበረ ሲሆን በመሀል የደህንነት ቢሮ ኃላፊ የነበረውና ሲአይኤ እንደመለመለው የሚገመተው ተስፋዬ ወልደሥላሴ ኮሎኔል መንግሥቱን በመጥራት የብላቴ ወታደራዊ ተቋም ተማሪዎች መንግሥቱ ካልመጣ እናምፃለን ብለው ስላስቸገሩ ፈጥነው መሄድ እንዳለባቸው ይናገራል መንግሥቱም ስብሰባውን ፍሥሐ ደስታ እንዲመራው አድርጎ ወደአውሮፕላን ጣቢያ ይጓዙ ኮማንዶ አበራና የደህንነት ቢሮ ሃላፊው ተስፋዬ ወልደሥላሴ አብረው እንደነበሩ ኮማንዶ አበራ ይናገራል። ቦሌ አየርመንገድ ሲደርሱ በስፍራው የነበሩት ሻለቃ ደመቀ ባንጃው ይጨምራሉ በመቀጠልም ሻለቃ ደመቀ ባንጃው እና ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደሥላሴ ለኮሎኔል መንግሥቱ እና ለአጃቢዎቻቸው ብላቴ ከፍተኛ የሆነ የወባ ስርጭት ስላለ የወባ መከላከያ መድሃኒት እንዲውጡ ትእዛዝ ይሰጣሉ እነመንግስቱም በታዘዙት መሰረት መድሃኒቱን ይውጣሉ ይህ የሆነው ከቀኑ ስድስት ሰአት ተኩል ላይ ነበር የወባ መድሐኒት ተብለው የእንቅልፍ መድሐኒት የዋጡት እነመንግስቱ ኃይለማርያም እና አጃቢዎቹ እነኮማንዶ አበራ ገና ወደታሰበላቸው ኬንያ ሳይደርሱ እነኮሎኔል ተስፋዬ ወልደሥላሴ አዲስ አበባ ላይ “የመንግሰቱ ኃይለማርያም ከሥልጣን መልቀቅ አስፈላጊ ሆኖ ስለተገኘ ኮሎኔል መንግሥቱ ከሥልጣን ለቀው ከኢትዮጵያ ወጥተዋል” በማለት አስነገሩ።

ኮለኔል መኮንን አደላ ዋና አብራሪው ትእዛዝ ይቀበሉ የነበሩት ቀጥታ ከሻለቃ ደመቀ ባንጃው ነበር። እነረዳት ካፒቴን ያሬድ ተፈራ ቢዋሹም ኬንያ ላይ የወቅቱ የኬንያ ፕሬዚዳንት ጭምር አቀባበል አድርገውላቸዋል በወቅቱም ኮሎኔል መንግሥቱ ድጋሚ ወደኢትዮጵያ ተመልሰው መግባት እንደማይችሉ ተነግሯቸው ከአንድ አጃቢያቸው ጋር ወደዚምባብዌ ሲላኩ ሌላኛው አጃቢያቸው ኮማንዶ አበራ ከሌሎች ተጨማሪ ሁለት ሰዎች ጋር ወደአዲስ አበባ ተመልሰው ሄደዋል። ኮማንዶ አበራን ለመግደል እነኮሎኔል ተስፋዬ ሲሯሯጡ ኢህአዴግ ገብቶ ሁሉንም ወደእሥር ቤት ከተታቸው ኮማንዶ አበራ ወዲያው የተፈታ ሲሆን ሌሎቹ ሲማቅቁ ከርመዋል።
መንግሥቱን ለመተቸት ራዲዮ ፋናን እንደምንጭነት መጠቀም አስነዋሪ ነው። መንግሥቱ ኃይለማርያም የሰሯቸው በርካታ ስህተቶች አሉ ልበሙሉነቱን ግን ማንም ሊክደው አይችልም እውነት ደግሞ ቀስ እያለች እንደመስከረም ጀምበር ትወጣለች።

Filed in: Amharic