በተሰጠው ውሳኔ መሰረትም ነፃ የተባሉት የዞን ዘጠኝ አባላት ከእስር የተለቀቁ ሲሆን በመደበኛው ወንጀል ሕጉ መሰረት ክሱን እንዲከላከል የተወሰነበት በፍቃዱ ኃይሉ በሃያ ሽህ በር ዋስትና ከእስር ተለቋል፡፡ ነገር ግን ‹በከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔ ቅር ተሰኝቻለሁ› በማለት ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በታህሳስ 04/2008 የተፃፈ ይግባኝ ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የወንጀል ችሎት ይግባኝ አቅርቧል፡፡ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤትም ከሳሽ በፅሁፍ አለኝ ያለውን ቅሬታ በቃል ሰምቶና የተከሳሾቹን ምላሽ በማዳመጥ ለነገ መጋቢት 20/2008 ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምን ሊከሰት ይችላል?
በነገው የፍርድ ቤት ውሎ ችሎቱ መዝገቡን መርምሮ የጨረሰ ከሆነና ‹ተጨማሪ ማስረጃ አያስፈልገኝም› የሚል ከሆነ ሶስት የተለያዩ ነገሮች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡
የመጀመሪያው ነገር ‹የስር ፍርድ ቤቱ የሰጠው ውሳኔ ተገቢ ነው› በማለት የስር ፍርድ ቤቱን ውሳኔ በማፅናት የተከሳሾቹን ነፃነት ማስጠበቅ ነው፡፡
ሁለተኛው ሊከሰት የሚችለው ጉዳይ ደግሞ ከመጀመሪያው በተቃራኒ የከሳሽ ቅሬታን ተቀብሎ የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በመሻር ‹ተከሳሾቹ ክሳቸውን እንዲከላከሉ› የሚል ውሳኔ በመስጠት ተከሳሾቹን ዳግም ወደ እስር ቤት መመለስ ነው፡፡
ሶስተኛው የሚጠበቀው ጉዳይ የስር ፍርድ ቤት 2ኛ ተከሳሽን በፍቃዱ ኃይሉን የሚመለከት ሲሆን፤ በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕጉ መሰረት አንድ ሰው በተመሳሳይ ጉዳይ በተመሳሳይ ጊዜ በሁለት የተለያዩ ፍርድ ቤቶች ክሱን ሊከታተል ስለማይገባ ከሕግ አግባብ ውጭ በፍቃዱ ላይ የቀረበውን ይግባይ ውድቅ ያደርገዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
እኛም ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በማፅናት ይህ በመናገር ነፃነት ላይ የተሰነዘረን ጥቃት ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እልባት ይሰጠዋል የሚል ተስፋ አለን፡፡