>

ኮከቡ ሙሉጌታ ሲያበራ ይኖራል! [ከአንተነህ መርዕድ]

Ato Mulugeta Lule የምንወደውን አንጋፋ ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌን ካጣን ሁለተኛ ሳምንታችን ነው። ጋሽ ሙሉጌታ እንደ ባህር ተጠልቆ የማያልቀው እውቀቱና ልምዱን በአንደበቱ ፤ ለብዙዎቻችን አስተማሪ ለነፃነት ጠላቶችም ቅስም ሰባሪ የሆነው ጽሁፉ ዳግም በእጁ ላይጻፉ በሞት ቀዝቃዛ እጅ ተዳኝተዋል። ሞት ሊዳኛቸው የማይቻለው ግን ዘወትር ሺ ቅን ዜጎችን የሚያፈሩ ስራዎቹን ነው። የእሱ ሞት እኩያኖችን በያሉበት ካስደሰተው በላይ ለእውነተኛ ኢትዮጵያውያን መራራ ሃዘን ነው። ገና ብዙ ለማወቅ ስንጓጓና  ከገባንበት ጨለማ የሚያወጣን መሪና አስተማሪ በምንሻበት ሰዓት ነው ያጣነው።

ሙሉጌታ ሉሌ ስለታሪካችን፣ ስለነፃነት ጥማታችንና ስለብልሹው ፖለቲካችን ብዙ ብዙ ለማስተማር የደከመ እንጂ ስለራሱ ማንነት ለመተረክ ፍላጎቱ ስላልነበር ብዙዎቻችን የምናውቀ ሥራውን እንጂ እሱን አልሆነም። (በእሱ ስብዕና ዙርያ ለወድፊት በሰፊው ለመምጣት ቃል እገባለሁ)። በህይወት ዘመኔ አብሬው የቆየሁባቸውና የሠራሁባቸውን ወርቃማ ዓመታት የሚተካልኝ አላገኘሁም። ያ ወቅት “የጦብያ” ወቅት የሙሉጌታ ሉሌ ወርቃማ ወቅት ነበር። በሙሉ ኃይሉ አጠገቡ ያለነውንም፣ ህዝቡንም ያስተማረበት። በብዕሩ ብቻ ሳይሆን፣ መታሰርን፣ ህይወትን ለታላቅ ዓላማ መስዋዕት ማድረግን፣ መንገላታትን ሁሉ በተግባር ያሳየበት ጊዜ ነው።

በጠባቡዋ ማዕከላዊ ውስጥ ከጀማሪ ወጣት ጋዜጠኞች ጋር ታስሮ የጣለው የመሸጋገርያ ድልድይ ነው የሱና የመሰሎቹን ፈለግ ተከትለው  የሚሠሩ ትንታግ ጋዜጠኞች አገሪቷ በአጭር ጊዜ እንድታፈራ ያስቻላት። የሙሉጌታን ፈር የተከትሉትን ህዝባችን ብቻ ሳይሆን ዓለም ያወቃቸውን እስክንድር ነጋን፣ ተመስገን ደሳልኝን፣ ውብሸት ታዬን፣ ርዕዮት ዓለሙን፣ በዓለም ዙርያ ዌቭሳይቶችንና ሬድዮ ጣብያ ከፍተው አፈና የሚታገሉትን፣ ኢሳትን፣ ማህበራዊ ገፆችን፣ ጋዜጣና መፅሄቶችን ያየ የጋሽ ሙሉጌታ ሉሌን አሻራ ያገኛል።ታስረው ሲወጡ የበለጠ ቆራጥ፣ ለሙያው ያደሩ ወጣቶች እየበረከቱ መሄድ ያደናገጠው ወያኔ ነፃ ሚድያን ለማዳፈን ሁሉንም ጨካኝ መንገድ ተጠቅሟል። በተለይ አቶ ሙሉጌታ ላይ ያነጣጠረው አዳጋ ከሁሉም የከፋ መሆኑን በጊዜው ከጎኑ ያለነው ብንረዳም እስከመጨተሻ ሊጋፈጥ ቆርጦ ስለነበር ባጭር ጊዜ ጨርሰን ልናጣው እንደምንችል ሰግተን ነበር። ስደቱን ባይወደውም ጊዜ ሰጠው፣ እንደ ፍላጎቱና አቅሙ መሥራቱን ቢያጓትትበትም በዝግታ ማድረግ የቻለውን ሁሉ አድርጓል። ያ ወርቅማው የጦቢያ ዘመን ዳግም መጥቶ በሙሉ አቅሙ ሊያገለግል በኢሳት ብቅ ሲል ደግሞ ሰምተን ሳንጠግበው፣ ማስተማሩን ሳያገባድድ፣ ገና ገና ብዙ ስንጠብቅ ሞት ቀደመን። በኢሳት ዙርያ ያሉ ወንድሞቼና እህቶቼ ጋሽ ሙሉጌታን ቀርበው ማወቅ ሲጀምሩ፤ ሙያውንና ስብዕናውን የራሳቸው ለማድረግ ሲድክሙ በድንገት ሲያጡት የተሰማቸውን ስሜት እኔና ጓደኞቼም ጦቢያ ላይ ስናጣው የተሰማንን ስለማውቅ የጉዳታቸውን ጥልቀት እጋራለሁ። ከእሱ ጋር የምናሳልፋት እያንዳንዷ ደቂቃ ዋጋዋ ምን ያህል ከፍ ያለ መሆኗ ጎልታ የምትታየው ስናጣው ነው።

ይህን ዘመን ተሻጋሪ ጀግና ጋዜጠኛ፣ ታሪክ አዋቂና የፖለቲካ ተንታኝ  ሁላችንም ስንወደው የሚፈሩትና የሚጠሉት አምባገነኖች ብቻ ሳይሆኑ በማንነታቸው ላይ ችግርና ጠባሳ ያለባቸው ድንኮችም ናቸው። ለአገር፣ ለታሪክ በተለይም ለሰብአዊ ፍጡር የሚሳሳን ጋሽ ሙሉጌታን ከሙያ ባልደረባው ከበዐሉ ግርማ አሟሟት ጋር አዳብለው ጥላሸት ሊቀቡት የዳዱት ግለሰቦች በስራቸው ራሳቸውን አጋልጠዋል። “በገዛ መብራቷ እርቃኗን ዐዩባት” እንደተባለው ወያኔ ቢቻለው ኑሮ ሊጠቀምበት የማይሳሳበትን ወንጀል ሊወነጅሉ ሞከሩ።  የአድርባይነት ቫይረስ ደሙ ላይ ያለበት በእድሜም ብዛት አይለቀውምና በሰብዕናው ሳይሆን በጽሁፎቹ አከብረው የነበረው አበራ ለማ “በፖለቲካ” ስደተኝነት ከሚኖርበት ኖርዌይ  ወደ ኢትዮጵያ ሲሄድ ለወያኔ እጅ መንሻ ያቀረበው የመስዋዕት በግ ሙሉጌታ ሉሌን ነበር። እንኳን ለህዝቡ ለወያኔም ውሃ አልቋጠረለትም። ከሁሉም በላይ ደግሞ ሰሞኑን  የጋሽ ሙሉጌታ አስከሬን ሳይቀዘቅዝ፣ አፈርም ሳይነካ ተሽቀዳድሞ ታሪኩን ለማጠልሸት ለወንድሞቹ ለህወሃቶች እጅ መንሻ ያቀረበው የኢትዮ ሚዲያ ባለቤት አብርሃ በላይ ነው። ከውሃ ደም ይወፍራል እንዲሉ ከሙያ አባቱና በክፉ ቀን ከደረሰለት ከሙሉጌታ ሉሌ ለአብርሃ የሚቀርቡት አንድ ሃሙስ የቀራቸው ወያኔዎች መሆናቸውን ከትንንሽ ምልክቶች አልፎ ግልፅ ሥራው መስክሯል።

ዛሬ ይሄን ለምን አነሳህ የሚል ቅን ጠያቂ ይኖር ይሆናል። ትናንት ጋሽ ሙሉጌታ ነበር። ስለራሱ ራሱ መናገር ይችል ነበርና ምንም ማለት አላስፈለገኝም።  “ለምን አንድ ነገር አትላቸውም?” ስንለው “ከላካቸው ጋር እንጂ ከተላላኪ ጋር አፍ አልካፈትም” ሲል በኩራት ንቆ ትቷቸው ነበር። ዛሬ ግን ጋሽ ሙሉጌታ ታሪክ ነው። ታሪክን የሚያጥለሽ እቡይ ብቅ ሲል ደግሞ ልንከላከል ግድ ይለናል። ሙሉጌታ ሉሌ እንደ ንጋት ኮከብ ከፍ ብሎ በኢትዮጵያ አድማስ ላይ እያበራ ነው። መቃብር ውስጥ ያለው ስጋው እንጂ ሥራው ከመቃብር በላይ ወጥቷል። ምድር ያልለቀቁ ድንኮች ብርሃኑን አይከልሉም። በሁሉም ዘርፍ ያለው ኢትዮጵያዊ በተለይም ጋዜጠኛው ከአንጋፋው ሙሉጌታ ሉሌ የምንማረው ነገር ቢኖር ሥራችን በእውቀት ላይ የተገነባ፣ በመረጃ የተደገፈ፣ የአገርንና የህዝብን ጥቅም ማዕከል ያደረገ ከውስኑ የህይወት ዘመናቸን አልፎ ዘመናት የሚሻገር አስተዋፆ ማበርከት ነው። በሙያው ላይ የተከፈለው መስዋዕት ቀላል አይደለም። የነፃነቱ ባለቤት እንዲሆን የተደከመለት ህዝብ አሁንም መከራው አላበቃም። አምባገነኖችም መዳከም ጀመሩ እንጂ አልወደቁም።  እንኳን ዛሬ ህዝቡ ዴሞክራሲይዊ መብቱ መከበር ቢጀምርም ድሉን ነቅቶ የመጠበቅ ሃላፊነት የነፃ ሚድያ ነው። ለዚህም ነው የሙሉጌታ ሉሌ ሥራ ዘላለማዊ የሚሆነው። ኢትዮጵያ በልጆቿ ነፃነቷን ትጎናፀፋለች!

Filed in: Amharic