>

የዶ/ር ዳኛቸው አሰፋን መኖሪያ ቤት በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ዩኒቨርሲቲው እንደሚያሽገው አሳወቀ [ዶክተር ዳኛቸው የጻፉትንም ይዘናል]

Dr. Dagnachews letterየዶ/ር ዳኛቸው አሰፋን መኖሪያ ቤት በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ዩኒቨርሲቲው እንደሚያሽገው አሳወቀ፡፡ እርሳቸው ለዩኒቨርሲቲው የቤቶች አስተዳደር ኃላፊ ስለእሸጋው ትዕዛዝ የመለሱበት ግልጽ ደብዳቤ እና የዩኒቨርሲቲው የዕዝ ደብዳቤ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

ጥቅምት 2 ቀን 2008 ዓ.ም.

ለአቶ ብርሀኑ አበራ፡
የቤቶች አስተዳደር፤

ግልፅ ደብዳቤ!

በቅድሚያ የከበረ ሰላምታዬን እያቀረብኩ፤በአካል በተገናኘንባቸው ጥቂት አጋጣሚዎች ላሳዩኝ ትህትና የተመላበት አቀራረብ በእጅጉ ላመሰግንዎ አወዳለሁ፡፡

ከእርስዎ ቢሮ መስከረም 28 ቀን 2008 ዓ.ም. “ቤት እንዲያስረክቡ የተሰጠ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ” በሚል ርዕስ በተለመደው አካሄዳችሁ በምኖርበት አፓርትመንት በበር ሥር የተወረወረ ደብዳቤ አገኘሁ፡፡
መልዕክቱን በጥሞና ከተመለከትኩት በኋላ ሦስት መሠረታዊ ሀሳቦች ነቅሼ በማውጣት የሚከተለውን ምላሽ ማቅረብ ተገቢ መስሎ ታይቶኛል፡፡ እነዚህም ነጥቦች፡- (ሀ) “ውድድር”፣ (ለ) “ውዝፍ ኪራይ”፣ እና በመጨረሻም (ሐ) “ማሸግ” የሚሉትን ይመለከታል፡፡

ውድድር፡-
ከሁሉ አስቀድሞ “የዩኒቨርሲው ቤት በውድድር እንደሚሰጥ ይታወቃል” የሚለው የደብዳቤው ሀረግ በጣም አሻሚ እና ከእውነት የራቀ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ይህንንም እንድል ያስገደደኝ ሦስት ዐበይት ሀኔታዎች ስላሉ ነው፡፡

አንደኛ፡- እዚህ አፓርትመንት እንድኖር የተደረገው በውድድር አሸንፌ ሳይሆን፤ የፍልስፍና ዲፓርትመንት ኃላፊ የነበሩት ዶ/ር በቀለ ጉተማ ቤት እንድሚያስፈልገኝ ተረድተው፤ በጊዜው የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ለነበሩት ፕ/ር አንድርያስ እሸቴ በደብዳቤ በማሳወቅ በዩኒቨርሲቲው ይሁንታ ቤት እንዳገኝ ተደርጓል፡፡

ሁለተኛ፡- እርስዎ “ውድድር” የሚለውን ቃል ሲጠቀሙ፤ የሥያሜዎ መስፈርት፤ ሃይማኖትን፣ ጾታን፣ ብሔርን፣ የትምህርት ደረጃን፣ ወይም የሥልጣን እርከንን አሊያም ሌላ ጉዳይ ስለሚጠቁም፤ የእርስዎ አባባል የትኛው መስፈርት ላይ በቀዳሚነት እንደተመረኮዘ ግልጽ አይደለም፡፡

ሦስተኛ፡- በሦስት ዓመታት ቆይታ ትዝብቴ፤ በእርግጠኝነት ለማለት የምችለው፤ የዩኒቨርሲው የቤት አሰጣጥም ሆነ የማስለቀቅ እንቅስቃሴ፤ በዋናነት ሥልጣንን እና ብሔርን ያማከለ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ለማሳያ ያህል፤ በእነዚህ ሦስት ወራት ውስጥ በፕሬዚዳንት አድማሱ ጸጋዬ ትዕዛዝ ከገቡ ሦስት ቤተሰቦች መካከል፤ቢያንስ ሁለቱ የእርሳቸው “የወንዝ ልጆች” ልንላቸው የምንችላቸው ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ፤ ከዩኒቨርሲቲው ጋር የአገልግሎትም ሆነ የሥራ ግንኙነት የሌላቸው፣ ግንኙነታቸውንም ያቋረጡ ግለሰቦች ለረጅም ጊዜ ምንም ሳይባሉ ለዓመታት እንዲኖሩበት መደረጉን፤የአፓርትመንት ነዋሪ መምህራኑ የሚያውቁት ዕውነታ ነው፡፡

ውዝፍ ኪራይ፡-
ይህን በሚመለከት ከዚህ ቀደምም እንደገለጽኩልዎት፤በእኔ በኩል ያለብኝን የቤት ኪራይ ለመክፈል ዝግጁ መሆኔ ግልጽ ነው፡፡ እንዲያውም እርስዎን በአካል ባገኘሁበት ወቅት፤ ቁልፉን ሳስረክብ ያለብኝን የቤት ኪራይ እንደምከፍል እና ከእርስዎም ቢሮ ደረሰኝ ሳይውል ሳያድር እንዲሰጠኝ የምጠብቅ መሆኔን መግለጼን አይዘነጉትም፡፡ይሁን እንጂ፤ ዩኒቨርሲቲው “ውዝፍ የቤት ኪራይ አለብህ” እንዳለኝ ሁሉ፤ እኔም ከስምንት ወራት በፊት በተለያዩ ዲፕርትመንቶች ያስታማርኩበትን ውዝፍ ክፍያ እንዳልተሰጠኝ ቢያስቡበት መልካም ነበር፡፡ ሆኖም ዩኒቨርሲቲው ያልከፈለኝ ሂሳብ አለኝ በሚል እሳቤ እኔ ካለብኝ ግዴታ ወደ ኋላ እንደማላፈገፍግ ላሳውቅዎት እወዳለሁ፡፡

ማሸግ፡-
“ማሸግ” በሚል የመጣው ትዕዛዝ፤ መንስዔው ከእኔ መልቀቅና አለመልቀቅጋር የተያያዘ ሳይሆን፤ስለዩኒቨርሲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር አድማሱጸ ጋዬ፤ባለፈው ሳምንት በጋዜጦች ላይ ላቀረብኩለት ትችት የበቀል እና የእብሪት አጸፋ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ በጋዜጦቹ ላይ እንደገለጽኩት፤ ፕሬዚዳንቱ ትንሽ ሂስ ሲቀርብባቸው የተቻላቸውን ያህል ጉዳት ለማድረስ ወደ ኋላ እንደማይሉ ማረጋገጫም ነው፡፡ ከዚህ በፊትም በጽሑፍ እንዳቀረብኩት፤ የማጥቃት አቅማቸው ውስን ሆኖባቸው እንጂ፤ ፍላጎታቸው ቤት በማሳሸግ ብቻ የሚቆም ሳይሆን እኔንም ለማሳሸግ ወደ ኋላ አይሉም ነበር፡፡
“ማሸግን” በሚመለከት እኔን የሚገርመኝ፤ ትልቅ የሕግ ዲፓርትመንት ባለበት ግቢ ውስጥ፣ በተጨማሪም እርሳቸው እራሳቸው የሕግ አማካሪ እያላቸው፤ ከማናቸውም የሕግ አገልግሎት ምክር ሳይቀበሉ ካለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በዘፈቀደ የሚከናወን ጉዳይ እንዳልሆነ አለመረዳታቸው የሚያሳዝን ነው፡፡

ለማጠቃለል ያህል፡- ከዚህ በፊት “በ15 ቀናት ውስጥ ቤቱን አስረክበህ ውጣ” ስባል፤ እንደማንኛውም ዜጋ ሕጉ የሚፈቅደውን የሦስት ወራት የቤት መፈለጊያ ጊዜ ተሰጥቶኝ እንደምለቅ አሳውቄ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን፤ ባልኩት ጊዜ አብዛኛው ንብረቶቼን፤ ይህ “ይታሸግ” የሚለው ደብዳቤ ከመድረሱ በፊት ማውጣቴን አጎራባቾቼ እና የግቢው የጥበቃ ክፍል የሚያውቀው ሀቅ ነው፡፡ ቢሮው ፕሬዚዳንቱን ለማስደሰት ማሸግ ካስፈለገውም የሚያሽገው ባዶ ቤት መሆኑን እንዲያውቁት እፈልጋለሁ፡፡

ያም ሆነ ይህ፤ እንዲህ ባለ ጥቃቅን ጉዳይ ጊዜዬን ማባከን የማፈልግ ሲሆን፤ ከፊታችን ያሉ በርካታ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ ትግሉን መቀጠልን መርጫለሁ፡፡

Filed in: Amharic