>

"ሁልግዜ ለምንድነው ስከርቭ የምታረገው???"

ሃና ረጋሳ

ፌስቡክ ካፈራልኝ ምርጥ ወዳጆች አንዱ ተመስገን ደስአለኝ ነው።Temesgen Desalegn - photo#massbr ከሶስት አመት በፊት ነበር ተመስገንን በአካል ያገኘሁት ያኔ ይመስለኛል ፍትህ ለይ እየሰራ ነበር እናም ላገኘው እንደምፈልግ ስነግረው ያለምንም ማመንታት ነበር ስልኩን የሰጠኝ።
ታድያ በአንዱ ቀን ተደዋወልን እና ግንፍሌ አካባቢ በሚገኝ አንድ ትልቅ ሆቴል በረንድ ለይ እንድንገናኝ ተቀጣጠርን። እኔ በቀጠሮው ቦታ ስደርስ ተመስገን ከኔ ቀድሞ ነበር የተገኘው ታድያ ተመስገንን ከጠበኩት ውጭ ሆኖ ነበር ያገኘሁት። ተመስገን ሲበዛ በጣም ተጫዋች እና ትሁት ልጅ ነው ብ በጣም ከመግባባታችን የተነሳም ብዙ ግዜ የማውቀው ያክል ነበር የተሰማኝ።
በጣም የገረመኝ ነገር ግን እኔና ተመስገን በተቀመጥንበት ከጀርባ ሶስት ሰዎች ያለምንም ማቋረጥ በዝምታ ወደ እኛ ነበር የሚመለከቱት ተመስገን የሰዎቹ እይታ እኔ እንዳልተመቸኝ ሲያውቅ “ሀና ምንም አትጨነቂ እኔ የለመድኳቸው ናቸው የትም ስንቀሳቀስ አብረውኝ አሉ እንደውም ከመልመዴ የተነሳ ከሌሉ ይደብረኛል” አለኝ እኔም በጣም ተገረምኩ እንዴት አንዲትን ትልቅ ሀገር የሚመራ መንግስት እንዲህ ወደ ታች ወርዶ በጀት መድቦ ግለሰቦችን ቀጥሮ አንድ ጋዜጠኛ ሲወጣ ሲገባ ሲከታተል ይውላል??????
ከተመስገን ጋር በቆየንባቸው ሶስት ያህል ሰአታት ስለ ብዙ ነገር ተጨዋውተናል ተመስገን በውጭ ሳውቀው የበለጠ ለሱ አድናቆቴ እና አክብሮቴ እንዲጨምር ነው ያረገው በጣም ሲበዛ እራሱን የማይቆልል እና ግልፅ እና ሀገሩን የሚወድ ኢትዮጲያዊ ሆኖ ነበር ያገኘሁት።
በነበረን ግዜ ያለ ማቋረጥ ብዙ ጥያቄ ጠይቄው ነበር እሱ ራሱ ተገርሞ እንዲህ አለኝ “እንዴ ሀና እኔ ነኝ ጋዜጠኛ አንቺ ???” አለኝ በመገረም። እኔም የምፈልገውን ዋና ጥያቄ አነሳ በሚል እሳቤ እንዲህ አልኩት።
“አይ እኔም እኮ ዝም ብዬ እሞነጫጭራለሁ እንደውም ቦርሳዬ ውስጥ አለ እስቲ እየው” ብዬ ከቦርሳዬ ወረቀቶች አውጥቼ አቀበልኩት ከ20 ደቂቃዎች ላላነሱ ግዜያት ካነበበ በዋላ ካቀረቀረበት ቀና ብሎ እንዲህ አለኝ ” ጥሩ ነው ግን እኛ እንዲህ የምንገላታለትን ሞያ መቀላቀለ ትፈልግያለሽ???” አለኝ።
እኔም አዎንታዬን ጭንቅላቴን በመነቅነቅ ገለፅኩለት።
ከዛም ቃልበቃል እንዲህ ነበር ያለኝ
“አየሽ ምንግዜም ከመፃፍሽ በፊት በደንብ አንብቢ ለምትሰሪው ነገር ሁሉ ማስረጃ ይኑርሽ በቃ እነዚን ስታሟይ ምንም ፍርሀት የሚባል ነገርም ካንቺ ጋር አይኖርም” ነበር ያለኝ። ተመስገን እውነቱን ነበር የሚናገረውንም እንደሚኖር ከፊቱ ገፅ ለይየሚነበበው በራስ መተማመን እና መረጋጋጋቱ ምስክር ናቸው።
ተመስገን ባወራንባቸው ሰአታት ከአፉ የማይነጥለው አንድ ሰው ነበር እስክንድር ነጋ ስለ እሱ አውርቶ አይጠግብም በእውነት በኛ ሀገር ብዙ ግዜ በአንድ ዘርፍ ለይ ያሉ ሞያተኞች ሲተቻቹ እንጂ እንዲህ በፍፁም ፍቅር ሲከባበሩ ማየት ብዙ አይቼ አላውቅም።
ተመስገንን ከጠየቁት ጥያቄዎች ውስጥ አንዱ ሁልጊዜ ስለሚለብሰው ስከርቭ ነበር።
“ሁልግዜ ለምንድነው ስከርቭ የምታረገው???” ብዬ ስለው ከረጅም ሳቅ ብዋላ እንዲህ ሲል መለሰልኝ
ምንም የተጋነነ ምክንያት የለውም ግን ለግዜው አልነግርሽም” አለኝ። ከዛን ቀን በዋላ ተመስገንን በአካል አግንቼው አላውቅም የፍርድቤት ቀጠሮ በነበረው ቀን ሁሉ ግን እየደወልኩ እጠይቀው ነበር ጥቅምት ሁለት ሁለት ሺህ ሰባት ደሞ የመታሰሩን ዜና ሰማሁ።
በእውነት ስለ ተመስገን ለመናገር ቃላት የለኝም ግን እንዲህ እለዋለሁ።
አንተ በእስር ብትሆንም እንኳን ብዙ ሺህ ሚሊዮን ተመስገኖችን ፈጥረሀል እና ልትኮራ ይገባል ዛሬም ብርቱው እና ጠንካራ መንፈስህን በብዙዎች ልብ አስርፀሀል እና ሀሴት ልታደርግ ይገባሀል።
ይህ ትውልድ ምን ያገር ፍቅር አለው ብለው ለሚሉ ሰዎች አንተ የእውነት ለሀገር በመኖር መልሰሀልና እናመሰግናለን።
ተሜ እኛ በልባችን አንግሰን ጅግነትህን ከመሰከርን ቆይተናል በአደባባይ የምናመሰግንህ እና ጅግንነትህን የምንመሰክርበት ግዜም ሩቅ አይመስለኝም እስከዛው ልኡል እ/ር እድሜ እና ጤና አብዝቶ ይስጥህ።


“ኢትዮጲያ ለዘለአለም ትኑር”

Filed in: Amharic