>

‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባልነትህን የማታቋርጥ ከሆነ አንተን ማስደፋት ቀላል ነው!›› [የደብር ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ ጽ/ቤት ኃላፊ]

Samuel Aweqe‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባልነቴን አንተ አታስቆመኝም፡፡ አገሬም ኢትዮጵያ ነው! ከኢህአዴግ ጋር ስታገልም ይህን ሁሉ አውቃለሁ፡፡ የፈለግከውን ማድረግ ትችላለህ!››

ወጣት ሳሙኤል አወቀ

ሳሙኤል አወቀ ሚያዝያ 3 ቀን 2006 ዓ.ም. ቅፅ 1 ቁጥር 8 የነገረ ኢትዮጵያ እትም ላይ በምስራቅ ጎጃም ዞን አስተዳደር በተለይም የደብረማርቆስ ከተማ ባለስልጣናት የሚደርስትን በደል ገልጾ ነበር፡፡ በዚህ ፅሁፉ ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባልነትህን የማታቋርጥ ከሆነ አንተን ማስደፋት ቀላል ነው፡፡›› እንዳሉት አስፍሯል፡፡ እሱም ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባልነቴን አንተ አታስቆመኝም፡፡ አገሬም ኢትዮጵያ ነው፡፡ ከኢህአዴግ ጋር ስታገልም ይህን ሁሉ አውቃለሁ የፈለግከውን ማድረግ ትችላለህ!› ብሏቸው ነበር፡፡ ሙሉውን ፅሁፍ ያንብቡት፡፡

ለፍትህ ስርዓቱ ፍትህ ያስፈልጋል

ሳሙኤል አወቀ

(ሚያዝያ 3 ቀን 2006 ዓ.ም.)

ባህር ዳር ወንዱ ህንጻ

ጳጉሜን 2 ቀን 2002 ዓ.ም ከዛሬ ሶስት ዓመት በፊት ከአንድ የፍትህ ባለስ ልጣን ጋር ቢሮው ውስጥ ኢ-መደበኛ ውይይት በማድረግ ላይ ነበርን፡፡ አፈሩን ገለባ ያድርግለት ያ ባለስልጣን አሁን በህይወት የለም፡፡ ሰውየው ወጉን ሲጀምር ያነሳልኝ ስለ ህወሓት/ኢህአዴግ የፖለቲካ ሁኔታና ስለኢትዮጵያ እጣ ፈንታ ነበር፡፡ “አየህ እኔ ድሮ በደርግ የመጀመሪያዎቹ ዘመን ከአስመራ ዩኒቨርሲቲ በህግ ዲፕሎማየን አግኝቻለሁ፡፡ ኤርትራዊ ነኝ፡፡ ህወሓት/ኢህዴግ ኢትዮጵ ያን በዘር ፖለቲካ አጥሮና ከልሎ ሳይከፋፍለን ኤርትራም ሳትገነጠል ማለት ነው፡፡ አስመራ ዩኒቨርሲቲ ስማርም በኢትዮጵያዊነቴ እንጂ በኤርትራዊ ነቴ አይደለም፡፡ አሁን ያ ሁሉ ቀርቷል፡፡ ለበርካታ አመታት በአማራ ክልል ፍትህ ቢሮ ከዞን የመምሪያ ሀላፊ እስከ ክልል ፍትህ ቢሮ በሀላፊነት እየሰራሁ ነው፡፡ ነገር ግን ሙያየን ስገመግመው የምሰራውና የተማርኩት የህግ እውቀት ተገናኝቶልኝ አያውቅም፡፡ ምክንያቱም በወያኔ ስርዓት የፍትህ ስርዓቱ ለአገዛዙ የአፈና መዋቅርነት የተዋቀረ ነው፡፡ ዜጎች በመንግስት ባለስልጣናት ወንጀል ተፈጽሞባቸው ወደ እኔ አቤቱታ ይዘው ሲመጡ እና መፍታት ሳልችል ስቀር እንቅልፍ ሲነሳኝ ያድራል፡፡

እንግዲህ የኢትዮጵያ የፍትህ ስርዓት ይህን ይመስላል፡፡ ‹‹አየህ! አንተ ወጣት የህግ ባለሙያ ነህ፣ እግዚአብሄር ረጅም ዕድሜ ከሰጠህ የፍትህ ስርዓቱን የመለወጥ ተስፋ አለህ፡፡ ምክንያቱም የወያኔ ስርዓት ማክተሙ የኢትዮጵያ ህዝብና ኢትዮጵያ ግን መቀጠላቸው የተፈጥሮ ህግ ነውና እንግዲህ በአሁኑ ሰዓት የህግ የበላይነት ሳይሆን የባለስልጣናት የበላይነት ነግሷል፡፡ ፍትህ የለም፡፡ ዳኝነት የለም፡፡ ነገር ግን የፍትህ ተቋማት፣ ፍ/ቤት እና ፖሊስ ለይስሙላ ተቋቁመዋል፡፡ ይህ ታዲያ ፍትህ ነው እንዴ? አሁን የተቀመጥንበትን ህንጻ ኢህአዴግ ሳይሆን የሰራው በኢትዮጵያ ህዝብ ግብር ነው፡፡ በዚህ ህንጻ ውስጥ ግን ዳኞችና ዐ/ህጎች ታያለህ፡፡ እኒህ ባለሙያዎችም ለህዝቡ ፍትህ ሳይሆን በደልን እያበባሱ ነው፡፡ የአማራ ክልል ፕሬዝዳንት ክቡር አቶ አያሌው ጎበዜ ይህንን ህንጻ “ወንዱ ህንጻ” ብለውታል፡፡ ‹‹በዚህ ህንጻ ውስጥ ምንም አይነት ህግና ህጋዊነትም ሆነ ፍትሀዊ የፍትህ ስርዓት አይቼ አላውቅም፡፡

ወያኔ ግን ዳኞችንና ህጎችን በዚህ ህንጻ ውስጥ በምቾት አስቀምጦ ህዝቡን እያስለቀሰ የህግ የበላይነት እያለ መልሶ ያደነቁረናል፡፡ በቀላሉ እንኳ በግል በጥብቅና ሙያ በነጻነት ለመስራት ጥብቅ የአፈና መዋቅር ተዘጋጅቷል፡፡ የፍትህ ሰዎች ጥብቅናን የሙስና መቀባበያ መረብ እንጂ የፍትህ ተቋም አድርገው አያዩትም፡፡ ሲፈልጉ ያስራሉ፣ ሲፈልጉ ፈቃድ ይነጥቃሉ፡፡ ጠበቃው ዳኞችን ያውቃል አያውቅም ለሙስና ስርዓቱ ተባባሪ ነው አይደለም የሚለው፡፡ በሚስጢር ይጠናና በፍትህ ድለላው መረብ ውስጥ እንዲገባ ተደርጎ ከተጠረነፈ በኋላ መንግስት ለህዝቡ መልሶ ፕሮፖጋንዳውን ይነፋል፡፡
‹‹እኔ የማውቀው የፍትህ ስርዓት እንግዲህ ይህ ነው፡፡ አንተ ካወቅከው እወቀው ነገር ግን ለህግ የበላይነት መከበር እና ለፍትህ ስርዓቱ መሻሻል በወጣትነት እድሜ የምትታገለውና የምትከፍለው መሰዋትነት እንዳለ አውቀህ ተስፋ ሳትቆርጥ ኮረኮንቻማውን ጉዞ ብትቀጥል መልካም ነው፡፡ ከህሊና ወቀሳም ሆነ ከታሪክ ተጠያቂነት ትድናለህ፡፡ ለሚቀጥለው ትውልድም ህግን፣ ህጋዊነትን እና ተቋማዊ አሰራርን ትመሰርት ይሆናል፡፡ አሁን እኔ አንተን ልመክርህ እንጂ እንድንለያይ አልፈልግም፡፡ ምክሬን ብትቀበል ግን መልካም ነው ጨርሻለሁ፡፡›› አለኝና ሮዝማን ሲጃራውን እና ክብሪቱን ከኪሱ አውጥቶ ተሸከርካሪ ወንበሩ ላይ ወደ ኋላ ተንጋሎ ሲጃራውን ሲያትጎለጉል እኔም ያነን ያማረና የተንጣለለ “ወንዱ ህንጻ” ለቅቄ የድሀ ጠበቃ (streat lawyer) የተባለውን መጽሀፍ ከባለስልጣኑ ፊት አንስቼ ወደ ጣና መናፈሻ እየበረርኩ ስሄድ ሌላ አንድ ጓደኛየን አገኘሁትና ስለ ፍትህ ስርዓቱና ስለ ጥብቅና ስራ አንስቶልኝ ስንወያይ ፍትህ የለ፣ ህግ የለ ይህ ሁሉ የጠበቃ፣ የዐ/ህግ፣ የዳኛና የፖሊስ ጋጋታ ለዚህች አገር ምን ይጠቅማታል? ሲል ጥያቄ ሰነዘረልኝ፡፡ እኔም ይህ ጓደኛዬንና የባለስልጣኑን አገራዊ እሳቤዎች በማብሰልሰል የተበላሸው የፍተህ ስርዓት ተቀይሮ ፍትህና የህግ የበላይነት ይሰፍን ዘንድ አገራዊ ግዴታየን መወጣት እንዳለ ብኝ የለውጡም አንድ አካል መሆን እንዳለብኝ ያለማቅማማት ወሰንኩ፡፡
አቤት ጊዜው እንዴት ይነጉዳል እኛ ግን ባለንበት ተከንችረን በህግ አምላክ ፍትህ፣ ፍትህ፣ፍትህ እንዳልን ይኸው መንቀሳቀስ አቅቶናል፡፡ ይህንን የኢህአዲግ አስማት አብዮታዊ ዴሞክራሲ ተብየው ከመታገል ውጭ ሌላ ምን አማራጭ ሊኖረን ይችላል፡፡ ውድ አንባቢዎች ለመግቢያ ያክል ይህን ካወራን አሁን ወደ ዋናው የጽሁፉ ዓላማ ልመልሳችሁ፡፡

‹‹ህገ መንግስቱ አያድንህም››

ታህሳስ 29 ቀን 2006 ዓ.ም ደብረ ማርቆስ የምስራቅ ጎጃም ዞን ፍትህ መምሪያ ሀላፊ የሆኑት የወያኔ ካድሬ እኔን የደብር ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ ጽ/ቤት ሀላፊው አስገድዶ ከቢሯቸው ድረስ እንዲያቀርበኝ ባስተላለፉት ትዕዛዝ መሰረት ከጠዋቱ 4፡00 ሰዓት ሲሆን ጸሀፊዋን አስፈቅጀ ወደ ቢሯቸው ገባሁ፡፡ ሰውየውም እንደ መብረቅ በሚፈነዳ የጩኸት እና የቁጣ ድምጽ ለምን እንደ ጠሩኝ እንኳ ሳያስረዱኝ የበቃቸውን ያክል ቢሯቸውን ዘግተው ዘለፋና ቀፋፊ ስድባቸውን ከዘበዘቡ በኋላ (የእርሳቸውን ስድብ መጻፍ እንደ እርሳቸው ባለጌ መሆን ነውና አልፈዋለሁ)፡፡ ስድባቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባልነትህን የማታቋርጥ ከሆነ አንተን ማስደፋት ቀላል ነው፡፡ ያለ ምንም ጥያቄ ጠፍንጌ አስሬ እስር ቤት እወረውርሃለሁ እንዲሁም የጥብቅና ፈቃድህን ነጥቄ ሰንክዬ እስቀምጥሃለሁ፡፡ የማታርፍ ከሆነ አገር ለቀህ ውጣ ይህን ጉዳይ ለሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ወይም ለፓርቲህ ብትገልጽ ህገ-መንግስቱ አያድንህም፡፡ አሁን በአስቸኳይ ቢሮዬን ለቅቀህ ውጣ ከሰዓት ማኔጅመንቱን ሰብስቤ ስለምጠብቅህና ምንም አይነት ምላሽ ከአንተ አሁን አልፈልግም፡፡››
እኔም ምንም እንኳ ሰውየው ባይሰሙኝም ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባልነቴን አንተ አታስቆመኝም አገሬም ኢትዮጵያ ነው ከኢህአዴግ ጋር ስታገልም ይህን ሁሉ አውቃለሁ፡፡ የፈለግከውን ማድረግ ትችላለህ!›› ብዬ ጥየው ወጣሁ፡፡ ከሰዓት በኋላ ከሰዓትም በቀጠሮዬ መሰረት ወደ ቢሯቸው ስሄድ ማኔጅመንቱን ሰብስበው አገኘኋቸው፡፡ እርሳቸውም ለደቂቆቻቸው ‹‹ይህንን ልጅ ከየት እንደመጣ ታሪኩን ሁላችንም እናውቃለን፡፡ አሁን ልሰበስባችሁ የቻልኩት ለፍትህ ስርዓቱ አደገኛ በመሆኑ እና በመንግስት ላይ እምነት ስለሌለው በአስተያየት መስጫ መዝገብ ላይም ሳይፈቀድለት እየጻፈ ዳኞችን አላሰራ ስላለ እርምጃ ለመውሰድ ነው፡፡›› ሲሉ አሳሰቡ፡፡ ከዛ በኋላም አሽከሮቻቸው ድጋፍ እንዲሰጧቸው ጋብዘው ሁሉም ያሉትን ካሉ በኋላ ‹‹ሰማህ ከአስር ሌባ መሀል አንተ ንጹህ ሆነህ ሙስናን ልትታገል አትችልም፡፡ አሁን በወንጀል እንከስሃለን፡፡ ጨርሰናል ሂድ!›› አሉኝ፡፡
የክሱን ድራማ የስራ ክፍፍል ለማድረግ የተሰባሰቡት ዐ/ህግና ዳኛው ወደ ኋላ ሲቀሩ ትቻቸው ወጣሁ፡፡ የክሱ ድራማ ጅማሮ ሁለት ዳኞች ከሳሽ በመሆን ሌሎች ደግሞ በምስክርነት በመሰለፍ ፖሊስ ምርመራውን ቀጠለ፡፡ ‹‹ፖሊስም በፍ/ቤት የአስተያየት መስጫ መዝገብ ላይ ሙስኛ እየተበላ ነው! በማለት ስም ስላጠፋህ ተከሰሃል ቃልህን ስጥ፡፡›› አለኝ እኔም ይህ ህገ- መንግስታዊ መብቴን የሚጥስ በመሆኑ ቃል ለመስጠት ፈቃደኛ አይደለሁም፡፡ በማለት ስመልስለት ለአንድ ሰዓት ያክል በፖሊስ ጣቢያ በእስር ላይ ከቆየሁ በኋላ በ1000 ብር ዋስ ልለቀቅ ችያለሁ፡፡ ጉዳዩንም ለፓርቲዬ በመግለጽ ዓለም እንዲያውቀው ተደርጓል፡፡ የክሱ ድራማ በዚህ ሳያቆም በደብረ ማርቆስ ከተማ ወረዳ ፍ/ቤት ተከፍቶ ሁለቱ ዳኞች እና ሁለት ጠበቆች በምስክርነት ፍ/ቤቱ በደራማ ችሎት ትወናው በቀን 22/07/2006 ዓ.ም ቀርቤ ይህ ፍ/ቤት በማኔጅመንት ተወያይቶና አቅዶ የተወሰኑት ከሳሽ ሌሎች ምስክርና ዳኛ በመምሰል የቀረበብኝ ክስ ድራማ ስለሆነ በዚህ ፍ/ቤት ጉዳዩ ሊታይ አይችልም፡፡ በማለት ክርክሬን አቅርቤ ዳኛውም አምኖበት መዝገቡ ከተቋረጠ በኋላ ጉዳዩን ለምስራቅ ጎጃም ምስ/ዞን ከፍተኛው ፍ/ቤት አመልክቼ በፋ/ቁ/ 1198 በቀን 23/07/2006 ዓ.ም በዋለው ችሎት ከዐ/ ህግ ክስና ማስረጃ ተነስተን ጉዳዩን ስንመረምር በአንድ ወይም በሌላ መንገድ በስር ፍ/ቤት ጉዳዩ ቢታይ ገለልተኛ በሆነ መንገድ ክርክሩ ተመርቶ ማስረጃ ተሰምቶና ተመዝኖ ውሳኔ ይሰጣል ብለን ለማሰብ ተቸግረናል፡፡ በመሆኑም መዝገቡ በዚህ ፍ/ቤት ተዛውሮ ሊታይ ይገባዋል ሲል በድራማነት የቀረበውን ክስ አጋልጧል፡፡
ህገ-መንግስቱን የማይቀበል የፍትህ ስርዓት በኢፊዴሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 25 ላይ ሁሉም ሰዎች በህግ ፊት እኩል ናቸው፡፡ በመካከላቸውም ማንኛውም አይነት ልዩነት ሳይደረግ በህግ ፊት እኩል ጥበቃ ይደረግላቸዋል፡፡ በዚህ ረገድ በዘር፣ በብሄር፣ በቋንቋ፣ በፖለቲካ …ልዩነት ሳይደረግ ሰዎች ሁሉ እኩልና ተጨባጭ የህግ ዋስትና የማግኘት መብት አላቸው፡፡ የፍትህ ስርዓቱ ግን ይህንን ህገ-መንግስታዊ መብት የፈቀደው ለወያኔ ስርዓት እና ድርጅት ብቻ መሆኑን በህገ-መንግስቱ አንቀጽ 9 ህገ-መንግስቱ የህጎች ሁሉ የበላይ ህግ ነው፡፡ ህገ መንግስቱን የማክበና የማስከበር ግዴታ እና ለህገ-መንግስቱ ተገዥ የመሆን ሀላፊነት እንዳለ በግልጽ ቢደነግግም በፍትህ ስርዓቱ ውስጥ ያሉት የፍትህ ባለስልጣናት ሳይቀሩ ሲቢልና ፖለቲካዊ መብት በመጣስ ላይ ይገኛሉ፡፡

ሙስና እና የፍትህ ስርዓት

ሙስናን ለመከላከልና ህግ ለማስፈጸም የተቋቋመው የፍትህ አካል ከተቋቋመለት አላማ ውጭ በጣም በሚያሳፍር መልኩ ‹‹አንተ ስለ ሙስና ምን አገባህ? ከአስር ሌባ መሀል አንተ ንጹህ ሆነህ መኖር አትችልም፡፡›› ያለኝ የፍትህ መምሪያ ሀላፊው መሆናቸውን ሳስብ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ከመሞቱ በፊት ‹‹የመንግስት ሌቦች›› ተደራጅተው አገር እየዘረፉና ህዝብን እየጨቆኑ መሆኑን አምኖ ነበር፡፡ እኔ ግን እላለሁ የፍትህ ስርዓቱ የማፍያ ቡድን እየተሰገሰገበት የአፈና መዋቅር ስለሆነ ፍትህ ያስፈልገዋል፡፡ በዚህች አገር ከእንግዲህ ወዲያ የአገዛዝ የበላይነትን ሳይሆን የህግ የበላይነትን ለማምጣት መታገል እንዳለብንና የፍትህ ስርዓቱ ቆርጥሞ ሳይጨርሰን የተሰገሰጉትን አምባገነኖች ታግለን የወያኔን የሙስና ስርዓተ-መንግስት እና የአፈና ስርዓት ይለወጥ ዘንድ በቅድሚያ ለፍትህ ስርዓቱ ፍትህ ስላስፈለገው ፍትህን እፈልጋለሁ፡፡

ኑ እራሳችንን ነጻ እናውጣ!

Filed in: Amharic