>

ከሳሙኤል ወዲያስ?... [ሄኖክ የሺጥላ]

Samuel Aweqeጩህ ላለው ጉሮሮ

አልቅስ ላላው ካንጀት
ይበቃ ነበረ የ-የኔ ሰው ገበሬ በሳት አሮ መሞት !

በደል ለበቃው ሕዝብ
መናቅ ለመረረው
የባልቻ መታረድ ፣ ምን ሲል አስፈለገው ?
የስክንድር መታሰር የርዮት እንግልት
ያስነሳን ነበረ ፣ ሰው ብኖሆን ባንድነት ።

የሸዋስ ፣ ተመስገን ፣ አንዷለም ሀብታሙ
ስለምን ታሰሩ ፣
ስለምን ስለ-ማን የመከራ ገፈት ዛሬም ይቀምሳሉ?
ብለን የምንጠይቅ ሰዎች ሆነን ቢሆን
ህሊና ቢኖረን ፣ እንደሰው ብናስብ
በምኑም በምኑም ሰበብ ባንሰበስብ

ይህ አይሆንም ነበር የኛ ታሪካችን
ቀና ብለን ነበር እኛም ባገራችን ።

የሸዋስ ሲታሰር ፣ አንዷለም ሲገረፍ
መስከረም ጠብቶልን ፣ ዓመት ዓመት ስንድረስ
ቃላት ስንደረድር ፣ ስብሰባ ስንጠራ
እንደ የኪስ ሌባ ተገርፈን ስንገባ
ሰብስበው ሲያንጫጩን
እርስ በርስ ሲያጋጩን
በጎሳ ና በዘር እንደ አርማታ ድንጋይ ለማነስ ስያፋጩን
ፈልገን ነው እንጂ ፣ መረገጥ ወዶልን
ቢሻለን ነው እንጂ ፣ መዋረድ ሰምሮልን
ይበቃን ነበረ ፣ በቃን ብለን ብንል ።

ዘጠና ሚሊዮን አፉ ተለጉሞ
ነብሱ የጭንቀት ጏዳ
ደሙ “ብርክን ” ወልዳ
አያልቅም ፍርሃቱ ቢቀዳ ቢቀዳ
አይ ያበሻ ዕዳ!!!

ጏደኞቹን ቀብሮ
እናትና እህቱን ዛሬም አሳስሮ
ከአምናው ፍርሃቱ ዘንድሮም ተምሮ
በታመቀው ድምጹ ራሱን አፍኖ
ይኖራል ሀበሻ በማነሱ ገኖ !

ሳሙዔል ቢገደል ፣ ሐበሽ ቀባሪ ነው
ድንኳኑን ሰባሪ
ካርታ እየፐወዘ ፣ ተረት ተረት አውሪ !
አንድ ሳጥን ኮካ ፣ አንድ ድስት ምንቸት
የዝን ነው ጥይቱ ፣ ለሞተው ወንድሙ ወንዱ የሚቆጭበት!
ገደሉት እያለ ከንፈር መምጠጥ እንጂ
በለቅሶ መፈንዳት ፣ እሪ ማለት እንጂ
የሀበሻ መዳፎች ረስተዋል ፈንጂ !

ይልቅስ ያወራል
የአከሌ ቀብር ላይ እኔም ነበርኩ እኮ
አፈር ካለበሱት ፣ አንዱ እኔ ነኝ እኮ
” ቀበር አትሄድም ወይ !?” ይልሃል ሀበሻ
ለቅሶ አትደርስም ወይ ይልሃል ሀበሻ
ቀብር እና ለቅሶ ሆኖ የሱ ጥሻ !

ታዲያ ሳሙዔል ቢሞት ፣ ምኑ ነው እሚገርመው
ወንድሙ በደሉ ፣ ሞቱ ካላመመው ።

እስክንድር ቢታሰር ፣ አንዷለም ቢሰቃይ
የሀበሻ ወንድ ልጅ ፣ ተደፍኖበት ሰማይ
ባህር የቧጥጣል ፣ ሊወጣ ወደላይ !

ታዲያ ምኑ ይገርማል ፣ ምርጫው ቢጭበረበር
ምኑ ነው የሚገርመው ፣ ሀብታሙ ቢታሰር
ሞቶም ” መኖር ደጉ ” እያለ ለሚኖር
ለእንደዚህ አይነት ሕዝብ ፣ ምኑስ ነው የሚገርም ?

ከሳሙኤል ወዲያስ
ከሞቱ ባሻገር
ካለፈላት ሀገር
ከሞተለት ፍቅር

ከሱ ወዲያ ምንድን
ምንም ካልተሰማን ፣ ካልተነሳን በቀር
አንገት ለመቆልመም ፣ ነብስ ለመቀርቀር
ከሆነ ድንኳኑም ፣ መቀበሩም ይቅር !

ከሳሙኤል ወዲያስ
ስንት ወጥተን እንቅበር
ስንቱን እናሳስር ስንቱን እናስገድል?
ለስንቱስ እናልቅስ ስንቱንስ እንቅበር ?
ካልበቃን ፣ ዘንድሮ ባንድ ላይ ካልሞትን
ባንድ ላይ ባንድነት ፣ ሞት ጋልተጋፈጥን
የጀግና ሰው ሞቱ ፣ የዜና ማድመቂያ
የውይይት መድረክ ፣ ድንኳንን ማሞቂያ
የሚሆን ከሆነ
ከሳሙኤል ወዲያ ፣ ሞቱ የማይከፈል
ሺ ሳሙዔል አለ !

ስለዚህ ጥያቄው ከሳሙኤል ወዲያስ
ምን መሆን አለበት
አንገቶች ይቃኑ ፣ ከተመሸጉበት
ድምጾች ድምጽ ይሁኑ ከተዳፈኑበት
ጉልበቶች ይበርቱ ፣ ክንዶች ይፈርጥሙ
ሳሙዔል ይነሳ ፣ ይሁን ዲበ- ኩሉ !

ከሳሙኤል ወዲያ
ምንድን ነው ዕጣችን
የሚለው ነገር ነው ፣ የኛ ፈተናችን
ትልቁ ጥያቄ ፣ ትልቁ ጭንቃችን
ደፍረን ካልመለስነው
ዙሮ ዙሮ ያው ነው !

Filed in: Amharic