>
5:13 pm - Sunday April 19, 3136

‹‹ከእኛው ውጭ ማንም ሊደርስልን አይችልም!›› ኢ/ር ይልቃል ጌትነት

ቁጭት፣ አንገት መድፋት፣ ሁል ጊዜ ሀዘን፣ ሁል ጊዜ ወደ ውስጥ ማልቀሳችን አልፎ፣ ወይም ደግሞ ደረቅ ታሪክ ሆኖ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ የስልጣኑ ባለቤት፣ የሰው ልጅ ክብር አግኝቶ የሚኖርበት ቀን በጣም ይናፍቀኛል፡፡ ይህ የህዝብ ሰቆቃ ስለመረረኝ አንዳንዴ ከዛ የነፃነት ቀን የምደርስ ሁሉ አይመስለኝም፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለምንድን ነው መኪና የሌለህ? ለምንድን ነው ጥሩ ኑሮ የማትኖረው? ብለው ስለ ቅንጦት ሲያወሩ አሊያም ቢያስሩህስ ብለው ሲጨነቁ ምንም ነገር የማይሰማኝ ይህ ያለንበት የመከራ ጊዜ ስለማይጥመኝ፣ ስላስመረረኝም ነው፡፡

ከእኛው ውጭ ማንም ሊደርስልን ...ኢትዮጵያ ትልቅ ታሪክ ያላት አገር ናት፡፡ ነገር ግን ምርጫውንም እንዳያችሁት ይህን ያህል አዋርደዋታል፡፡ የሀይማኖት ሀገር ነበረች፡፡ አሁን ግን በሚያሳዝን መልኩ ሀይማኖትንና ሽምግልናን ቀልደውበታል፡፡ የስልጣኔ አገር ነበረች፣ አሁን ግን ዛሬ የተሰራው ነገ የሚፈርስበት አገር ሆናለች፡፡ መንግስት ተብለው ህዝብን የሚያዋርዱበት አገር ሆናለች፡፡ ሞት ያለ ነገር ነው፡፡ እኛም እንደ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን መሄዳችን አይቀርልንም፡፡ ለዚህም መታገላችን ካልሆነ በስተቀር ሌላ ተስፋ የለንም፡፡

በዚህ ስቃይ ቅር ቢለኝም፣ ከልቤ ባዝንም ከሁሉም ነገር ቀጭኗ መስመር ላይ መቆሜን እንደቁም ነገር እቆጥራታለሁ፡፡ ይህ መከራ የሚበቃበት በዚህ መንገድ ነው፡፡ ሀገሩም፣ ስቃዩም፣ ተስፋውም የእኛው ነው፡፡ ከእኛ ውጭ ማንም ሊደርስልን አይችልም፡፡ ላያችን ላይ ያሉት ሰዎች ዋናው መሰረታቸው ማታለል ነው፡፡ 97 ላይ አቶ መለስ ከእነ ቶኒ ብልየርና ከሌሎች የምዕራባዊያን ዴሞክራቶች ጋር ጎን ለጎን በመቀመጣቸው በህዝቡ እውቅና ያገኙ መሰላቸው፡፡ ምንም አይመጣም ብለውም ምህዳሩን ገርበብ አድርገው ከፈቱት፡፡ ቅንጅት ደግሞ በርግዶ በመክፈት ኢህአዴግን አርበደበደው፡፡ ያኔ ሲጨንቃቸውና ፍፁም ያላሰቡት ነገር ሲከሰት በስልጣን መቀለድ አይቻልም ብለው ሁሉንም ነገር እንዳልሆነ አደረጉት፡፡ ቅንጅትን አፈረሱ፣ የገደሉትን ገደሉ፡፡ ከዛ ነው ቀያጅ አዋጆች የወጡት፡፡ ከዛ በኋላ ነው 99 በመቶ ማሸነፍ የሚባለው የመጣው፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያንም በቀላሉ እንታለላን፡፡ በወቅቱ ልደቱ እንዲህ አደረገ፣ ብርሃኑ እንዲህ አደረገ፣ ኃይሉ እንዲህ አደረገ.. እያሉ ሲያታልሉን ቅንጅትን ማን እንዳፈረሰው ረስተን መሪዎቹን መወቀስ፣ የኢህአዴግን በደል መርሳት ጀመርን፡፡ሰኔ 1 ቀን የተፈፀመው ጭፍጨፋ አሁንም የቁልቁለት መንገድ ሆኖ እየተባባሰ ነው፡፡ ከዛ በኋላ አማርኛ ተናጋሪዎችን በየ ቦታው እየገደሉና እያፈናቀሉ ነው፡፡ በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ምክንያት ብሩህ አእምሮ ያላቸው ወጣት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ግንባር ግንባራቸውን ተብለው ተገድለዋል፡፡ ሙስሊም ወንድሞቻችን በየ መስጊዱ ደማቸው እየፈሰሰ ነው፡፡ ይህ ሁሉ በአይናችን ያየነው ብቻ ነው፡፡ አሁን በየ መንገዱ እየታሰሩ የሚገኙት ወጣቶች በርክተዋል፡፡ ‹‹ያለ ምንም ደም ኢህአዴግ ይውደም፣ ሰማያዊ የኛ›› ብለዋል ዘምረዋል ተብለው ወጣቶች 5 ወር ተፈርዶባቸዋል፡፡ እንዲህ አይነት ነፍሰ በላ ስርዓት ውስጥ ነው የምንገኘው፡፡ ከዚህ ሁሉ የውርደት ማቅ የምንወጣው እኛ ራሳችን ነን፡፡
ነገረ ኢትዮጵያወደ ውስጥ ማልቀሱ ወደ ውጭ መውጣት አለበት፡፡ ወደ ውስጥ ማልቀሱ ወደ ወጭ አለመውጣቱ ነው እንጅ ከገዥዎቻችን ጋር ማንም እንደሌለ ግልጽ ሆኗል፡፡ አሁንም ፕሮፖጋንዳ የሚሰሩበት አጥተዋል፡፡ አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ከሚባሉት ደህንነቶችና ካድሬዎች ውጭ ማስመሰላቸውን የኢትዮጵያ ህዝብ ነቅቷል፡፡ ፖለቲካ የርዕዮት ዓለም መሆኑ ቀርቶ አሁን እናቶችን አስፈራርቶ መመረጥ ሆኗል፡፡ እንዲህም አድርገውም መቶ ፐርሰንት አሸነፍን የሚሉትንም መሸከም አቅቷቸዋል፡፡ አሁንም እስሩ፣ ማዋከቡ ቀጥሏል፡፡ሰኔ 1 ላይ የተጨፈጨፉት ሰማዕታት ናቸው፡፡ እንዲህ በኃላፊነት ከተጓዝን የተጨፈጨፉት ወንድሞች ደም በከንቱ እንደማይቀር ተስፋ አለኝ፡፡ እኛ እንደ ትውልድ ኃላፊነታችን በመወጣት ይህን ትግል ማድረግ ስላለብን እንጅ እኛም ባንታገል መከራው እስካለ ድረስ ይህን የመከራ ቀን እንዲያልፍ የሚታገል ትውልድ መምጣቱ የማይቀር ነው፡፡
ኢትዮጵያ የእውነት፣ የነፃነት፣ አገር እስክትሆን የምንፈልጋቸውን የምንመርጥበት፣ የማንፈልጋቸውን የምናስወግድበት ቀን እስኪመጣ ድረስ አሁን ያለንን መገፋት ወደ ቁጭት ተቀይሮ፣ ቁጭቱ ወደ ወጭ መፍሰሱ የማይቀር ነው፡፡ ወደ ፊት መውሰድ ያቃተንን ትግል አሁን ተምረን መጓዝ አለብን፡፡ ሰማያዊ ይህን ትግል ወደ ፊት ለመምራት የተቻለውን ሁሉ እንደሚያደርግ ጥርጥር የለኝም፡፡
(በሰኔ 1 ሰማዕታት መታሰቢያ ላይ ካደረጉት ንግግር የተወሰደ)

ሰኔ 1/2007 ዓ.ም

ነገረ ኢትዮጵያ

Filed in: Amharic