>

“ሽኩፍ” ሲገለጥ [አርአያ ተስፋማሪያም]

shkuf sigelet be Araya Tesfamariamጠ/ሚ/ር ሃ/ማርያም፣ ባለቤታቸውና ሌሎች አንገታቸው ላይ ስላጠለቁት በተመለከተ አንድ የቀድሞ አንጋፋ የድርጅቱ ታጋይ በግል ያደረሱኝ መልእክት እንዲህ ሲል ይጀምራል « በታጋዮች ዘንድ “ሽኩፍ” ተብሎ ይጠራል። ታጋዩ ከሞተ በኋላ የሚገነዝበት ጨርቅ ነው። ድርጅቱ አላማ ያለው የመሰለው አብዛኛው ታጋይ ያን ጨርቅ አንገቱ ላይ በማጥለቅ ለመሰዋት (ለመሞት) ቁርጠኝነቱን የሚያሳይበት ነበር። 98 በመቶ የሚሆነው ተዋጊ ያልተማረ ስለነበረ የድርጅቱ አላማና አካሄድ ሊያውቅበት የሚችል አንድም መንገድ አልነበረም። በእሱ ደምና አጥንት ተረማምደው ሲያበቁ የራሳቸውን ድብቅ አጀንዳ አስፈፀሙ። 36 ሺህ የህወሀት ታጋዮችን ገና በጠዋቱ አባረው ለአስከፊ የጐዳና ህይወት ዳረጓቸው። ኢትዮጵያውያን ወንድማማቾችን በብሄር ፖለቲካ እርስ በርስ እንዲናቆሩ እነመለስ የጥፋት ወጥመድ ዘረጉ። “ፓርቲው ወዴት እየሄደ ነው?..ግምገማ መካሄድ አለበት፤ ሙስና ተቀጣጥሏል..” የሚሉ ጥያቄዎችን ያነሱና ከጋንታ እስከ ሬጅመንት አዛዥነት (ኋላ መኮንኖች) ቦታ የነበራቸው 5 ሺህ ታጋዮች ሆለታና ታጠቅ እስር ቤቶች ታጐሩ። አቶ መለስ 36 ሺህ ታጋይ በ84 ዓ.ም ሲያባርሩ «ጓሃፍ ፅረጉለይ..» ማለትም “እነዚህን ቁሻሻ ጥራጊዎች አስወግዱልኝ” ነበር ያሉት። ትእዛዙን ደግሞ ስዬ አብርሃ ተፈፃሚ አደረጉ። ለ5 ሺህ መኮንኖች ደግሞ ያቀረቡት ሰበብ «መፈንቅለ ፓርቲ ለማድረግና እኔን ለመገልበጥ ሲያሴሩ..» የሚል የፈጠራ ክስ በመለስ ዜናዊ ቀረበባቸው። በሆለታ እስር ቤት በ1988 ዓ.ም እንዶድ የተባለ መርዝ ጨቅጭቀው የጠጡ 1 ሺህ 5 መቶ (1,500) መኮንኖች ህይወታቸው ሲያልፍ የሁሉም ሬሳ በአንድ ጉድጓድ በሌሊት እንዲከተት ተደረገ። በታጠቅ ከ1 ሺህ የሚበልጡ በተላላፊ ሳንባ እንዲያልቁ ተፈረደባቸው። የዚህ ሁሉ እልቂት ምስጢሩ ታጋዮቹ “የሃየሎም ግሩፕ” በሚል በነመለስ ስለተፈረጁ ነበር። እነሱን ከጨረሱ በኋላ እሱንም አስገደሉት። ሃቁ ይህ ሲሆን ዛሬ እነሃ/ማርያምና ሌሎቹ ባልዋሉበትና ባልነበሩበት ትግል ያን “ሽኩፍ” አጥልቀው መታየታቸው ያሳፍራል። ለነገሩ በታጋዩ መስዋእትነት የተረማመዱት የዛሬው ሚሊየነሮች አጥልቀው ታይተው የለ!! ታሪክና ጊዜ ይፈርደናል!» ይላል። …በነገራችን ላይ የሆለታና ታጠቅ እስር ቤት የጅምላ እልቂትና ስቃይ በተመለከተ በ1994 ዓ.ም ጥቅምት ወር አንስቶ የአንዳንድ ሟች ታጋዮች ፎቶ በማስደገፍ እንዲሁም በእስር ቤት የፃፏቸውን መልእክቶች በማያያዝ በኢትኦጵ ጋዜጣ በተከታታይ መረጃው ይፋ ተደርጓል።

Filed in: Amharic