>

“ሰማንያ አንድ ዜሮዜሮ – ኤ” [ክንፉ አሰፋ]

ወቅታዊው የቴሌቭዥናችን አዝማች፤

.. ሰማንያ አንድ ዜሮዜሮ- ኤ ብለሽ መላዕክት ከላልሽ፣

አባይን ገድበሽ ሽልማት በሽበሽ። …. 8100 …. 8100 …. 8100-A A A

የምትለው ዜማ በብዛት ትለቀቃለች። ኮሜዲያን ተሰብሰበው የሰሩዋት ዜማ ናት። ቀልደኞቹን ማኖ ለማስነካት ተብላ የተቀነባባረች ነገር ናት የሚሉም አሉ። የቴሌቭዥኑን ጣብያ ከፍቶ የሚመለከተው ሰው እጅግ ጥቂት ቢሆንም መልእክቱ በማህበራዊ ድረ-ገጾች መደመጡ አልቀረም። የዚህ ማስታወቅያ አላማ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ የእጣው ዝርዝር ግን ለብዙዎች እንግዳ ሳይሆን አልቀረም።

አንዲት አዛውንት የልጃቸውን ተንቀሳቃሽ ስልክ እያነሱ ይቀጠቅጣሉ።  በሳምንት ሶስቴ 8100 እየደወሉ ‘A’ ፊደልን ይጫናሉ። ከብዙ ግዜ በኋላ ታዲያ ልጃቸው አወቀባቸው። በመገረምም ለምን ይህንን ሁሉ ግዜ መደወል እንደፈለጉ ጠየቃቸው።  እናት መለሱ “ሁሉም ነገር አለኝ። ዲግሪ ግን የለኝም። በዚህ እድሜየም  በአቋራጭ ካልሆነ ላገኘው አልችልም።” ሲሉ የማስትሬት ዲግሪው እጣ እንዳጓጓቸው ነገሩት።

ሶስት ብር ከፍሎ ‘8100-A’ አጭር መልዕክት የላከ ሰው ሁሉ እጣ ይወጣለታል። እነሱ እንደሚሉት ከሆነ እድሉ የቀናው ሰው የመኖርያ ቤት፣ መኪና፣… እንዲሁም ዶክትሬትና ማስትሬት ዲግሪ ይደርሰዋል።

ማስትሬት እና ዶክትሬት ዲግሪ በእጣ እንዴት ነው ለህዝብ ሊቀርብ የሚችለው? መሰረታዊ ትምህርት የሌለው  አንድ አርሶ-አደር አልያም አንዲት የቤት እመቤት የዶክትሬት ዲግሪ እጣ ቢደርሳቸው ዩኒቨርሲቲ ገብተው ዲግሪያቸውን ሊጭኑ ነው? ብቻ  ምን ችግር አለ?  ለመዕተ-ዓመቱ እቅድ ማሟያ ተብለው የተሰሩት ፴ ዩኒቨርሲቲዎች አሉ። ምሁራንን ሳይሆን ‘ድንጋይ ማምረቻ’ እየተባሉ የሚተቹ ዩኒቨርሲቲዎች። የኮሌጅን መስፈርት በአምስት በመቶ እንኳን የማያሟሉ ባዶ ህንጻዎች። ከነዚህ ኮሌጆች እየተመረቁ የሚወጡት ተማሪዋች ስማቸውን እንኳን በቅጡ መጻፍ አይችሉም የሚባሉበት ኮሌጆች።

ለነገሩ በስልጣን ላይ ያሉትም ሁሉ ዛሬ የማስትሬት እና የዶክትሬት ዲግሪ ባለቤቶች ሆነዋል። ሴንቸሪ ዩኒቨርሲቲ ምስጋና ይግባውና እነ አባዱላ ገመዳም ማስትሬት ዲግሪ ገዝተዋል። ጀነራል ባጫ ደበሌም ሁለት ዲግሪ ጭነዋል።

ያልተጠና እና ግብታዊ በመሆኑ ይመስላል የ 8100-A ዘመቻ መቀለጃ እየሆነ መምጣቱ። ኢሳያስ አፈወርቂም የዚህ እጣ እድል ደርሷቸዋል አሉ። ባለፈው ሰሞን የኢትዮጵያ አየር ሃይል ባልደረባ የነበረው ካፒቴን የህወሃትን ስርዓት በመቃወም ይዞት የጠፋውን ሚግ 23 አውሮፕላን ለአስመራው መንግስት እንዳስረከበ ነበር ይህ ቀልድ የተነገረው።

የዚህ ጽሁፍ ዋናው ጉዳይ የትምህርት ማሽቆልቆል ነገር አይደለም። የ 8100-A ዜማ እንዳበቃ  ባናቱ ላይ የሚነገር አንድ መልእክት ላይ እንጂ። የሰማንያ አንድ ዜሮ-ዜሮ ቁልፍ በእዚህ መልእክት ላይ ይገኛል።

“እንደጀመርነው እንጨርሰዋለን?”

ምን ማለት ነው? ላይጨርሱት ኖሯል እንዴ የጀመሩት? አባባሉ የጀመሩትን የመጨረስ ጥርጣሬ ውስጥ እንዳሉ ፍንጭ ይሰጠናል። ፍጹም በግብታዊ በሆነ፣ በዕውቀት እና ዕቅድ ላይ ያልተመረኮዘ፣  የባለሙያ ክህሎት ያልነበረው ጅምር መሆኑን ፍንትው አድርጎ ያሳየናል።

“እንደጀመርነው እንጨርሰዋለን!” መፈክር ሆነ። እድገት የሚመጣው በመፈክር ሳይሆን በስራ ነው። ስራ ደግሞ በእውቀትና በእቅድ እንጂ በስሜት አይከወንም።

ሃይለማርያም ደሳለኝ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱ ስልጣን ላይ ጉብ ያሉ ሰሞን ደጋግመው የሚሉት ነገር ነበር። “እዚህ የተቀመጥቁት መለስ የጀመረውን እቅድ ሁሉ ለመጨረስ ነው።”

ይህን ካሉን ሶስት አመታት አለፉ። ሃይለማርያም ደሳለኝ የጨረሷቸውን ፕሮጀክቶች ስንፈትሽ አንድ ነገር ብቻ አገኘን። እሱም የጸረ-ሽብር አዋጁን ተግባራዊ በማድረግ የህሊና እስረኞችን ቁጥር መጨመር ብቻ ነው። ከዚህ ውጭ በገዢው ፓርቲ ተጀምረው የተጨረሱ ነገሮች የሉም። ሌሎቹን ለግዜው ተወት አድርገን የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶችን ብቻ እንቃኝ።  አስራ አንድ ግድቦች ተጀምረዋል። ግን ሁሉም አላለቁም። ለምን? በዚህ ላይ ወደ ኋላ እመለስበታለሁ።

ባለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት የተጀመሩት የመስኖ እርሻ እና የሃይድሮ-ኤሌክትሪክ ልማት ፕሮጀክቶች በርካታ ናቸው። የተንዳሆ ግድብ፣ የከሰም ግድብ፣ የርብ ግድብ፣ የጊዳቦ ግድብ፣ የአርጆ ደዴሣ ግድብ፣ የራያ አዘቦ ግድብ፣ የቆቦ ጌራ ግድብ፣  አድአ በቾጠ ግድብ፣ የቆጋ ግድብ፣ የመገጭ ግድብ፣ እንዲሁም የጉደር እና ዳቡስ ግድቦች ናቸው። በ፩፱፱፯ ዓ.ም  በአፋር የተጀመረው የከሰምና የተንዳሆ ግድብና መስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ  አመታት አለፉት። የታቀደለት ጊዜ ከ ፭ አመት በፊት ቢያልፍም ስራው ገና አልጀመረም። በ፪፻፪ ዓ.ም የተጀመረው የርብ ግድብ ግንባታ፣  የጊዳቦ ግድብ ግንባታ፣ የአርጆ ደዴሣ ግድብና መስኖ ልማት፣ የራያ አዘቦ  መስኖ ልማት፣ የቆቦ ጊራ መስኖ ልማት፣ አድአ በቾጠ መስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ሁሉ ግዚያቸውን በልተው የኤሊ ጉዞ ላይ ናቸው።  ግንባታው በ፪፻፬ የተጀመረው የቆጋ መስኖ ልማት፣ የመገጭ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት፣ ላይኛው ጉደር መስኖ ልማት፣ ዳቡስ መስኖ ልማት … ተጀምረው ቆመዋል።…እነዚህ እንግዲህ “እንደጀመርነው እንጨርሰዋለን!”  ያልተባሉ ፕሮጀክቶች ናችው። ምክንያቱም የፖለቲካ ጠቀሜታቸው ይህን ያህል ስላልሆነ።

እርግጥ ነው። በመጀመሪያው “የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ” ውስጥ የአባይ ግድብ ፕሮጀክት አልነበረም። ከበጀቱም ውጭ ነው። ስለሆነም አጀማመሩ ድንገት ነበር። ጥናት ሳይጠና፣ ሳይመከር፣  በጀት ሳይያዝ የተጀመረ ፕሮጀክት ነው።  አባይ በባዶ ተጀመረ። የቦንድ ሽያጭ ተሞከረ።…እንዲህ እያለ ሎተሪ ላይ ደረሰ… ይህ ብዙ እንዳላስኬደ በግልጽ ይታያል። በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ሁሉም ነገር በስሜት እና በግብታዊነት ስለሚሰራ የአጭር ጊዜን እንጅ ረጅሙን አያዩትም። በመጨረሻ ግን ግዜው ደርሶ ማጠፊያው ሲያጥራቸው ይታያሉ።  የዚህ ፕሮጀክት አጀማመር በእርግጠኝነት አባይን ገድቦ ልማት ላይ ለማዋል ተብሎ ሳይሆን ከወቅታዊው የስልጣን ችግር ለማምለጥ የተወጠነ  እቅድ ነበር።  ለግዚያዊ ጥቅም ተብሎ እንደቀልድ የተጀመረው ነገር አሁን የህዝብ እምሮ ውስጥ ስለገባ ይመስላል ቅኝቱን ያስተካከሉት። … እንደጀመርነው እንጨርሰዋለን!

የአባይ ጉዳይ ለገዥው ፓርቲ  ህልውና ወሳኝ ነገር ተደርጎ ተወስዷል። ከኢኮኖሚው ይልቅ የፖለቲካ ጠቀሜታው ቀላል አይደለምና።  የኢኮኖሚውን ጠቀሜታ ቢመለከቱ ኖሮ አባይን መገደብ እንደሚያወሩት ከባድ አልነበረም። ገዥው ፓርቲ ለሃገር ካሰበ ገንዘቡም ቅርብ ነው። የዜጎች ደሞዝ ሳይቆረጥ፣ ቦንድ ሳይሸጥ፣  ህዝብ ሳይቸገር፣ ቀረርቶ ሳይነፋ… አባይን መገደብ ይቻላል። የኤፈርት ገንዘብ ብቻ አንድ ሳይሆን ሃምሳ አባይን ይገድበዋል። በግል ከተዘረፈው 16ቱ ቢሊየን ዶላር ሳይነካ ማለት ነው።

አባይ ተገድቦ አገልግሎት ቢሰጥ መልካም ነገር ነው። ይህ ጎስቋላ ህዝባችንም ከድህነት አረንቆ ሲወጣ ብናይ ሁላችንም ደስታችን ነው።ዲያስፖራውም አባይ ተገድቦ ማየት ይፈልጋል።  ችግሩ ያለው ግልጽነት እና ቅንነት በጎደለው በዚህ መልኩ ለፖለቲካ ትርፍ ሲባል ብቻ በመከናወኑ ነው። ችግሩ ያለው በልማት ስም በሚደረገው የሰብአዊ መብት ጥሰት ላይ ነው። አባይን ከመገደቡ በፊት የመብት ረገጣው ቢገደብ ዲያስፖራውም በዚህ ላይ በተረባረበ ነበር።

“እድገትና ትራንስፎርሜሽን” የተባለው “ቅኝት” አምስቱን አመት እንደዋዛ ዘልቆታል። የተባለው ለውጥ ግን አልታየም። ሃይለማፘም ደሳለኝ ፓርላማ ላይ ጉብ ብለው በእቅዱ አፈፃፀም የነበሩ ተግዳሮቶችን ዘርዝረውልናል። አፈጻጸም አሉን እንጂ ነገሩ ሌላ ነው። ከ85 በመቶ በላይ የሚሆነው የአገሪቱ ህዝብ የሚተዳደርበትን የግብርናውን ዘርፍ  ለማሻሻል የታቀዱ የመስኖ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ አልሆኑም። የገጠር መንገዶች ሰባ በመቶ እንደሚሰሩ ቅኝቱ ላይ ነበር። ይህም ፈጽሞ ሊሆን አልቻለም። አሁን ያለውን አስር በመቶ የኤሌትርክ ሃይል ተጠቃሚ በሰማንያ አምስት በመቶ ለማሳደግ ቃል ገብተው ነበር። ወጤቱን ስናየው ግን የነበረው አስር በመቶም ወደ ፈረቃ አሽቆልቁሎ መሄዱን ነው።

በደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ታምቦ ምቤኪ የሚመራው የጥናት ቡድን ባለፈው ወር ከሂልተን ሆቴል የለቀቀው ዘገባ በኢትዮጵያ ስለሚካሄደው ስለዘረፋው አስደንጋጭም አስረጋጭም ነበር። ከኢትዮጵያ ተዘርፎ የወጣው ገንዘብ 16.5 ቢሊየን ዶላር መድረሱን አረጋግጦልናል።  ይህ አስደንጋጭ ዘገባ ከዚህ ቀደም Global Financial Integrity (GFI)  አለማቀፍ የገንዘብ ግልጸኝነት ተቋም ዘገባ ላይም ወጥቷል።  የትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽባል ዘገባ እንደሚለው ከሆነ ከተዘረፈው ገንዘብ ግማሽ ያህሉ ከሃገር የወጣው በእድገት እና ትራንስፎርሜሽኑ ዘመን ነው።

ሌላም አስደንጋጭ ነገር አለ። ኢትዮጵያ በዘመነ ህወሃት በዋስትናም ሆነ ያለዋስትና የተበደረችው እዳ 40 ቢሊየን ዩ..ኤስ. ዶላር ደርሷል። ይህን የዘገበው ላሙዲ የተባለው አለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ነው። ይህ እዳ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ሲሰላ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የግማሽ ሚሊዮን ዶላር ባለ እዳ እንደሆነ ይጠቁመናል። ይህ ገንዘብ ለልማት መዋል ሲኖርበት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ከሀገር እየወጣ መሆኑን ነው እንዚህ አለም አቀፍ ተቋማት እየነገሩን ያለው።

በዚህ በኩል የ”ሰማንያ አንድ ዜሮዜሮ” ዘመቻ፣ በዚያ በኩል ደግሞ ዘረፋው ሊጣጣሙ አልቻሉም። የሚወጣው ከገቢው አልተስተካከለም። ዘረፋው ግዙፍ ነው። በዚህ ሁኔታ ነው መፈክር እየተሰማ ያለው። “እንደጀመርነው እንጨርሰዋለን!”

በኢትዮጵያ የዓለም ባንክ ዳይሬክተር ከሆኑት ከኬን ኦሃሺ ስለ መፈክሩ ቅኝት የተናገሩት የሚያስደምም ነው።

“ኢትዮጵያ … ተዓምራዊ በሆነ መልኩ የነዳጅ ክምችት ጉድጓድ ካላገኘች ወይንም ያልተጠበቀ – ነፋስ አመጣሽ የሆነ ገንዘብ ከሰማይ እንደ መና ካልወረደ በስተቀር (እድገት እና ትራንስፎርሜሽኑ) በምንም ዓይነት መልኩ ቀጣይነት ያለው መሆኑ አይታየኝም… እንደዚህ ያለውን በኃይል እና በመፈክር የተሞላ እና የውስጥ ችግሩን በጥልቅ ያልተመለከተ ዕቅድ እንዴት ሊያስቀጥሉት እንደሚችሉ የሚታየኝ ነገር የለም።  እንደ ሀገር በቂ የሆነ ጥሪት መቆጠብ እስካልተቻለ ድረስ ምንጊዜም ቢሆን ጥገኛ የሚሆነው በውጭ መዋዕለ ንዋይ፤ አልያም ደግሞ ጤናማ እና ቀጣይነት በሌለው የመዋዕለ ንዋይ መሰብሰቢያ መንገድ ነው… እንደዚህ ያለ ወጥመድ ውስጥ ነው ተወጥረው ያሉት…

“ዕዳ ካለ አደጋ አለ… ይህ የመንግስት-መራሹ ኢንቨስትመንት ዕድገት አንድ ቦታ ላይ ቢቆም ወይም ለጥቂት ጊዜ መንቀሳቀስ ባይችል እና ቢንገዳገድ እነዚህ ሁሉ የብድር ዕዳዎች ይመሰቃቀላሉ…የግል ዘርፉን ባላሳተፈ እና ጠንካራ ሆኖ ባልተስፋፋበት መልኩ የሚመጣ ፈጣን የምጣኔ ሀብት ዕድገት ዘለቄታ እንደማይኖረው እና፤  ይህ ከሆነ እነዚህ በጊዜ ሂደት የሚደረጉ የብድር ዕዳዎች ሁሉ ከቁጥጥር ውጭ ሊሆኑ የሚችሉ መሆናቸው እጅጉን ያሳስበኛል።”

ሲሉ ለገዥው ፓርቲ ዱብዳ የሆነ ይህን እውነታ አፍረጥርጠውታል። እውነታው ይህ ነው። ሳይጨመርና ሳይቀነስ የቀረበ የገለልተኛ አካል ምልከታ።

ሁላችንም በአንድነት እንዲህ እንበል። አባይ ይገደባል። ከአባይ በፊት ግን የመብት ረገጣው ይገደብ!

በሰሞኑ ቀልድ ልሰናበት። ጎተራ አካባቢ ነው። መብራት ፈረቃውን ተከትሎ ጠፍቷል። የሰፈሩ ማጅራት መቺ ምሽቱን ተገን በማድረግ ፍተሻ ጀምሯል። ጸዳ ያለ መኪና አቁሞ ወደ ቅምጥ ቤቱ እየነካ ያለውን ስውዬ አስቆመው።

“ቁም! ሳተበላሽ ገንዘብህን በሙሉ አስረክብ!”

“ምን ነካህ!  እኔ’ኮ ባለስልጣን ነኝ።  ምንስቴር!” ባለስልጣኑ መለሰ።

“አሃ!  ክቡር ሚኒስቴር እንግዲያውስ ገንዘቤን ሃምጣ!”

***

ለዛሬ በዚህ እነሰነባበት። በሚቀጥለው ጽሁፌ ስለ ኢሳያስ አፈወርቂ የምለው አለኝ። የነገ ሰው ይበለን።

Filed in: Amharic