>

‹‹በብርቱ ታምሜያለሁ›› [ አበበ ቀስቶ - ከዝዋይ እስር ቤት]

30 ደቂቃዎችን በዝዋይ እስር ቤት (ግዞት)

በላይ ማናዬ

ዝዋይ የሚገኙ የፖለቲካና የህሊና እስረኞችን በቦታው ተገኝቼ ለመጠየቅ እቅድ ከያዝኩ ረዘም ያሉ ቀናት አልፈዋል፡፡ እንዲያውም ጉዞው ከወዳጆቼ ጋር ሰብሰብ ብለን ቢሆን እንደሚመረጥ ተነጋግረንበት ነበር፡፡ ሆኖም ግን የዕለት ከዕለት ሩጫችን አላወላዳ ብሎን ባቀድነው ጊዜ ወደ ዝዋይ መጓዝ ሳንችል ቆይተናል፡፡ አርብ ህዳር 12/2007 ዓ.ም ግን እንዳሰብነው ሰብሰብ ብለንም ባይሆን በመጨረሻ አብሮኝ ከተጓዘው የሰማያዊ ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት ቋሚ ኮሚቴ ባልደረባ ወጣት ፍቅረማርያም አስማማው ጋር ከአዲስ አበባ በጠዋት ተነስተን ወደ ዝዋይ አምርተን ለ30 ደቂቃዎች ያህል የናፈቅናቸውንና የናፈቁንን እስረኞች ልንጎበኝ በቅተናል፡፡

ዝዋይ ለመድረስ ከ2 ሰዓት በላይ ጉዞ ማድረግ ነበረብን፤ በጠዋት ቃሊቲ መነሐሪያ በመገኘት የዝዋይን ትራንስፖርት ለመያዝ ስንገኝ መልካም አጋጣሚ ተከሰተ፡፡ አጋጣሚው እኛ ወደምንሄድበት ዝዋይ እስር ቤት ሊሄዱ የተሰናዱትን የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ወንድም እና ሌላ የስራ ባልደረባውን ያገናኘ ነበር፡፡ ቁጥራችን መጨመሩ ለእኛም ለምንጠይቃቸው እስረኞችም መልካም ነበር፡፡

ከተማዋ እንደደረስን ወደ አንድ አብረውኝ የተጓዙት ወዳጆቼ የሚያውቁት ቤት አመራን፤ ቡና በፔርሙስ ለመያዝ፡፡ ‹‹ተመስገን ደሳለኝ በእጅጉ ቡና ይወዳል አለኝ›› ታናሽ ወንድሙ፡፡ ቡናውን አስቀድተን ከከተማዋ ትንሽ ወጣ ብሎ ወደሚገኘው እስር ቤት አመራን፡፡ ጉዞው ደግሞ በጋሪ ነበር፡፡ ወደእስር ቤት የሚወስደው መንገድ እጅግ አቧራማ በመሆኑ ተጓዦች አቧራውን መልበሳቸው እሙን ነው፡፡ በእግር ለመጓዝ የፈቀደ ካለ ድልህ ቲባን በጫማዎቹ ልክ ይዋኝበታል፡፡ የእኛ ጉዞ በጋሪ ቢሆንም ከአቧራው ማምለጥ ግን አይቻልም፡፡

እስር ቤቱ በር ደርሰን ከጋሪ እንደወረድን ወደጥበቃዎቹ ቀርበን የምንጠይቃቸውን እስረኞች ስም ሰጥተን የእኛን ሙሉ አድራሻ አስመዘገብን፡፡ የምንጠይቃቸውን እስረኞች ስናስመዘግብ ‹‹ምኑ ነህ?›› የሚለው ጥያቄ ይነሳል፡፡ ጓደኛ፣ ወንድም፣ ዘመድ…እያልን አስሞላን፡፡ መዝጋቢ ፖሊሶቹ ቀና እያሉ በጥያቄ ያዩናል፡፡ ኢትዮጵያውያን ወገኖች ‹ጓደኛ፣ ወንድም፣ ዘመድ…› ተብለው እንጂ ሌላ በምን ይገለጻሉ ታዲያ! በዚህ መሰረት የአራት እስረኞችን ስም አስመዘገብን፤ እነሱም ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፣ ብ/ጄ አሳምነው ፅጌ፣ ፖለቲከኞቹ ናትናኤል መኮንን እና ክንፈሚካኤል ደበበ ናቸው፡፡ ጥብቅ ፍተሻውን አልፈን ልናያቸው የጓጓንላቸውን እስረኞች ወደምንገናኝበት ቦታ አመራን፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

Journalsit Temesgen Desalegnቦታው ላይ ስንደርስ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በሶስት ፖሊሶች ተከብቦ ቀድመውን ከደረሱ ወዳጆቹ ጋር እያወራ ነበር፡፡ ከአጥር ወዲህ እና ወዲያ ማዶ ሆነን ግማሽ አካል ተቃቅፈን ሰላምታ ተለዋወጥን፡፡ ደስ አለን፤ ተመስገንም ደስታው በመላ ፊቱ ሲበራ ተመለከትን፡፡ በደስታው ድጋሜ ደስ ተሰኘን፡፡ በእኛ በኩል ትንሽ ስለ ጤንነቱ፣ በእሱ በኩል ስለቤተሰብ እና ስለእኛ ደህንነት ተጠያየቅን፡፡ በመካከላችን ትንሽ ዝምታ ሰፈነ፡፡ እኛም ተመስገንም ቀና ብለን ፖሊሶችን ተመለከትን፡፡ ከዚያም ተመስገን ጥያቄ ወረወረ፡፡

‹‹ውጭ ያለው እንዴት ነው? አንድነትና ሰማያዊ….›› ተሜ የጀመረውን ሳይጨርስ ሁለቱ ፖሊሶች አንባረቁብን፡፡
‹‹ፖለቲካ አታውራ! እናንተ ፖለቲካ አታውሩ! ዝም ብላችሁ ሌላ ሌላ አውሩ!…›› አሉን ፖሊሶች አንዴ እኛን አንዴ ከአጥር ማዶ የተቀመጠውን ተመስጋንን እየተመለከቱ፡፡ የፖለቲካ ድርጅቶችን ስም መጥራት ፖለቲካ ማውራት ሆኖ ተሰማቸው፣ እዚያ ለነበሩ ፖሊሶች፡፡ የአንድነትን እና የሰማያዊን ስም ጠርቶ ተሜ ምን ሊያወራ እንደፈለገ እንኳ ለመስማት አልተዘጋጁም፡፡ በየዕለቱ መረጃ የሚያነፈንፍ፣ ያገኘውን መረጃ ደግሞ ወደህዝብ የሚያደርስ ሙያ ላይ እንደነበር ለእነሱ አልገባቸውም፡፡ አዎ መረጃ ምን ያህል እንደሚርብ ለፖሊሶቹ የተገለጸላቸው አልመሰለኝም፤ ለዚያውም ለጋዜጠኛ፡፡

ተሜ ጋር ልናወራ ያሰብነው ብዙ አብይ ጉዳዮች ቢኖሩም ክልከላው የሚያወላዳ አልሆነም፡፡ በበኩሌ በኋላ ተመስገን ላይ ሊያደርሱበት የሚችሉት ጫና ይኖራል ከሚል ርዕሱን መቀየሩን መርጬ ነበር፡፡ ተመስገን ግን ‹‹እናውራበት›› በሚል ትንሽ ከፖሊሶቹ ጋር ተከራከረ፡፡ ተሜ ድፍረቱ በብዕሩ ብቻ አይደለም፡፡ መብቱን ለማስከበር ወደኋላ የማይል ብርቱ ሰው መሆኑን ከሁኔታው አነበብኩ፡፡

በመሐል ላይ ሌሎች እስረኞችን እንዲጠሩልን ስም ዝርዝር ሰጥተን ስለነበር ሲዘገዩ ጊዜ ‹‹እነ ክንፈሚካኤልና አሳምነውን ጥሩልን እንጂ!›› አልናቸው፡፡ አንደኛው ፖሊስ ቆጣ ብሎ ‹‹ቆይ እሱ ጋር ጨርሱ!›› አለን፡፡ ከተመስገን ጋር ያለንን ቆይታ ማለቱ ነበር፡፡ እኛም እስኪመጡ እንደምንጨርስ በመጥቀስ አስጠሩልን አልናቸው፡፡ በዚህ መሐል ትንሽ ጭቅጭቅ ድጋሜ ተፈጠረ፡፡ ‹‹እንዲያውም ስማቸውን በትክክል አልጻፋችሁም፤ ስለዚህ አንጠራላችሁም አሉን፡፡›› እኛም የሰጠናቸውን የስም ዝርዝር የጻፉት የራሳቸው ባልደረቦች እንጂ እኛ አለመሆናችንን ጠቅሰን ነገርናቸው፡፡

ካፈርኩ አይመልሰኝ በሚመስል መልኩ አንጠራላችሁም አሉን፡፡ ‹‹በቃ አምጣው እንደገና አስተካክለው እንዲጽፉ አድርገን እናምጣው!›› አልናቸው፡፡ በእርግጥ ትክክለኛ ምክንያታቸው የስም ስህተት እንዳልሆነ እናውቅ ነበር፡፡ ሲጀመር አሳምነው ፅጌን ከእኛ ከወጣቶች ይልቅ እነሱ ከበረሃ ጀምረው ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ ስለሆነም ‹‹እገሌ የሚባል ሰው የለም፤ እዚሁ ተወለደ ካላላችሁን›› እያሉ ሲናገሩ በውስጤ እየሳቅሁ ነበር፡፡ እንዲያውም፣ ‹‹አዲስ ታሰረ ካላላችሁ በቀር አዲስ እንደማይወለድ ታውቃላችሁ፤ ሴትና ወንድ የት ይገናኛሉና ነው!›› አልኩ፡፡ የግዳቸውን ፈገግ አሉ፡፡

በዚህ መሰል ጭቅጭቅ ከተመስገን ጋር ያለንን ጊዜ ተሻሙብን፡፡ ይህ የገባው ተመስገን ደሳለኝ በጭቅጭቁ ጣልቃ ገብቶ፣ ‹‹ሰዎቹ ከአዲስ አበባ ነው የመጡት፡፡ ስለሆነም ከሩቅ ቦታ መጥተው ሳያገኟቸው ቢመለሱ ደስ አይልም›› አላቸው፡፡ ወዲያው አንደኛው ወደ እኛ ዞሮ ‹‹ናትናኤል መኮንንን የት ነው የምታውቀው?›› አለኝ፡፡ ጥያቄውን ወደጓደኛየም ወሰደው፡፡ ‹‹ይህን ጥያቄ ምን አመጣው›› ብዬ ጥያቄውን በጥያቄ ከመመለሴ፣ ጋዜጠኛ ተመስገን ቀበል አድርጎ ‹‹ኢትዮጵያዊ ወገኑን ሳያውቀውም ቢሆን መጠየቅ ይችላል!›› አለ፡፡ ተመስገን ተቆርቋሪነቱ ደስ ይላል፡፡ ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ እስረኞቹ ሊጠሩልን ስምምነት ላይ ደረስን፡፡ እስኪመጡ ድረስም ከተመስገን ደሳለኝ ጋር ‹‹ከፖለቲካ ውጭ›› ባለ ድባብ ጨዋታችንን ቀጠልን፡፡

ተሜ ስለሚዲያ አብዝቶ ጠየቀኝ፡፡ ያለው ሁኔታ ከሚያውቀው እውነታ እንዳልተለወጠ ገለጽኩለት፡፡ ከዚያም ወደወንድሙ ዞሮ ስለቤተሰባዊ ጉዳዮች ሲያወራ ዓይኖቼን ወዳስጠራናቸው እስረኞች መምጫ አማትር ያዝኩ፡፡ ብ/ጄ አሳምነው ፅጌ፣ ፖለቲከኞቹ ናትናኤል መኮንን እና ክንፈሚካኤል ደበበ ከርቀት አንድ ላይ ሆነው ሲመጡ ተመለከትኩ፡፡ ከፖሊሶች ጋር ባለው እሰጣ ገባ ስሜቴ ተረብሾ ነበር፡፡ ይህ ስሜቴ ግን ድንገት ሶስቱ ሰዎች ከርቀት በፈገግታ ታጅበው ወደ እኛ ሲመጡ ሳይ በንኖ ጠፋ፡፡

Kinfe Mikael  Abebe (Abebe Kesto)ሞገደኛው አበበ ቀስቶ እና የተጓደለው ጤናው ጉዳይ

ብ/ጄ አሳምነው ፅጌ፣ ፖለቲከኞቹ ናትናኤል መኮንን እና ክንፈሚካኤል ደበበ (አበበ ቀስቶ) ካለንበት ስፍራ ደርሰው ተቃቅፈን ሰላምታ ተለዋወጥን፡፡ አቤት እንዴት ደስ እንዳላቸው! ሙሉ ፊታቸው ያበራል፡፡ ‹‹እኛን ልትጠይቁ መጣችሁ?›› እያሉ በደስታ ተቁነጠነጡ፡፡ እውነት ለመናገር ደስታው የእነሱ ሳይሆን የእኛ ነበር፡፡ በበኩሌ በእስር ላይ ያሉ ወንድም እህቶቼን መጠየቅ ምን አይነት የህሊና እረፍትና ደስታ እንደሚሰጠኝ የማውቀው እኔው ነኝ፡፡

ይህ ደስታችን ታዲያ ተመስገን ደሳለኝ ጋር በነበረው መልኩ ድንገት ደፈረሰ፡፡ ፖሊሶቹ አሁንም እሳት ለበሱ፡፡ ከውጭ ያለውን ነገር የተራቡት እነ ክንፈሚካኤል እነዚያን የፓርቲ ስሞች ጠቅሰው ጥያቄ ሰነዘሩ፡፡ ‹‹አንድነትና ሰማያዊ…›› ካፋቸው ቀልበው ፖሊሶቹ አንባረቁ፡፡ ‹‹አንተ ፖለቲካ አታውራ!›› በማለት ያዙኝ ልቀቁኝ አሉ፡፡ እንዲያውም ምንም ሳናወራ ተነሱና ግቡ አሏቸው፡፡ በዚህ ጊዜ አበበ ቀስቶ በኃይለ ቃል መልሶ ፖሊሶቹ ላይ አፈጠጠ፡፡ ፖሊሶቹ ትንሽ ድንግጥ በማለት ‹‹ሌላ ሌላ አውሩ በቃ!›› አሉን፡፡

ዝዋይ እስር ቤት ካሉ እስረኞች ጋር የሚገናኝ ጠያቂ ‹‹ደህና ነህ፣ እንዴት ነህ…›› ብቻ ብሎ እንዲመለስ ነው የሚፈለገው፡፡ ከሁሉም ጋር ያለውን ማህበራዊና የጤና ሁኔታ አንስተን ስንጨዋወት አበበ ቀስቶ ወደእኔ አንገቱን ሰገግ አድርጎ ‹‹አሞኛል፣ በብርቱ ከታመምኩ ቆይቻለሁ›› አለኝ፡፡ ከዚህ ቀደም በጤናው ላይ እከል እንደገጠመው አውቅ ነበር፡፡ የአሁኑ ህመሙ ምን ይሆን በሚል የበለጠ እንዲነግረኝ እኔም አንገቴን ሰገግ አድርጌ ጆሮዎቼን ሰጠሁት፡፡

‹‹የሚያመኝ ይሄን የጆሮየን አካባቢ ነው፡፡ በብርቱ ታምሜያለሁ፡፡ አብሮኝ የሚተኛው ናትናኤል መኮንን ባይሆን ኑሮ ምን እንደሚውጠኝ አላውቅም፡፡ ቁስል አበጅቶ መጥፎ ጠረንም ፈጥሯል›› አለኝ፡፡ እኔም የህመሙ ምክንያት ምን እንደሆነ ጠየቅኩት፡፡

‹‹ያኔ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እያለሁ የደረሰብኝ ድብደባ ነው ዛሬም የሚያሰቃየኝ›› አለኝና ከዚያ ወዲህ እንዴት እየተሰቃየ እንዳለ አስከትሎ አስረዳኝ፡፡ እኔም ‹‹ህክምና…›› ሳልጨርሰው ተቀበለኝ፡፡ ‹‹ህክምና የሚባለውን ተወው፡፡ ይሄው ስንት ጊዜ እንዲያሳክሙኝ የምጮኸው! ሰበቡ አያልቅባቸውም! ምንም በቂ ህክምና አላገኘሁም፡፡ መቼስ….›› ብሎ ያ ከደቂቃዎች በፊት በሳቅ፣ ከዚያም በንዴት ውስጥ የነበረው ቆፍጣናውና ቀጭኑ ፖለቲከኛ በትካዜ አንገቱን ደፋ፡፡ ውስጤ በማላውቀው ስሜት ተላወሰ፡፡ አበበ ቀስቶ በስካርቭ ጨርቅ ሙሉ ጆሮ ግንዱን ጠምጥሞ የመጣበት ምክንያት ገባኝ፡፡ ቁስሉን ለመሸፈን ነው፡፡

ከአበበ ጋር ይህን ስናወራ ሌሎች ወዳጆቼ ከእነ አሳምነው እና ናትናኤል ጋር ስለተለያዩ ጉዳዮች (‹ከፖለቲካ ውጭ›) እያወሩ ነበር፡፡ ‹‹እስኪ ደግሞ ከእነሱ ጋር አውራ፣ ጊዜህን እኔ ብቻ ወሰድኩብህ›› አለኝ አበበ ቀስቶ ወደ ናትናኤልና አሳምነው እየተመለከተ፡፡ እኔም በአለችው ትንሽ ደቂቃ ከሌሎቹ ጋር ጨዋታ ያዝኩ፡፡ በዚህ መሐል ግን ቀልቤ የአበበ ቀስቶ ጤንነት ላይ ነበር፡፡ እንዴት ሰው አካሉ እንዲያ ቆስሎ ህክምና አይሰጠውም?

ስንብት

በፖሊሶች ተደጋጋሚ ማሳሰቢያ ለሰላሳ ደቂቃዎች ብቻ የነበረን ቆይታ ማብቃቱን ስንረዳ 30 ደቂቃ ምን ያህል አጭር እንደሆነ ተገነዘብን፡፡ ስድስት ሰዓት ደርሶም ስለነበር መለያየታችን ግድ ሆነ፡፡ ስንገናኝ እንዳደረግነው ሁሉ እንደገና ለስንብትም ተቃቀፍን፡፡ በእቅፎቻችን መካከል የተሰነቀረው አጥር ደግሞ የመለያየታችን ደንቃራነት ማሳያ ነበር፡፡

ከእነ አበበ ቀስቶ ጋር ያለኝን ስንብት ጨርሼ ወደ ተመስገን ደሳለኝ ስጠጋ በእጆቹ አንገቴን ሳብ አድርጎ ወደ ጆሮዬ ጠጋ በማለት ‹‹ስርዓት ሲፈርስ የሚያደርገውን ያጣል፡፡ ስርዓቱ እየፈረሰ ነው›› አለኝ፡፡ ምንም አልመለስኩለትም፡፡ በእጆቼ ትከሻውን መታ መታ በማድረግ የተናገረውን መስማቴን አረጋገጥኩለት፡፡

Filed in: Amharic