>

የአውሮፓ ህብረት ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በምርጫው ጉዳይ አነጋገረ


• ጠቅላይ ሚኒስትሩንም ምሽቱን ያነጋግራል ተብሎ ይጠበቃል

• ህብረቱ ምርጫውን አይታዘብም ተብሏል

ነገረ ኢትዮጵያ
የአውሮፓ ህብረት ልዑክ ዛሬ ህዳር 11/2007 ዓ.ም ሶስት የተቃዋሚ ፓርቲዎች መሪዎችን ያነጋገረ ሲሆን፣ በኢህአዴግ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ለማነጋገር ምሽቱን ቀጠሮ መያዙን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በአውሮፓ ህብረት የልዑል መሪ ሻንታል ሔቤሬት የተመራው የልዑካን ቡድን የሰማያዊ ፓርቲና የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነትን፣ እንዲሁም የመኢአድና የመድረክን አመራሮች ማነጋገራቸው ታውቋል፡፡

የአውሮፓ ህብረት ሶስቱን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያነጋገረበት ዋነኛው አላማ ከምርጫ 2007 በፊት ያሉትን ችግሮች ለማወቅ የሚል ሲሆን በተቃዋሚዎቹ በኩል ያሉትን ችግሮች ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚያቀርቡ ገልፀዋል፡፡

የሰማያዊና የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል የአውሮፓ ህብረት ላቀረበው ጥያቄ በርካታ ችግሮች መኖራቸውን በማመልከት፣ ‹‹የምርጫው ችግር ከአጠቃላይ የኢትዮጵያ ችግር የመነጨ ነው፡፡ በተለይ ከ1997 ዓ.ም በኋላ ሚዲያውን፣ ሲቪክ ተቋማቱንና ተቃዋሚዎችን ለማፈን መሳሪያ የሆኑ አዋጆች የአገሪቱን ፖለቲካ አበላሽተዋል፡፡ በምርጫው ላይ የተፈጠረው ችግር የዚህ ሁሉ ድምር ነው›› በማለት መሰረታዊ የአገሪቱ ችግሮች ካልተፈቱ ምርጫው ላይ የተደቀነው ችግርም ሊፈታ እንደማይችል እንደገለጹላቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል ከአሁን ቀደም የተደረጉትን ምርጫዎች የታዘበውና በምርጫዎች ሂደት ነበሩ የተባሉትን ችግሮች በሪፖርቱ በማካተት የሚታወቀው የአውሮፓ ህብረት ስለ ምርጫው ሁኔታ በቅርቡ ስላወቀና ቀድሞ ስላልተጋበዘ ምርጫውን እንደማይታዘብ የተቃወቀ ሲሆን በአንጻሩ የአፍሪካ ህብረት ምርጫውን እንደሚታዘብ ከወዲሁ ለመረዳት ተችሏል፡፡

Filed in: Amharic