>

ወያኔና ይሉኝታ አይተዋወቁም [አንተነህ መርዕድ-ጋዜጠኛ]

TPLF african Naziህወሃት በሻዕብያ ታዝሎ* ምኒልክ ቤተመንግስት ከገባና ኦነግንም ሆነ ሌሎቹን ጠፍጥፎ የሰራቸውን መናኛ ድርጅቶች እንኳ ሳያስቀርብ በብቻው የተያያዘው ዘረፋ፣ ሁሉን ለእኔ ብቻ ያለ ሂደቱ ያላስደነገጠው ኢትዮጵያዊ አልነበረም። ያለፉትን ስርዓቶች የተሻገሩ ሁለት አንጋፋ ጓደኛም ጋዜጠኞች ሲጨዋወቱ በቦታው ነበርሁ። አንደኛው ወያኔ ነፃ አወጣዋለሁ ከሚለው ከኩሩው ኢትዮጵያዊ ከትግራይ ህዝብ አብራክ የተገኘ ነበርና “ወንድሜ ይሉኝታ በትግርኛ ምንድን ነው የሚባለው?” ሲል ጠየቀው። “ይሉኝታ..ይሉኝታ…” እያለ ቃሉን ማፈላለግ ሲጀምርና ፈጥኖም ቃሉን ማግኘት ሲሳነው “ተወው ወንድሜ የሌለውን ነው የጠየቅሁህ ቃሉ ከሌለ ወያኔዎች ከየት ይማሩታል ብዬ ልጠብቅ” በማለት ሁላችንንም አሳቀን።
ለነገር ማሳመርያነት አነሳሁት እንጂ ይሉኝታማ ኢትዮጵያዊ ባህል ነው። ወያኔ ከመፈጠሩ በፊት ሆነ ስልጣን ከያዘም በሁዋላ በርካታ የሰሜን ወንድሞቼና እህቶቼ ጋር ኑሬአለሁ። የሚታወቁበት ትልቁ ኢትዮጵያዊ ባህላቸው ይሉኝታቸው ነው። የወያኔ መሪዎች ካባቶቻቸው ያልወረሱት ኢትዮጵያዊነታቸውንና ይሉኝታቸውን ነው። የትግራይ ህዝብ የሚታወቀው ከቀሪው ወንድሙ ኢትዮጵያዊ ጋር ተባብሮ አገሩን ሲያስጠብቅ፣ የመከራን ጊዜ በመደጋገፍ ሲያሳልፍ እንጂ ራሱን ከሌሎች አብልጦም ሆነ አሳንሶ ሲመለከት አይደለም። ከአብራኩ ወጣን ያሉት ጥቂት የህወሃት መሪዎች ግን ትናንት ተንቆ እንደነበር ከመስበክ አልፎ ከሌሎች የሚበልጥ መሆኑን በመንገር በፈጠሩለት ማንነቱ ዙርያ ለዘላለማዊ ስልጣናቸው ጭፍን ድጋፍ እንዲሰጣቸው ያዘጋጁታል። ከተቃወማቸውም ራስን ዝቅ በማድረግ እንደተሳተፈ በመወንጀል እንዲያፍርበት ሊያደርጉ ይሞክራሉ። ለዚህም ነው በርካታ የትግራይ ምሁራን አንድም በፍርሃት ያለዚያም እነመለስ ያስቀመጡትን የማይጠቅም ይበላይነት ምናብ መዳፈር አቀበት የሆነባቸው። የተያዘው መርዘኛ አካሄድ ልጆቻቸው ነገ ቀና ብለው እንዳይሄዱ እንደሚያደርግ ሳያጡት ቀርተው አይደለም።
ሂትለር የአርያንን ዘር ንፁህና ከማንም በላይ ነው ሲል እውነት ለጀርመኖች ትልቅነት አስቦ አልነበረም። ጠቅልሎ የያዘውን ስልጣን ለማቆየት የዋህ ጀርመኖች በጭፍን እንዲደግፉትና እንዲታወሩ፣ በፈጠረላቸው የምዕናብ ዓለም እየማለሉ እውነቱን እንዳያዩ በመሆኑ ይህንን ያልደገፉትን የበላይነታቸውን የሰበካቸውን ጀርመኖች ሳይቀር አይቀጡ ቅጣት አድርሶባቸዋል። ጀርመኖች ከውድቀታቸው በኋላ በዓለም ፊት አንገታቸውን ቀና እንዳያደርጉ፣ አባቶቻቸው በሠሩት ስህተት ልጆቻቸው እንዲያፍሩበትና ይቅርታ እንዲጠይቁ ተደርገዋል። በጊዜው “ኸረ ይህ ነገር ትክክል አይደለም፣ ሰው ሁሉ እኩል ነው፣ ጀርመኖች ከሌላው አንበልጥም፣ ሌላውም ከኛ አያንስም፣ በሌሎች ላይ የሚሰራውን ግፍ አንቀበልም” የሚል እውነት ገኖ እንዳይወጣ በዚህ መርዘኛ የዘር ልክፍት የተበከሉ ውርጋጦች ጩኸት ሰማየ ሰማያትን ሞልቶ፣ ሰይፋቸው ማንንም ተቃዋሚያቸውን ለመቅላት ሲወናጨፍ በፍርሃትና ባርምሞ የተቀመጡ ብዙ የሆኑትን ያህል ታላላቅ የተባሉ ምሁራን ሂትለርን ለመሰለ መሃይም በአገልጋይነት ተንበርክከዋል። እነዚያ አገልጋዮች እስከ ዛሬ ከየተደበቁበት እየታደኑ በዘጠና ዓመታቸው ሳይቀር ፍርዳቸውን ሲያገኙ የዛሬ ጀርመኖች ዓለምን ተባበሩ እንጂ ትክክል ናቸው ብለው ከጎናቸው አልቆሙም።
ወያኔዎች ስልጣን በያዙ ማግስት ጎንደር ከተማ ጣልያን የተከለውን የበሰበሰ አሮጌ ጄኔሬተር ነቅለው ወደ ትግራይ ሲወስዱ ለትግራይ ህዝብ ይጠቅማል ብለው አልነበረም። ገና ሲነቀልና ሲጫን ፍርስርሱ የሚወጣ መሆኑን ያውቁታል። ዋናው ዓላማቸው ዮሃንስ አንገታቸውን ሰጥተው ያጸኑትን የጎንደርና የትግራይ ህዝብ የቆየ አንድነት ለመበጠስ ነው። ስልጣን ላይ ያሉትን ወያኔዎች እንተውና በጊዜው የዚህ እኩይ ተግባር ተዋናይ የነበረውን ስዬ አብርሃን “ለምን ጥቅም ነበር የወሰዳችሁት?” ብሎ በመጠየቅ እውነቱን የሚናገር ከሆነ መስማት በተቻለ ነበር።
ሰሞኑን ኢሳት የምስራቅ አፍሪካ በይነ መንግስታት (ኢጋድ) ተወካዮች ሁሉም የትግራይ ተወላጆች ናቸው ሲል ዜና አቅርቧል። ዜና የሆነው ለኢሳት ነው? ወይስ ለኢትዮጵያ ህዝብ? ብሎ መጠየቅ የተገባ ነው። በውጭ ለሚኖረው ኢትዮጵያዊ እንኳ ዜና መሆን አይችልም። ምክንያቱም በየትኛውም ውጭ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጉዳዩን ለማስፈፀም የሄደ ሁሉ ኤምባሲው በማን እንደተሞላ በቀላሉ ያየዋልና። አውሮፓና አሜሪካ ቤት የሚገዙት፣ ቢዝነስ የሚከፍቱት አዳዲስ ስደተኞች እነማን እንደሆኑ ያውቀዋልና። አባዱላ ገመዳና ጥቂት ኦህዴዶች የተወረወረችላቸውን ፍርፋሪ ሲሻሙና ሲሻኮቱ ቀልባችን ተስቦ ሳለ ድፍን ኦሮምያን መሬት ቱባ ህወሃቶች ወስደውት ብታገኙ፣ የጋምቤላን ደን ከነነዋሪው ጨፍጭፈው ዐይናችንን ካራቱሪ ላይ ተክለን ሳለ በነጋታው ባንድ ቋንቋ ተናጋሪ ህወሃቶች ሁሉም መሬት ተይዞ ብናገኘው፣ የአዲስ አበባ ክፍት ቦታ ሆነ ነዋሪው ያለበት ለልማት ነው ተብሎ በማፈናቀል ጄኔራሎቹና ትልልቅ ካድሬዎች የሰማይ ጠቀስ ፎቅ ባለቤት ቢሆኑና አዲስ አበባ ጠብባቸው ከኦሮምያ ዞን ገበሬ ማፈናቀል ቢያምራቸው የተቃወማቸውን አምቦ ላይ ቢጨፈጭፉ ለምን አዲስ ይሆንብናል? የመለስን ቦታ ማን ይይዘው ይሆን በሚል እሳቤ ሰው ሁሉ ስራ ሲፈታ ያለ ጠቅላይ ሚኒስትር አቅራቢነት ከትግርኛ ተናጋሪዎች ብቻ ጄኔራሎች ሲሾሙ ለምን እንደነግጣለን? ሃያ ሶስት ዓመት ሙሉ የሚደረገው አንድ ዓይነት ነገር ሆኖ በየቀኑ ለምን ዜና ይሆናል? የተያዘው ነገር የትግራይ ህዝብ ከቀሪው ኢትዮጵያዊ የተለየ ተጠቃሚ በማስመሰል መለያየትና ያለነሱ ስልጣን ላይ መቆየት የትግራይ ህዝብ ህልውናው እንደማይጠበቅ በማስፈራትና በማሳመን ሙሉ ድጋፉን እንዲሰጣቸው ነው። ልክ ሂትለርና ጓዶቹ እንዳደረጉት። ከትግራይ ህዝብ መካከል ለህሊናው፤ ለእውነት የቆመ ብቅ ሲል ይቀጠፋል። አብርሃ ደስታን ያዩአል። ለሌሎቹ ለህሊናቸው የተገዙ ትግርኛ ተናጋሪዎች ሊተላለፍ የተፈለገ መልዕክት ነው።
ከአስራ አምስት ዓመት በፊት ከከርቸሌ ፍርድ ቤት ከሚያመላልሱን ህወሃቶች አንዱ ጠጋ ብሎ ያዋራኝ ነበር። የምንጽፈው ሁሉ የትግራይ ህዝብ የበለጠ ተጠቃሚ እንደሆነ አድርገን መሆኑን ሊነግረኝ ሞከረ። እኛ የምንጽፈው ሆነ የምንናገረው ከዚያ በተቃራኒ እንደሆነ አስረዳሁት። የተወያየነው ብዙ ቢሆንም ጭብጡ እንዲህ ነበር። እያንዳንዱ የትግራይ ቤተሰብ አንድና ሁለት ልጆቹን ለዚህ ትግል ገብሯል፣ የጋገራትን ቂጣ፣ የቆላትን ጥሬ አካፍሏችሁ ለዚህ በቅታችኋል። ከበርካታ ሺህ ወያኔዎች የጥቂቶች ህይወት ብቻ ተቀይሯል። እንኳን ጠቅላላው የትግራይ ህዝብ ይቅርና አንተና መሰሎችህ እንኳ ይዛችኋቸው የመጣችሁልንን መኳንንትና እነሱ የሚያስሩንን ከመጠበቅ የምትገላገሉ አይመስለኝም። አይደለም ያንን ሁሉ በወጣህ በወረድህበት ገደላገደል የሚኖሩ ትግራዋይን፤ የቅርብ ቤተሰብህን የሚያረካ ነገር የማድረግ አቅም የለህም። አንተና አለቆችህ በሌሎች ኢትዮጵያውያን በምትፈጽሙት ግፍ የትግራይ ህዝብ ርሃብ ቢጠናበት እንኳ ተሰድዶ ነፍሱን ማትረፍን እንዲፈራ፣ ሌሎችም በጥርጣሬ እንዲያዩት አደረጋችሁ። የወንድማማችነት ገመዱን በጠሳችሁ። በማለት ስሞግተው አንገቱን ከደፋበት ማቅናት ተሳነው። እውነቱ በርግጥ ገዝፎ ታይቶት ይሆን? ያ አጃቢዬ ዛሬ አንድም እንዳልሁት አሁንም የጌቶቹና የእስረኞች ጠባቂ ነው። ቀንቶት ሚሊየነር ከሆነም የሱ ኑሮ ጥርሾና ቆሎ እያካፈሉ ነፍሱን ላሳደሩት የትግራይ ገበሬዎች አይተርፍም፤ አስር የሚሆኑ ቤተሰቦቹን ረድቶ ከሆነም ትልቅ ነገር ነው። አዲስ በለመደው ኑሮ ተውተብትቦ ሲኳትን የቀሪውን ትግራይ ህዝብ መከራ ያከብደዋል። ሃውዜንና በሌላም የትግራይ አካባቢዎች ላይ የተጨፈጨፉ ሰዎችን አፅም ከርሻው እየለቀመ ወደ ጎን አድርጎ ዝናብ ጠብቆ በደንጋዮች መካከል በምትበቅል እፍኝ የማትሞላ እህል የሚንጠራወዝ የትግራይ ብዙሃን ከርሃብ አሁንም አልተገላገለም። ከዚችውም ኑሮው የአካባቢ የህወሃት ካድሬዎች ስቃይ ይታከልባታል።
ይህ ይሉኝታ ያጣ የወያኔዎች ዘረፋ ይዋል ይደር እንጂ ራሳቸውን መልሶ ይውጣቸዋል። ስግብግብ ፍላጎታቸው ዳርቻ ስለሌለው መከራው የበዛበት ህዝብ አሁንስ በቃኝ የሚልበት ምልክቱ እየታየ ከመሆኑም በላይ ዳር ለዳር ፍርፋሪ በመልቀም የደለቡ የኦህዴድ፣ የብአዴን፣ የደህዴን፣ የሶማሌ፣ የአፋር፣ የጋምቤላ ወዘተ ካድሬዎች ፍርፋሪው እጅ እጅ ብሏቸው ከዋናው ሞሰብ ወያኔዎች ጋር በእኩልነት መቋደሱ ስለሚያምራቸው መገፋፋቱ መናናቁ እየተከሰተ ነው። የትግራይ ህዝብም ሆነ ልሂቃኑ አዳጋው ማንጃበቡን ለማየት የሚሳናቸው አይመስልም። በተለይ ምሁራኑ ሳይማር ያስተማራቸውን ህዝብ ከወንድሞቹ እንዳይቆራረጥ በማስተማርና ድምፃቸውን በማሰማት መታደግ ያለባቸው ጊዜ አሁን ነው።
በረሃ ላይ በርካታ የትግራይ ልጆችን ሲጨፈጭፉ ምንም ያልተሰማቸው ወያኔዎች ባለፉት ሃያሶስት ዓመታት በቀሪው ኢትዮጵያዊ ደም የጨቀየ እጃቸውን በትግራይ ህዝብ ላይ ሊያብሱ ሲሚክሩ ዝም ሊባሉ አይገባም። ሰሞኑን በኢሳት እንደተከታተልነው ያንን ሁሉ ግፍ የሰሩት በጣት የሚቆጠሩት የህወሃት ባለስልጣናት በስዊድን ዓለም አቀፍ ጦር ፍርድ ቤት ክሳቸው ሊመሰረት እንድሆነ ሰምተናል። አርከበ እቁባይ፣በረከት ስምዖን፣አባዱላ ገመዳ፣ ሳሞራ የኑስ፣ አባይ ፀሃዬ፣ጌታቸው አሰፋ፣ ሌ/ጄ ታደሰ ወረደ፣ ሃሰን ሺፋ፣ ሙሉጌታ በረሄ፣ ነጋ በረሄ፣ ወርቅነህ ገበየሁ፣ ኮማንደር ሰመረ…ስማቸው ይፋ ሆኗል። እነዚህና ሌላ ጥቂት የህወሃት ከፍተኛ ወንጀለኞች ዓልም አቀፍ በሆነ መልኩ ተጠያቂ እንዲሆኑ መቅረቡ ብቻ አይደለም ትልቁ ድል። ከአሁኗ ሰዓት ጀምሮ ህዝቡ ዐይኑን ገልጦ የሰሩትን ሁሉ ወንጀል በመከታተል ለፍርድ ሊያቀርባቸው ቆርጦ መነሳት መጀመሩም ነው። ከህዝብ በግፍ የጋፈፉት ገንዘብ የሰሩትን ሃጢያት ሊሸፍንላቸው ካለመቻሉም በላይ በየትኛውም የዓለም ክፍል ቢሄዱ ከተጠያቂነት አያመልጡም። የሂትለር ናዚዎችም ከሰባ ዓመት በፊት በሰሩት ወንጀል ፍርዳቸውን ለማግኘት እስካሁኗ ሰዓት እየተለቀሙ ነው። በስሙ የተነገደበት የትግራይ ህዝብ እነሱን ደግፎ የራሱን ታሪክ አያበላሽም። ለልጆቹም ሃፍረትን አያወርስም።
በፍርሃትና በጥቅም ወያኔን የተጠጋ ሁሉ ከሚወድቅ ስርዓት ጋር አብሮ መውደቅ እንደሌለበት ማገናዘብና ወደ ህዝብ መቀላቀል ያለበት ጊዜ አሁን ነው። አምባገነኖች በተለይም ወያኔዎች ይሉኝታ የሚባል ነገር የላቸውም። ነገሮች ሲከፉ ቆይተው ለመስዋዕት የሚያቀርቡት ቢኖር በአድርባይነት የተጠጋቸውን ነው። ከራሱ በላይ ለሚያገለግለው እቃ ክብር የሚሰጥ ማን አለ? ኦህዴዶች፣ ብ አዴኖች፣ ደህዴዶች፣ አፋሮች፣ ሶማሌዎች፣ ጋምቤላዎች ወዘተ እየተባላችሁ ለፍርፋሪ የተጥጋችሁ የሞሰቡ ዋና ተቋዳሽ አለመሆናችሁን አውቃችሁ ከዘመናዊ ባርነት ራሳችሁን አውጡ።
ቀሪው ኢትዮጵያዊ እነሱ በፈጠሩልን መከፋፈል ሆነ በራሳችን ድክመት ያሳለፍነው መከራ ተጠያቂዎች ነን። ሁሉም በተደራጀ መልኩ ሆነ በግሉ ጠጠሩን ወደ አንድ አቅጣጫ ይወርውር። ወደ ዘረኛው ወያኔ። ያ ጠጠር ናዳ ሆኖ የማይገደብ ሃይል ይሆናል። ከአሁን በኋላ ከወያኔ ውጭ በሌላው ኢትዮጵያዊ ላይ ጠጠር በመወርወር ጊዜና አቅሙን የሚያባክን ካለ ከውያኔ አረመኔዎች አካል እንደሆነ ይቆጠራልና።
የኢትዮጵያ ህዝብ በልጆቹ ትግል ነፃነቱን ይጎናጸፋል!
ጸሃፊውን በ amerid2000@gmail.com ማግኘት ይችላሉ

Filed in: Amharic