ሐምሌ ፲፰ (አስራ ስምንት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የግንቦት7 ዋና ጸሃፊ የሆኑት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ከሰኔ 18 ቀን 2006 ዓም ጀምሮ ደብረዘይት በሚገኘው የአየር ሃይል ግቢ ውስጥበአንድ አነስተኛ ክፍል ውስጥ ታስረው ከፍተኛ ስቃይ እየደረሰባቸው እንደሚገኝ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።
ስለ አቶ አንዳርጋቸው የእለት ውሎ ማወቂያ ብቸኛው ዘዴ የመርማሪዎች ፊት ነው የሚሉት ምንጮች፣ እስካሁን ድረስ ምርመራ በሚያካሂዱ የህወሃት አመራሮች ዘንድ የደስታ ፊት እንደማይነበብ ገልጸዋል።
የኢህአዴግ መንግስት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የታሰሩበትን ቦታ ይፋ ለማድረግ እስካሁን ፈቃደኛ አልሆነም። የእንግሊዝ ባለስልጣናት ለአቶ አንዳርጋቸው የኮንሱላር የማማከር አገልግሎት ለመስጠት ጥያቄ ቢያቀርቡም ኢህአዴግ ባለስልጣናት ፈቃደኛ አልሆኑም።
ከዚህ በተቃራኒ ኢህአዴግ በአቶ አንዳርጋቸው እና በግንቦት7 ላይ ለሚሰራው ድራማ ግብአት ይሆን ዘነድ የተለያዩ ሰዎችን ማሰማራቱን ምንጮች ገልጸዋል። ቀደም ብለው በአገዛዙ ለስለላ ወደ ኤርትራ ተልከው እና ለተወሰኑ ወራት ግንቦት7 ትን ተቀላቅለው በመጨረሻ የኢህአዴግ የስለላ አባላት መሆናቸው ሲታወቅ የጠፉ እንዲሁም ፈንጅ ሊያፈነዱ ሲሉ ተያዙ የተባሉ እና በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎችን ለመጠቀም እንቅስቃሴ መጀመሩን ለማወቅ ተችሎአል።
የኢትዮጵያ ህዝብ በአቶ አንዳርጋቸው መያዝ ያሳየው ቁጣ ያስደነገጣቸው ደህንነቶች ለማንኛውም በሚል በደንበር አካባቢ ጥበቃቸውን እያጠናከሩ ነው። የአቶ አንዳርጋቸውን መያዝ ተከትሎ ግንቦት7ትን የሚቀላቀሉ ሰዎች መጨመራቸውንም ከድርጅቱ የወጣው መረጃ ያመለክታል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በቤልጂየም ብራሰልስ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ኢህአዴግ አቶ አንዳርጋቸውን ለመያዝ የሄደበትን እርቀት ከማውገዝ በተጨማሪ የእንግሊዝ መንግስት የአቶ አንዳርጋቸውን ጉዳይ አጥብቆ እንዲከታተል ጠይቀዋል። ኢትዮጵያውያኑ ዛሬ በአውሮፓ ህብረት ቆንስላ ጽ/ቤት ፊት ለፊት የተቃውሞ ድምጻቸውን በከፍተኛ ቁጣ ከማሰማት በተጨማሪ፣ ያዘጋጁትን ደብዳቤ ለአውሮፓ ህብረት ባለስልጣናትና ለእንግሊዝ መንግስት ኮንስላ ጽ/ቤት ሃላፊዎች አስረክበዋል።