>

ከአማራ ህዝብ የሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪ ጊዜያዊ ኮሚቴ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ!!!


ከአማራ ህዝብ የሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪ ጊዜያዊ ኮሚቴ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ!!!
ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ መንግሥት ፣ ለአማራ ብ/ክ/መ ፣ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ፣ ለአፍሪካ ህብረት ፣ ለዓለማቀፉ ማህበረሰብ ፣ ለሀገር ውስጥና ዓለማቀፍ የዜና አውታሮች ፤-
ዝምታውን ሰብረን የህዝባችንን እንባ እናብሳለን !!!
የአማራው ህዝብ ባለፉት ሃምሳ ዓመታት የኢትዮጵያ ታሪካዊና ወቅታዊ ጠላቶች ዒላማ ሆኗል፡፡
በተለይ ባለፉት 27 ዓመታት በወያኔ – ኢህአዲግ በተፈፀመበት ሁለገብ መንግሥታዊ ጥቃት በሚሊዮን የሚቆጠሩ የአማራ እናቶች መክነዋል ፣ እምቦቃቅላዎች በችጋር ቀንጭረዋል ፣ ወጣቶችና ጎልማሶች በእስርና በቶርቸር ማቅቀዋል ፣ በወጡበት ቀርተዋል፡፡
ሌሎች ሚሊዮኖች አማሮች ደግሞ ከትውልድ ቀያቸው ተሳድደዋል ፣ ጥረው ግረው ያፈሩትን ንብረት አጥተዋል ፣ በአሰቃቂና ኢሰብአዊ ሁኔታ እየተገደሉ ተጥለዋል፡፡
የአማራ ህዝብ በመላው የኢትዮጵያ ህዝብና በዓለም ማህበረሰብ ፊት በተፈፀመበት ረዥምና ስልታዊ የዘር ማጥፋት ዘመቻ ህልውናው ፅኑ አደጋ ላይ ወድቋል፡፡
 ይህ መንግሥታዊና መዋቅራዊ የዘር ጥቃት አሁንም ብዙ መስዋዕትነት ከፍሎ ለሥልጣን ባበቃው አገዛዝ አማካይነት ተባብሶ ቀጥሏል፡፡ ባለፉት ጥቂት ቀናት ብቻ አማራው ጥንተ እርስቱ በሆነው በመተከል ዞን ማንዲራ ወረዳ ህፃን ፣ ሴት ፣ አዋቂ ሳይል የበርካታ አማሮች ህይወት በአረመኔያዊ ሁኔታ በቀስት እየተወጋ እንዲያልፍ ተደርጓል፡፡
ይህንን በብሄረሰቡ ላይ ያንዣበበ የህላዌ ፈተና ለመመከትና የህዝባችንን እንባ ለዘለቄታው ለማበስ የአማራው ህዝብ ቁርጠኛ አቋም የሚወስድበት ምዕራፍ ላይ ደርሷል፡፡ ስለዚህም በነገው ዕለት በሚያዝያ 24 ቀን 2011 ዓ.ም በመላው የአማራ ክልል ከተሞች ከጠዋቱ 3፡30 እስከ – የሚቆይ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ተጠርቷል፡፡
ሰልፉ በየአካባቢው በተወሰነለት ቦታ የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግሥትና የአማራ ክልላዊ መንግሥት የአማራውን ህዝብ ከዘር ጥቃት ለመከላከል ህዝብ የሰጣቸውን ሃላፊነት በአስቸኳይ እንዲወጡና  የችግሩ መሰረታዊ ምንጭ የሆነው አማራውን ለማጥፋት የተጫነበት ህገ መንግሥት ያላንዳች ቅድመ ሁኔታ እንዲለወጥ ለመጠየቅ ፤ ይህ ባልሆነበት አማራው ራሱን የመከላከል ተፈጥሯዊ መብቱን ለመጠቀም እንደሚገደድ የሚገልፁ ዝግቶች ይከናወናሉ፡፡
በዚህ አጋጣሚ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ የአማራውን ህዝብ ጥቃት እንደራሱ ጥቃት በመመልከት ከጎናችን እንዲሰለፍ ፤ የአፍሪካ ህብረትና ዓለማቀፉ ማህበረሰብ በአማራው ህዝብ ላይ በሚፈፀመው የዘር ማጥፋት ረገድ የያዘውን አሳፋሪ ዝምታ በመስበር ይህን ለማስቆምና የህዝባችንን እንባ ለማበስ በሚደረገው ሰላማዊ ተጋድሎ ላይ በአጋርነት እንዲሰለፍ ጥሪ እናቀርባለን !!
በየደረጃው ያሉ የመንግሥት አካላትና የፀጥታ ሃይሎች ሰልፉ በሰላማዊ ሁኔታ እንዲከናወን ከየአካባቢው የአማራ ህዝባዊ ሰልፍ አስተባባሪዎች ጋር በጥምረት እንዲሰሩ ፤ የሀገራዊ ፣ ክልላዊና ዓለማቀፍ የዜና አውታሮችም በስፍራዎቹ ተገኝተው ይህንን ታላቅ ታሪካዊ ትዕይንት በመዘገብ ሞያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን !!
 ዝምታውን ሰብረን የህዝባችንን እንባ ለዘለቄታው እናብሳለን !!!
የአማራ ህዝብ ሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪ ጊዜያዊ ኮሚቴ ፣
                  ሚያዝያ 23 ቀን 2011 ዓ.ም
                              ኢትዮጵያ ፡፡
Filed in: Amharic