>

ከዘመነ መሳፍንት ወዲህ አራተኛው የታሪካችን አራተኛ ምዕራፍ!!!! (አያሌው መንበር)

ከዘመነ መሳፍንት ወዲህ አራተኛው የታሪካችን አራተኛ ምዕራፍ!!!!
አያሌው መንበር
እንደምናየው ሀገራችን ኢትዮጵያ ወደአላስፈላጊ ቀውስና መሆን ወደሌለበት ጨለማ እየተመዘገዘገች ነው።ይህ ወቅት በእኔ እይታ አራተኛው ሲሆን የአፄ ምኒልክ ዘመን፣የ1960ዎቹ እና የ1980ዎቹ ከአንድ እስከ ሶስት ደረጃን የያዙ የሀገራችን ምዕራፎች ናቸው።
አፄ ምኒልክ ኢትዮጵያ የምትባልን ሀገር ለእኛ ለማውረስ ሲሉ በጭቆና ውስጥ የነበሩትን ሁሉ ነፃነት እሰጣለው ሲሉ ብዙ ደክመው ካሸነፉ በኋላ ለነፃው ህዝብ ግን እሾህ ተክለው መሄዳቸው አይካድም።አፄ ምኒልክ ያን ጊዜ የአማራውን ጥቅም ባስከበረ መልኩ ሀገሪቱን ማዋቀር ሲችሉ ያለወቅቱ እጅግ ፍትሃዊ ሆኑ።ይሁንና ላሳዩት ርህራሄ የተከፈላቸው ውለታ 100 ዓመት ሙሉ ስማቸውን በመጥፎ ማንሳት እንጅ ማመስገን አይደለም።አፄ ምኒልክ ለአብራካቸው የአማራ ህዝብም ይህ ነው የሚባል ልዩ ነገር ሳያበረክቱ ለሌሎች እንደባዘዙ ነው ያለፉት።እንዲያውም ነፃነት የሰጡት እየቆየ ለአማራው ጠላት ሆኖት ሲሰለፍ እንመለከታለን።
የ1960ዎቹ ምሁራንም አብዛኛዎቹ የመብት አቀንቃኞች አማራዎች ሲሆኑ ለወገናቸው አማራ ያወረሱት ነገር ቢኖር ግን ትግላቸው ተጠልፎ አማራው ጨቋኝና በዝባዥ የገዥ መደብ ስምን እንዲሠጠው ማድረግ ነው።ከዛ ጊዜ ጀምሮ አማራው የፀረ ኢትዮጵያውያን ትርክት መታገያ መሰረት ሆኖ አገልግሏል።
እርግጥ እነርሱም በትግላቸው ውስጥ ከባዕድ ሀገር የወረሱትን ፍልስፍና ሳያላምጡ መዋጣቸው ትግላቸው የተዘበራረቀ እንደነበር አይካድም።ያም ሆኖ ግን አዲስ ምዕራፍ ነበር።
ሶስተኛው ምዕራፍ ደግሞ የ1980ዎቹ  ሲሆን አስተሳሰቡ የ 1960ዎቹ ሆኖ ነገር ግን በዚህ ጊዜ የአስተሳሰቡ ውጤት አደባባይ ወጥቶ አማራ እስካሁንም ድረስ በፖሊሲና ስትራቴጅ የጥቃት ሰለባ እንዲሆን ያደረገው ምዕራፍ ነው።ምንም እንኳን የምዕራፍ ሁለት ውጤት በደርግ ዘመንም አማራው ተጎጅ ቢያደርገውም በምዕራፍ ሶስት (1980ዎቹ) ግን እጅግ አደገኛ የሚባለው የህልውናው ስጋት የተረቀቀበት ነው።
የአራተኛው ምዕራፍ ጅማሮ 2007/2008 ሲሆን ይህንን የዘመናት አማራውንና የሚወደውን ሁሉ አከርካሪውን የመስበር አባዜን ያነገበ የተጣመመ እሳቤ ለመቀልበስ ከ2008 ጀምሮ ሰፊ ስራዎች ተሰርተዋል።ጥሩ ተስፋም ታይቶበታል።በተለይም አማራው ጉዳዩን በደንብ እንዲያጤነው እያስቻለው የቆየ ቢሆንም በ2010 እና በተለይም በ2011 የምናያቸው ነገሮች ግን ልክ እንደምኒልክ ዘመን አማራው ከታገለ በኋላ ለራሱ መቆም ሲገባው ለማይገባው አብዝቶ ነፃነት ሰጥቷል።
ይህ የአማራው አብዝቶ ቀናኢ መሆን ግን በምላሹ ያተረፈው ነፃነት ያላቸውንና ነፃነት የሚገባቸውን ነፃነታቸውን እየገፈፈ እንዲሄድ ቡር ከፍቷል።ይህ የታሪክ ምዕራፍ የመጭውን ሀምሳና መቶ አመት የኢትዮጵያ ሁኔታ ውስጥ ለውስጥ እየቀረፀ ያለ ሲሆን አልፎ አልፎ ለሙከራ የውስጥ ስራውን ወጣ እያደረገ ህዝቡ ላይ Test እያደረገ ነው ያለው።ይህ አራተኛው ምዕራፍና አደገኛ ጉዞን እየጀመረ ያለው እንቅስቃሴ ምልክቱ አስጊ ነው።
የFinal exam ላይ ሳንደርስ ገና ይህ ለሙከራ እየወጣ ያለውን Quiz እንኳን ብቻ ብንመለከት ሀገራችን ኢትዮጵያ ወደአላስፈላጊ ቀውስና መሆን ወደሌለበት ጨለማ እየተመዘገዘገች ለመሆኑ ይህ የስድስት ወር ጉዞ ከበቂ በላይ ምስክር ነው።
ይህ ወቅት በእኔ እይታ ብዙ ጥረውና ለአማራው የተሻለ ነገር ትተውልን ማለፍ ሲገባቸው መጨረሻ ግን አማራውን እሾህ ተክለውለት የሄዱት የአፄ ምኒልክ ዘመን እንዲሁም የ1960ዎቹ እና የ1980ዎቹ የፀረ አማራ ትርክት ቀጥሎ ለዚህ ያደረሰን የሀገርን አሰላለፍ የሚቀይር አራተኛ እና አደገኛ ምዕራፍ ሆኖ ይታየኛል።
ታድያ እነዚህ ሶስት ምዕራፎች እንዳይደገሙ አራተኛው ምዕራፍ መግቢያ ላይ ሆነን ምን እናድርግ? ብለን መጠየቅ አለብን።
በዚህ መሰረት ሌላ የዝርዝር መተግበሪያ የሚያስፈልጋቸው ሆኖ
1.ትልቁ ነገር ነባራዊ ሁኔታውን ሁሉም ትውልድ (ቢያንስ አብዛኛው እንዲረዳው ማድረግ ነው።ለዚህም እስካሁን የተፈፀሙ ስህተቶችና ወደፊት ምን ሊፈጠር እንደሚችል ጠቋሚ አመላካቾች በሰነድ መሰነድ፣ በግልፅ መነገር፣መፃፍና መተረክ አለባቸው።
2.የአማራን መከታነት የሚናፍቁበት ስትራቴጅክ አጋሮችን ለይቶ ተከታታይ ስራ መስራት ይጠይቃል።በታክቲክ አጋርም መፈለግ አለብን።ለምሳሌ የአማራው ጋር ተዛማጅ ታሪክና ስነልቦና ያላቸው ብሄሮች/ዜጎች ቀጥተኛ አጋሮቻችን ጋር  እየቀረቡ እውነቱን ማሳወቅ ይጠይቃል።
3.በውስጥም በውጭም ተከታታይ Resource Mobilization ስራ መስራት አለብን።
4.የአማራ ህዝብ አንድነትንና የስነልቦና የበላይነት ሊያመጡ የሚችሉ ተግባራትን በተከታታይ መስራት።ባለንበት ሰዓት ትልቁ ፈተና ጎጠኝነትና ሁልጊዜ ቅሬታ አቅራቢነት መስፈኑ ነው።አካባቢያዊነት እጅግ ትልቁ ፈተና ነው።ይህ ነገር በተለይ በብአዴንና በባለሀብቱ ውስጥ በግልፅ የሚታይ ሲሆን ላለፈት አራት አመት በጣም ታግለነው ቢቀንስም አሁን አሁን ብቅ ብቅ እያለ ነው።ይህንን አደገኛ ነገር መዋጋት አለብን።ሁላችንም በአማራነት መሰረት ላይ እና በእውቀት ላይ ብቻ መቆም አለብን።ሌላው ነገር ሁልግዜ ቅሬታ (Complain ) አቅራቢ ብቻ መሆን የለብንም።ከቻልን ገብተን መስራት አለብን።ካልሆነም መፍትሄ ማመላከት አለብን እንጅ ሁልጊዜ ተሳዳቢና በቁጭት ብቻ የምንናጥ መሆን የለብንም። አሁን ቢያንስ የማታገያ ድርጅቶች እና የመታገያ ሜዳ አለን።
5.የትግል መሰረታችን ወደ ሸዋ ማሻገርን በእጅጉ ማሰብ።እስካሁን የትግል መሰረታችን ብዙው ጎንደር ሲሆን ከዛም ጎጃምና ወሎ በደንብ ተቀጣጥሏል።በወቅቱ ከነበረው አንፃር ትክክል ቢሆንም አሁን ያለው ትግል ግን ይበልጥ የሚጠይቀው ሸዋን ነው።ሸዋ የሁለመናችን መሰረት መሆን አለበት።
ስለሆነም የጎንደር ጉዳይ ባለበት ቀጥሎ (በራሱ ያለድጋፍ መቆም የሚችል ነው) አሁን ፊታችን ወደ ሸዋ በማዞር የመጀመሪያው ምዕራፍ ስህተቶች ድጋሚ እንዳይደገሙ መታገል አለብን።
ለዚህ ሁሉ ትልቁ መሰረት ግን ያለንበትን ነባራዊ ሁኔታ በጥልቅ መመርመርና መረዳት ከዛም ለዚሁ መዘጋዘት ነው።
Filed in: Amharic