>

ዛሬስ"በሕግ አምላክ" እልዎታለሁ፤ (ዐቢይ ኢትዮጵያዊ)

“በሕግ አምላክ” እልዎታለሁ፤

«የሕግ ቀለም»አስፈፃሚዎችንም ዛሬም ይፈነቃቅሉልን።

 
ይቅርታ ነው ሲባል፣በፍቅር መደመር፤
ፍትህ እንደው አይቀርም፣
ሐቁ እስከሚጀመር። 
ቀረ’ኮ ይሉኝታ ቀረ’ኮ መደበቅ፤
በገዳዮች ጉያ ሕዝብ ላይ መሳለቅ።
እናም ሕዝቡን ስሙት አድምጡት ላንድአፍታ፤
ታሪክ ሳይጠራችሁ የማታ የማታ፤
ዛሬ ቁረጡና ቆማችሁ በዕውነታ፤
እንደልጅ ማዲንጎ ጠይቁ ይቅርታ።(18 July 2018)
 
ክቡር ጠ/ሚ ዶ/ር ዐቢይ አህመድ፤አቶ ወርቅነህ ቀምዚሎን ከሥልጣኑ በዲፕሎማሲ መንገድ አነሱት፤መልካም ዕርምት ነው፤አንዳንዴ እንኳን ጦማሪዎችን ይጎብኙ።ገና የውድመቱ ሂሳብ አልተወራረደም፤የነብስ፣የገንዘብ፣የንብረት፣ የሥልጣን (የሠይጣን)ብልግና ስንቱ ይነገራል?እንደው”አለ ገና”እንበል እንጂ እሱ ያደራው መረብ ከሸረሪት አሥር ዕጥፍ ነው። 
        ሕግ ምን ማለት እንደሆነ ቢያንስ ፖለቲካዊ ትርጉሙን ሳይሆን፣ጥሬ ቃሉን በማወቅ ግንዛቤ ማግኘት የማይችል ሰው አለ ብዬ አላምንም፤በተለይም በአሁኑ የኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ። ሰዎች አውቀውም ይሁን ሳያውቁ ሕግን እየጣሱ ወንጀል ሲፈፅሙ የነበሩትና አሁንም ያሉት እያወቁ መሆኑን በዕርግጠኛነት መናገር እችላለሁ።እናም ሕግ የኅብረተሠብ ሰላም  ኑሮና ጸጥታ ለመጠብቅ ከአንድ መንግሥት የወጣ መተዳደሪያ ደንብ ነው።ይሁን እንጂ:-የሕግን ኃላፊነት በዲሞክራሲ ሥም መስረቅ ተገቢ አይደለም ፤ ይህ ሲፈፀም  ግን አይተናል። 
      ሕገ ልቡናን ተሻግሮ የሰው ልጅ ዛሬም በሕሊናው መዳኘቱን አልተወ ውም፤በአብርሃማዊ ሃይማኖቶችም «ሕገ ኦሪት» ወይም በሕገ ሙሴ በተለይም አስርቱ ቃላት በወርቃማው ሕግ እንደተመሠረቱት ይተዳደራል።ይህ «ወርቃማው ሕግ» በሌሎቹም ዋና ሃይማኖቶች ተመሳሳይ ትርጉም ተሰጥቷል።ሕግ ለማድረግ የሚያዝ፣ከማድረግ የሚከለክል፤አድርጉ አታድርጉ የሚል ሲሆን፤አድርግ የሚለው ግን ትዕዛዝ ይባላል።
     በአለም ታሪክ፣ ብዙ ጊዜ የሰው ልጆች መንግሥታት አቁመው ለየራሳቸው ሕግጋት ይመሠርታሉ፤በዚህም መሠረት   በወኪሎቻቸው አማካኝነት የሚፈፀምላቸው መመሪያው “ሕገ-መንግሥት”ይባላል።  ሌላው ደግሞ  እያንዳንዱ የሕብረተሰብ አካል፣ለአቅመ አዳም ወይም ለአቅመ ሔዋን የደረሰ አባል ገፅ በገፅ አንብቦ እና ተወያይቶ በውሳኔ ሕዝብ በፊርማው ያፀደቀው ሕግ “ሕገ-ሕዝብ”ይባላል፤ይህም ሕግ የሁሉም ሕብረተሰብ አካላት አዛዥ፣የዜጎችን መሠረታዊ መብትና ግዴታ የያዘና የመንግሥትንም ኃላፊነትና ሥልጣን ጨምሮ የሚወስን ከሕገ-መንግሥቱ በላይ የሆነ የሕጎች ሁሉ ሕግ ነው።
           የሚያሳዝነው ደግሞ የሚቋቋመው መንግሥት የራሱን ሕገ-መንግሥት ይዞ፣በሕዝብ ላይ የሰው ልጅ ህጎችን በሀሣዊ መሠረት ከሆኑ፣ ለጥቂቶች ሥሥት ለማገልገል ሊሆኑ ወይም ሰፊ ጉዳት ሊያምጡ ይችላል።በድሮ ዘመን ባብዛኛው ሕግ የወጣ በንጉሥ ወይም በሌላ መሪ ቃል ይሆን ነበር፤ለዚህም ነው በ”ሕግ አምላክ!” የሚባለው። በተለይ ባለፈው 20ኛው ክፍለ ዘመን ይህን ሂደት በሥልጣኔ በማሻሻል፣ በተገዢ ሕዝቦች ምርጫ የሕግ አማካሪዎች ተመርጠው በምክር ቤት የሕግ አጻጻፍና ማረጋገጥ ሂደት በብዙዎች አገራት “ሕገ መንግሥት” ኑሯል። በሕጉ ወሰኖች ውስጥ በርካታ ሕጋዊ ኑሮ ምርጫዎች እንዲገኙ ስለ ሕዝቡ ነፃነት የሚሻ በማለት ነው።
         በኢትዮጵያ ግዛቶች ሁሉ አንዱ ጎሳ በሌላው ጎሳ ላይ ሲነሳ እና ሕዝቡ ለመፈናቀል ለመጋደል የደረሰው ለምንድነው?እንዳይመስለን የተረገምን ሆነን፤ፋሺሽት-ወያኔ ከጣሊያን በባንዳነት ተምሮ በኢትዮጵያ ላይ አልሳካ ብሎት ለሃያ ሰባት ዓመታት ሲዘራው የነበረና ለመቶ ዓመታት አቅዶልን የነበረው የደም-ገፈት ነው።እኛ ኢትዮጵያውያን ችግሩን አስቀድመን ስለምናውቅ እንወጣዋለን፤ይብላኝልኝ በትግራ ውስጥ የሚኖሩት ዜጎቻችን ትግሬዎች ብቻ አለመሆናቸውን ስለምናውቅ፤ሁሉም የዜግነት ነፃነታቸው ተገፎ እንዲሁ ይቀራል ብለን አናምንም። 
 
             «የሕግ ቀለም» ማለት የሕግ ወኪሎች የተባሉት ወይም አስመሳዮች አሳምነው በሐሳዊ ሕግ ወይም በወንጀል እርምጃ ሲወስዱ ነው።እንዲህ እንዳይደረግ፣የሕግ የበላይነት ካለና ማናቸውም ሰው ወይም ወኪል በሕጋዊ መሠረት ከሆነ ከሕጉ ሥር ተጠቅልሎ ይገኛል።ትግላቸው የሕግ የበላይነት እንዳይመጣ ነው፤ማስመሰላቸው በትልቁም በትንሹም”የሕገ-መንግሥትን ሥም”ማላዘናቸው “ሕገ-ሕዝብ”እንዳይወለድ ነው፤አዛዡ ነውና።
          ክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር፥እርስዎ መልካም-መልካሙን እና ቀና-ቀናውን መንገድ እየመረጡ፣በኢትዮጵያ የትግል ጉዞዎት ውስጥ መረማመዱን ተያይዘውታል።ተንኮለኞቹ ደግሞ የመሰሪዎቹን ጎዳና ያጣጥማሉ፤እርስዎን ሲያዩ እየተሽቆጠቆጡ የድጋፍ ፈገግታቸውንም በጭብጭባ እና በዑዑታ ያቀልጡታል።በመካከል ግን የሚሸረብበትን የሞት፣የስቃይ፣የእንግልት እና የመፈናቀል ፅዋ ይጋታል።ተፎካካሪዎች በሌላ በኩል ሥልጣን ይዘን ልናስተዳድረው ነው የሚሉት ሕዝብ በሞት እየተቆላ መሆኑን እንዳልሰሙት ተዘናግተው፣የወንበር ሸመታቸው ላይ አተኩረዋል።ከመሠረቱ ይህንን ፈንጂ ያጠመደችው ፋሺሽት ወያኔ ግን ዋሻዋ ውስጥ ተሸሽጋ ለእነ አባ ዱላና አርከበ እቁባይ በቴሌግራም ማታማታ መመሪያ ማስተላለፏን ቀጥላበታለች።ዘረኝነት ምን ያህል አስጠሊታ እንደሆነ በተግባር ያረጋገጥኩት፤የኦሮሞ እና የጌዶ ዘረኞች ከመቼው ተገልብጠው እንዲያ ሲገድላቸው፣ ሲቆርጣቸው፣ሲያፍናቅላቸው የነበረው፤ፋሺሽት-ወያኔን ወግነው የራሳቸውን ወገን በዘር ለይተው፤ ኢትዮጵያውያን እንዲጨፈጭፉ ማድረጋቸው ነው፣ “እንዲያው ከምትቀሪ ምንቸቱን አንቅሪ።”
 
     ፋሺሽት-ወያኔዎች ይህንን ተንኮላቸውን በጭራቸው ቆልፈው፤በወርቅነህ ቀምዚሎ በኩል ሲያስፈፅሙ ደጋግመን ብንጦምርም ሰሚ አላገኘንም።ዛሬ ዛሬ ያ ስንለው የነበረው የቶስ ቶስ ተንኮል ዕውነት መሆኑ ተረጋግጦ “ለትንሽ’ኮ ነው!” እያለ፤ በሥልጣን ሥም ከድንበር አልፎ ግዞት እንዲሆን ተደርጓል።አሁንም ዶክተር ጀሌው ቀምዚሎው መዋቅሩን ዘርግቶ መሄዱን እንዳይዘነጉት፤የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሙሉ ተበክሏል፤ሁሉም አምባሳደሮች ቀድሞም ተመርዘዋል፤ይህንን ሐቅ ለንደን የኤምባሲያችን ትውውቅ ስብሰባ ላይ በብሌኗ በአይናችን አየነው፣በሕውሃት ምትክ ዖህዲድ(ኦዶፒ)ወንበሩን ሲጠራርግ።ጉዳዩ የብሔር ሳይሆን የፋሺሽት ወያኔ ቅጥር አገልጋይ ሆኖ ሲያሳድደን የ”ነበረው የፖለቲካ ክፍል ኃላፊ”ተብሎ ባደባባይ መርዶ ተነገረን፤መቼም ዲሞክራሲ ዩኬ ነፍ ነው”እባብ”እያልን ስናጋልጥ ኣምባሳደሩ ያልጠበቁት ነገር እንደተሰማቸው አይተናል።ይሄ ሁሉ ሽረባ የወርቅነህ ቀምዚሎ መዋቅር እንደሆነም ይታወቃል፤እርሱ ላይመለስ ተጋልጦ:-ከሙስናው በዘለለ፤ገና የሰኔው ግድያ ውስጥ እጁ ይኑር አይኑር እየተጣራ ይገኛል።
     ያም ሆነ ይህ ወደለንደን እንደሚመጡ እየተነገረ ቢሆንም ውስጥ ውስጡን ድመትም አውሬ ነችና ካስመሳዮቹ ጋር እዚህ ለንደን ትግሉ ተጧጥፏል፤እርስዎ ደግ ደጉን ይመርጣሉ ካጠገብዎ ካሉት መካከል ግን ለውጡን ነቅፈው በጀሌነት፣ፋሺሽት-ወያኔ ከጀርባቸው የቆለፈባቸው ጥቂት አይደሉም።ኣብዛኛዎቹ ከርስዎ የፓርቲ ጆንያ ውስጥ በዘረኝነት ያሉ ሲሆን፤እኩሌታዎቹ ደግሞ ከዚህም ከዚያም ያኮረፉ ጀሌዎች ናቸው።ይህን ለማረጋገጥ ብዙ መድከም አያስፈልግዎትም፤ከወዲሁ አምባሳደርዎትን በዖሮምኛ አይጠይቋቸው ተቃዋሚዎቹ በትግሪኛ ሲጮሁ ይሰማሉ።በእኔ ይሁንብዎና “በሕግ አምላክ” እልዎታለሁ አስቀድመው በሚቋቋመው አዘጋጅ ኮሚቴ ላይ ጥንቃቄ ያድርጉ፤ያለበለዚያ እነዚህ«የሕግ ቀለም» አስፈፃሚዎች፤የለንደንን ዲያስፖራዎች ባደባባይ አጋጭተው ኪሳራውን ለመሰብሰብ፣እኛ የምንወድዎትን በሥርዓተ-ዓልባኛነት ሥማችንን በዓለም እንዲጠፋ አፀያፊ ተግባር ይፈፅሙብናልና ይምከሩበት።
 
ኢትዮጵያ በነፃነት ለዘላለም ትኑር !!! 
 
***«የሕግ ቀለም»ማለት የሕግ ወኪሎች የተባሉት ወይም አስመሳዮች አሳምነው በሐሳዊ ሕግ ወይም በወንጀል እርምጃ ሲወስዱ ነው።
ው/ፔዲያ ሕግ ትርጉም፤
Filed in: Amharic