>
5:13 pm - Sunday April 18, 2923

ከቀጣይ የእነ ዐቢይ መንገዶች መካከል ጥቂቶቹ!!! (ጌታቸው ሽፈራው)

ከቀጣይ የእነ ዐቢይ መንገዶች መካከል ጥቂቶቹ!!!
ጌታቸው ሽፈራው
1) “የኬኛ” ፖለቲካ መፍጠኑ በሕዝብ እንዳስጠላቸው፣ ጉዳዩን በዚህ መጠን ማፍጠናቸውና አንዳንድ መረጃዎችን (ለምሳሌ
አዲሱና ለማ በኦሮምኛ የተናገሩትን) በሚዲያ የማይነገር እንደነበር ይገመግማሉ።
ከአሁን በኋላ “የኬኛ” ፖለቲካ በሚዲያ ሳይሆን በተግባር ብቻ መፈፀም እንዳለበት “ጥልቅ ተሃድሶ” ያደርጋሉ። “የኬኛ ፖለቲካ አፈፃፀም” ላይ ችግር የነበረባቸው ግለሰቦች ይገመገማሉ። “አረጋጋው! አረጋጋው! እናረጋጋው” ተባብለው ይገማገማሉ። እንደገና ወደ ሕዝብ የሚገቡበት መንገድ ላይ ይወያያሉ። አንደኛው መወደጃ ይሆናል። እንደ “ኦሮማራ” አይነት ስልት። ሌላኛው ደግሞ ያባብሉናል ብለው የሚወስዱት ይሆናል።
ይህኛው የኦህዴድና የትህነግ ጥምረት ላይ ሊያተኩር ይችላል። እነ ኦነግና ሌሎቹ እንዲደነፉ፣ በየአካባቢው የክልል ጥያቄ እንዲነሳ፣ ግጭት እንዲባባስ ተደርጎ እነ ዐቢይ “ቆምጨጭ” ያለ እርምጃ እንወስዳለን ብለው ሲገለገሉ የሚያሳይ ድራማ ሊሰራ ይችላል። የኢትዮጵያ ሕዝብ እነዚህ ይሻሉናል እንዲል ነው!
2) ኦዴፓ በ9 ወር ውስጥ አሟጥጦ ያልያዘው ስልጣን የለም። ከዚህ መካከል ለአንዳንዶቹ እየቀነሱ ይሰጧቸዋል። “ኃላፊነትም ቢሆን የእኛ ብቻ አይደለም፣ እያጠፋ ያለው ሌላ ነው፣ አሁን ገዥው ኦዴፓ አይደለም” ለማለት ይጥራሉ። ትንሽ ትንሽ ስልጣን የተጣለላቸውን ድርጅቶች አፈ ቀላጤ አድርገው ወደ ሕዝብ ዘንድ ይልኳቸዋል። አንዳንድ ሀገራዊ የሚመስሉ ተግባራት እንደሚጀመሩ “የመሰረት ድንጋይ”ም ሆነ ሀሳብ ይጥላሉ። ከኬኛ ፖለቲካ አስፈፃሚዎች መካከል አንዳንዶቹን ለይምሰል “አጥፍተዋል” ይሏቸዋል።
 ዐቢይ የለገጣፎውን ጉዳይ “አልሰማሁም” ብሎ እንደሸመጠጠው የሚክዷቸው ሀቆች ይኖራሉ። ከራሳቸው አውርደው ለይስሙላህ ስማቸውን ለሚያድሱላቸው አንዳንድ መስዋዕቶች ይሰጧቸዋል!
3) በተቻለ መጠን ሕዝቡ የኢትዮጵያን ጉዳይ የሚረሳባቸው አጀንዳዎችን ይፈጥራሉ። ኢትዮጵያን አንድ ልናደርግ ነው ብለው የኬኛ ፖለቲካቸውን ሲያካሂዱ እጅ ከፍንጅ ስለተያዙ አሁን የፕሮፖጋንዳ አውደ ውጊያ ይቀይራሉ። ሕወሓት ወደመጨረሻው ያደረገው ይህን ነው። “እንኳን ለኢትዮጵያ ለምስራቅ አፍሪካ፣ ለአፍሪካ፣ ለዓለም ይበቃሉ” መባል ይፈልጋሉ። ሀገር ውስጥ ያለው የድጋፍ ምንጭ ሲደርቅ በቱቦ ከውጭ አምጥተው የኬኛ ችግኛቸውን ያጠጣሉ። ይህ የኢትዮጵያን ሁሉ እየናቀ የሌላውን ለሚያሞግስ ልቡ የተሰደደ ሕዝብ ዘንድ የቅቡልነት አማራጭ ነው ብለው ያስባሉ። ወደ ክፍለ ሀገር ከተሞች ከማቅናት ይልቅ ወደ ጎረቤት ሀገር ይመላለሳሉ።
ከውጭ አካላት ጋር በመተባበር፣ በብድር……ወዘተ አዳዲስና ሚዲያ የሚያጮሃቸው ፕሮጀክቶች ተጀመሩ ይባላል! ኢትዮጵያ፣ ኢትዮጵያ እያሉ ጎጥ ላይ እንዳላገኘናቸው ወደ ወጭ ወጣ ወጣ ብለው ኢትዮጵያን ከመንደርነት ወደ አለም መድረክ መለስናት ለማለት ብዙ ብዙ ይነግሩናል!
4) አራተኛው አይን ያወጣ ነው። “ተነቅቶብናል፣ የያዝነውን አንጥልም” ብለው ወደፊት ያለ ሀፍረት ይሮጣሉ። ” ሕዝብ ምን ያመጣል?” ብለው የኬኛ ፖለቲካ “ኢትዮጵያዊ ሱሴ” ፕሮፖጋንዳን ደርምሶ እንዲያልፍ ያደርጋሉ! ይህን ሲያደርጉ ሕዝብን በአጀንዳ ይወጥሩታል። በተለያየ የፖለቲካ ጉዳይ ይወጥሩታል። የወልቃይት እና ራያ ጥያቄን ላይ ፌደራል መንግስቱ የያዘውን ቸልታ በማጠናከር ብቻ ሳይሆን ደባም ጨምሮበት የትግራይና የአማራ ሕዝብ መካከል ውጥረት እንዲፈጠር ይሆናል። ደቡብ በየቦታው ጥያቄ እንዲያነሳ፣ የሀዋሳና ሌሎች ጉዳዮች መጫወቻ ካርድ ይሆናሉ! የሶማሊያና የአልሸባብ ዶሴ አቧራው ተራግፎ ይነሳል።
ሱዳን ጦሯን ወደ ኢትዮጵያ ታስገባ ዘንድ ሴራዎች ይደረጋሉ! ሕዝብ በዚህ በዛ ሲባክን ከኋላው የተወውን የኬኛ ፍላጎት በደንብ ያነሳሉ።
ሕዝብን ከአጀንዳ ከመወጠር ባለፈ የለየለት “የ150” አመት ፖለቲካ ትርክትና ጥላቻ በአንድም በሌላ መንገድ እንዲነሳ ያደርጋሉ። ዐቢይ “መንግስቴ ተነካ ብሎ ሊመጣ ነበር” ያለውን ሕዝብ ከጎናቸው መሆኑን ይነገሩናል “ቄሮ” የተጋነነ ጥያቄ እንዲያነሳ፣ አዲስ አበባን “እናስርባታለን፣ እናስጠማታለን” ማስፈራሪያን ከአቅማቸው ውጭ የሆነ በሚመስል ሴራ ይሞካክሩታል። በሚዲያ ወጥተው “ብለን ነበር” የሚሉ ፊት አውራሪዎችን ያሰማራሉ።
 አንዳንዴ “አንተም ተው አንተም ተው” እያሉ፣ በሌላ በኩል “ልዩ ጥቅም ሲከበር እናንተም ጥቅማችሁ አይቀርባችሁም” ብለው አዲስ አበባን “ማስራብና ማስጠማት”ን እንደ ትልቅ መደራደሪያ ይጠቀሙበታል!
Filed in: Amharic