>
5:13 pm - Thursday April 19, 3708

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አሕመድ የጥምቀት በዓልን አስመልክተው ያስተላለፉት ልዩ መልዕክት!

• የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አሕመድ ለክርስትና እምነት ተከታዮች ለጥምቀት በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዐቢይ አሕመድ፣ ለክርስትና እምነት ተከታዮች ያስተላለፉት መልዕክት
ለመላ የክርስትና እምነት ተከታይ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ በሙሉ እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ!
በሀገራችን በድምቀት ከሚከበሩትና ኅብረ ብሔራዊ አንድነታችንን ከሚያሳዩት በዓሎቻችን ውስጥ አንዱ የጥምቀት በዓል ነው፡፡ ቀደምት አባቶቻችን እና እናቶቻችን ይህንን በዓል እንድናከብር ሥርዓት ሲሠሩ በአንድ በኩል በትህትና ስለ ዝቅ ማለት እና ስለ መለወጥ፣ በሌላም በኩል ደግሞ ስለ መደመር ሊያስተምሩን የፈለጉ
ይመስለኛል፡፡ የቃና ዘገሊላን በዓል ያስከተሉትም መለወጥ ምን ማለት እንደሆነ ይበልጥ እንድንረዳው ነው፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠና ዘጠኙን ነገደ መላእክት ትቶ በባሕር መካከል ተገኘ እንላለን፡፡ ዝቅ ያለው ከፍ ሊያደርገን፣ የወረደውም ሊያወጣን ነው፡፡ ሕዝባችን ወደ ሥልጣኔ ሠገነት ከፍ እንዲል ከፈለግን፣ እኛ ዝቅ ማለት አለብን፡፡ መውረድ አለብን፡፡ ሳይወርዱ መውጣት፣ ዝቅ ሳይሉ ከፍ ማድረግ ፈጽሞ አይታሰብም፡፡ እርሱ በመንበሩ ሆኖ ‹ኑ› አላለንም፡፡ እንደማንችል ያውቃልና ወደኛ መጣ፡፡ ሕዝቡን ይህንን አድርግ፣ ይህንን ሥራ፣ እንዲህና እንዲያ ሁን ማለት ለውጥ አያመጣም፡፡ ይልቅስ ወደ ሕዝቡ እንውረድ፡፡ ችግሩን እንቅመስለት፣ መከራውን እንይለት፣ ተሸከርካሪ ወንበሮቻችንን፣ ያማሩ ቢሮዎቻችንን ትተን ወደ ታች- ወደ ችግሩ ዝቅ እንበል፡፡ ሐኪሙ ወደ ሕመምተኞች፣ ባለ ሥልጣኑና ባለ ሞያው ወደ ባለ ጉዳዮች፣ ሥራ አስኪያጁ ወደ ተራዎቹ ሠራተኞች፣ መምህሩ ወደ ተማሪዎች፣ በአጠቃላይም አገልጋዩ ወደ ተገልጋዮች እንውረድ፡፡ ሕዝቡን ወደ እኛ ውጣ አንበለው፡፡ ክርስቶስ ወደ ባሕሩ ሰው ፍለጋ ሲወርድ መላእክቱም አብረውት ወረዱ፡፡ እኛ መውረድ ከጀመርን ሌሎችም ተከትለው ወደ ሕዝቡ ይወርዳሉ፡፡ የሕዝቡንም ችግር ያያሉ፡፡ አይተውም ይፈታሉ፡፡ አስቀድሞ የሕዝብን ችግር ለመፍታት ወደ ሕዝብ መውረድ የለመደ ኑሮውም ሕይውቱም የሕዝቡ ነውና በኋላ ከሥልጣኑ ሲወርድ አይጨንቀውም- አይጠበውም፡፡ በፊትም ቢሆን ወደ ሕዝብ የወረደ እና ውክልናውም ሆነ ውግንናው ከህዝብ ነውና የመውረድ ኑሮ ግር አይለውም፡፡
ይህ በዓል የመለወጥ በዓል ነው ብለናል፡፡ ከተለወጡት ውስጥም አንዱ ውኃ ነው፡፡ የሰው ልጅ ከውሀው መለወጥ በፊት በነበረው ታሪኩ ውኃን የሚያስታውሰው በቁጣ መሣሪያነቱ ነው፡፡ የሰው ልጅ በውኃ ጠፍቷል፡፡ አሁን ግን ክርስቶስ ወደ ውኃው መጣ፡፡ የመዓቱን ውኃ የምሕረት አደረገው፡፡ በሀገራችንም ሕዝባችን በክፉ ሚያስታውሳቸው አያሌ ሞያዎችና ተቋማት አሉ፡፡ በቢሮክራሲያቸው፣ በግፋቸው፣ በማሰቃያነታቸው፣ በሰብአዊ መብት ጥሰታቸው፣ በአሳዳጅነታቸው፣ በኢፍትሐዊነታቸው፣ በአድሏዊነታቸው፣ ለተወሰኑ አካላት ጥቅም በመቆማቸው የተነሣ በመዓት የምናስታውሳቸው ተቋማት አሉን፡፡ አሁን የሚሻለን ምርጫ አልባ ምርጫ እነዚህን የክፋት መታወሻዎች እንደ ውኃው ሁሉ ወደ በረከትነት መቀየር ነው፡፡ ለመዓት የነበረው ውኃ ለምሕረት እንደተለወጠው ሁሉ በክፉ ሥራቸው የምናስታውሳቸውን ተቋሞቻችንንም ለሕዝብ የሚጠቅም ሥራ እንዲሠሩ አድርገን እንለውጣቸው፡፡ ሕጋቸውን፣ አሠራራቸውን፣ አደረጃጀታቸውን፣ ዕሴቶቻቸውን፣ አስተሳሰባቸውንና አካሄዳቸውን ሁሉ ለፍትህ እና ለእኩልነት ወደ ወገነ መልክ እንለውጣቸው፡፡
ክርስቶስ ከመንገድ ጠርጎ ያስወገደው ነገር አለ፡፡ ለውጦ እንድንጠቀምበት ያደረገውም አለ፡፡ እኛም ከመንገዳችን
ማስወገድ ያለብን ነገር አለ፡፡ ፈጽሞ እንዳንሄድ፣ ነጻ እንዳንወጣ፣ አንገታችንን እንድንደፋ፣ ቅስማችን እንዲሰበርና መንፈሳችን እንዲታወክ ያደረገውን ነገር ከመንገዳችን ገለል እናደርገዋለን፡፡ እርሱ የማይለወጥ ነው፡፡ የማይለወጥን ነገር ለመለወጥ መነሣት ነፋስን እንደሚከተል ሰው ትርፉ ድካም ነው፡፡ ግን ደግሞ ሁሉን አስወግደን አንዘልቀውም፡ በምሬታችን፣ በቁጣችን፣ በደረሰብን ግፍና መከራ ልክ ሁሉንም እናስወግድ ካልን የሚተርፈን አንዳች ነገር የለምና ሀገር ባዶዋን ትቀራለች፡፡ የተዋረደች ሀገር ከፍ እንድትል ማስወገድ ያለብን ነገር የመኖሩን ያህል መለወጥ ያለብንም ብዙ ነገር አለ፡፡ ውኃውን ሁሉ ማፍሰስ የለብንም፤ አንዳንዱን ወደ ወይን ጠጅነት እንዲቀየር ማድረግም ከሰሞነ ጥምቀት ልንወርሳቸው ከሚገቡን ቁም ነገሮች ውስጥ አንዱ ነው፡፡
በዚህ ቀን አንድ ታላቅ ሰው እናስታውሳለን፤ መጥምቁ ዮሐንስ፡፡ እውነተኛ፤ ቆራጥ፣ ፊት አይቶ የማያደላ፣
ሰው እንዲለወጥ እንጂ እንዲጠፋ የማይፈልግ፣ ለድኾች ጥብቅና የሚቆም ሰው ነው – ዮሐንስ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዮሐንስ ከመምጣቱ በፊት ብዙ ሰዎች ቀድመው መጥተው ነበር፡፡ ዮሐንስ በዚያ በረሐ ሦስት ነገሮችን ያደርግ ነበር፡፡ የሚመጡ ሰዎች ሲጠይቁት የሚገባቸውን ይነግራቸዋል፡፡ ምንን መለወጥ እንዳለባቸው
ይመክራቸዋል፡፡ ቀጥሎም ካልተለወጡ ምን እንደሚያጋጥማቸው ያስጠነቅቃቸዋል፡፡ ከዚያም ዋና ተልዕኮው
የሆነውን ማጥመቁን ይቀጥላል፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ በዋናው ተልዕኮው ላይ ሲያተኩር እንጂ ጊዜውን ከመጡት
ሰዎች ጋር በመጨቃጨቅና እነርሱንም ለማሳመን በመጣጣር ሲያጠፋ አናየውም፡፡ ለእርሱ ዋናው ጉዳይ
ተልዕኮውን መፈጸሙ ነው፡፡ በዓላማው ላይ ያተኩራል እንጂ ሰዎች በሚፈጥሩለት አጀንዳ ውስጥ ገብቶ ዘይት
እንደሚጨምቅ ግመል አታካች አዙሪት ውስጥ አይኳትንም፡፡ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን መጥተው ነበር፡፡
ቀራጮች ወይም ግብር ሰብሳቢዎችም መጥተው ነበር፡፡ ወታደሮችም መጥተው ነበር፡፡ ለሁሉም የሚገባቸውንና
ማሻሻል ያለባቸውን ነገራቸው፡፡ ከዚያም ወደ ዋናው ተልዕኮ ገባ፡፡
የኛም የለውጥ ጉዞ መርሕ ይህ መሆን አለበት፡፡ ጉልበታችንን፣ ጊዜያችንን፣ ገንዘባችንን እና ልምድ
እውቀታችታችንን በዋነኝነት ማዋል ያለብን ዋናው የለውጣችን ተልዕኮ ላይ ነው፡፡ በጎዳናችን ከሚያጋጥሙን
አይለወጤዎች ጋር ሁሉ ስንከራከር፣ ስንጨቃጨቅ፣ መልስ ስንሰጥና እነርሱን እናሳምናለን ብለን ስንደክም
አንውልም፡፡ እንዲለወጡ እንንገራቸው፤ መንገድ እናሳያቸው፤ ቅን ልብ ይዘን እንቅረባቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ያለውን ለራሳቸው እንተወው፡፡ ጎበዝ ሯጭ በመንገዱ ግራና ቀኝ ያሉ ተመልካቾች ለሚሰነዝሩበት ነገር ሁሉ መልስ  እሰጣለሁ፤ ከእነርሱም ጋር ጊዜዬን አጠፋለሁ ካለ እንኳንስ ሊያሸንፍ ሩጫውን አይቀጥልም፡፡ በለውጥ መንገዳችን ላይ በሚገጥሙን አላፊ ነገሮች ጋር ጉልበት አንጨርስ፡፡ አይነተኛው ትኩረታችን አይነተኛው ግባችን ላይ ይሆን ዘንድ የምንወስንበት ታሪካዊ ምእራፍ ላይ እንገኛለን፡፡
ዮሐንስ ለፈሪሳውያን፣ ለሰዱቃውያን ለግብር ሰብሳቢዎችና ለወታደሮች የነገራቸው ነገር የተጋነነም፣ የወረደም
አይደለም፡፡ ማረም ያለባቸውን ነገር ብቻ ነገራቸው፡፡ ዛሬ በለውጥ ጉዟችን ወቅት አንዱ ልንታገለው የሚገባን
ነገር ስሜታችንን ነው፡፡ ስሜት ዕውቀትን ከገዛው ኃይልና ጥላቻን ይወልዳል፡፡ ዕውቀት ስሜትን ከገዛው ግን
ጥበብና ብልሐትን ያመጣል፡፡ ‹ለሰይጣንም እንኳን ቢሆን የሚገባውን ስጠው› ይባላል፡፡ አንዳንድ ነገሮች ምንም ያህል ቢያናድዱን፣ ምንም ያህል ቢያንገፈግፉን፣ ምንም ያህል እንድንጠላቸው የሚያደርጉ ስሜቶች ቢመጡብን የምንናገረውና የምንሰጠው አስተያየት ግን ልከኛ መሆን አለበት፤ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ፡፡ የማይገባን ነገር መናገር ተናጋሪውንም አይጠቅምም፤ ሰሚውንም አያንጽም፡፡
ዮሐንስን ዛሬ የምናስታውሰው በምንድን ነው? በአጥማቂነቱ ነው፡፡ ዋናው ተልዕኮው እርሱ ነበርና፡፡ ስለ እርሱ
የተሳሉት ሥዕሎች ሁሉ የሚያሳዩት የእርሱን ዋና ተልዕኮ ነው፡፡ ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን፣ ከቀራጮችና
ከወታደሮች ጋር የነበረውን ነገር አያሳዩም፡፡ ሰው የሚለካው፣ የሚታሰበውም በዋናው ተልዕኮው ስኬት ነው፡፡
ይህ ትውልድ የሚታሰበው ዛሬ የተፈጠረውን ለውጥ ከሚፈለገው ግብ ላይ ካደረሰው ነው፡፡ በለውጡ መንገድ
ላይ እዚህም እዚያም ከሚነሡ ነገሮች ጋር የተነታረከውና የተጋጨው የትውልዱ መታሰቢያ አይሆንም፡፡
የሚለካውና የሚታሰበው በለውጡ ስኬት መጠን ነው፡፡ የዚህ ትውልድ ዋናው ተልዕኮም ለውጡን እና ለውጡን ተከትሎ የምናገኘውን በረከት በአግባቡ በመራበት፣ በተረዳበት እና ለፍሬ ባበቃበት ልክ እና መጠን ነው፡፡ በየዕለቱ የሚፈጠሩ አታካራዎችን ትተን እንደ ዮሐንስ በዋናው ተልዕኳችን ላይ ጊዜያችንን እናጥፋ፡፡ ዮሐንስ ክርስቶስን ለማጥመቅ የቻለው እየተከራከረ፣ እየተወዛገበ፣ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን በቀደዱለት ቦይ መፍሰስን ምርጫው አድርጎ አይደለም፤ በፍጹም፡፡ እዚያው በዮርዳኖስ ወንዝ፣ በዋናው ተልዕኮው ላይ ተሠማርቶ እያጠመቀ ነበር፡፡ ያጠምቅበት የነበረው ሥፍራ ከባሕር ወለል በታች የሚገኝ እና ፍጹም በረሀ ቢሆንም እርሱ ግን ሁሉንም ተቋቁሞ ዋናው ተልእኮው ላይ ጸንቶ ነበር፡፡ ዮሀንስንም ዮሀንስ የደረገው እና በዘመናት መሀል በአማኞች ልብ ውስጥ የተከለውም ቁልፍ ሚስጥር ዋናው አላማው ላይ የመተከሉ እውነት ነው፡፡
ትኩረታችንን በለውጥ ሥራችን ላይ አድርገን፣ የሚመጡብንን የግራ ቀኝ ጉሸማዎች እያለፍን፣ በሙሉ ዐቅማችን
የሚገባንን ከሠራን የምፈልገውን ማግኘታችን አይቀሬ ነው፡፡ ከቦታችን ሊያናውጡን፣ ከዋናው ተልዕኳችንም
ሊያዘናጉን ብዙ እንቅፋቶች ሊፈታተኑን ይችላሉ፡፡ አንዳንዶች በፈተና፣ ሌሎችም በሙገሣ ልባችንን ሊወስዱ
ይፈልጋሉ፡፡ እኛ ግን በብዙ መሰናክሎች ተከቦ፣ ሜዳልያውን እያሰበ፣ ወደ ሩጫው ፍጻሜ እንደሚገሠግሥ
ሯጭ ከፊታችን ያለውን ውብ ቀን እና በጥረታችንም የምናስመዘግበውን ጣፋጭ ድል እያሰብን በጽናት ልንሮጥ
ይገባል፡፡ በጊዜያዊ እና አልፎ ሂያጅ ነገሮች ላይ ማተኮር ውጤታችንንም ታሪካችንንም ጊዜያዊ አድርጎት ይቀራል:: በልፋታችን፣ በትግላችን እና በብርታታችን የምንቋደሰው ድል የሁላችንም የመሆኑን ያህል ተግዳሮት እና ፈተናውም የሁሉም ኢትዮጵያ ልጆች እንቅፋት መሆኑን በመረዳት እጅ ለእጅ ተያይዘን በፍቅር እና በመደመር ልንሻገረው ይገባል፡፡
ጥምቀት የሽግግር ወቅትም ነው፡፡ ለዓለም ሳይገለጥ የቆየው ክርስቶስ ለዓለም የተገለጠበት ድንቅ በዓል ነው፡፡
ለዚህም ነው የመገለጥ ወይም የአስተርእዮ በዓል የሚባለው፡፡ ጥምቀት መገለጥ ቢሆንም ክርስቶስ ለሁሉም
የተገለጠው ግን ከተጠመቀ ከዐርባ ሦስት ቀናት በኋላ ነው፡፡ ክርስቶስ በተወለደበትና ለዓለም በተገለጠበት ጊዜያት መካከል ብዙ ዘመን አልፏል፡፡ አንድ ነገር የሚጀመርበትና የሚገለጥበት ጊዜ ይለያያል፡፡ በዚህች ሀገር ውስጥ ለውጥ ለማምጣት ትግሉ ከተጀመረ ቆይቷል፡፡ ለውጡ ሕጋዊና ተቋማዊ ሆኖ የተገለጠው ግን በቅርቡ ነው፡፡
ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ለዓለም ከተገለጠ በኋላ ዐርባ የሽግግር ቀናት አልፈዋል፡፡ በነዚያ ዐርባ
የሽግግር ቀናት ብዙ ፈተናዎች ነበሩ፡፡ ብዙ ጥያቄዎችም ነበሩ፡፡ ያለንበት ጊዜም እንደዚያው ነው፡፡ የጀመርነው
የለውጥ ሂደት ሁሉም እስኪረዳው፣ ሁሉንም እስኪነካ፣ በሁሉም ቤት እስኪገባ ድረስ ብዙ ፈተናዎች፣ ብዙ
ጥያቄዎች ይኖራሉ፡፡ እርግጠኛ የምንሆነው ዋና ጉዳይ ግን ሁሉንም ፈተናዎቻችንን በድል የማለፋችን ነገር
ማለፋችን እርግጥ መሆኑን ነው፡፡
ጥምቀት ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ልዩ በዓላችን ነው፡፡ ከከተራ ቀን ጀምረን ውኃ ባለበት ሜዳ ተሰብስበን
እናከብረዋለን፡፡ ኢትዮጵያችን የሁላችንም መሆኗን የምናሳይበት በዓላችን ነው፡፡ ‹ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ…›
ብለን የየባህላችንን አልባሳት ለብሰን የምንወጣበት ደማቅ በዓላችን ነው፡፡ የሁላችንም ቋንቋ፣ የሁላችንም ዜማ
በአንድ መስክ ላይ ኅብር ሆኖ የሚቀርብበት የመደመር በዓል ነው፡፡ እዚህ አማርኛ፣ እዚያ ትግርኛ፣ እዚያ
ወላይትኛ ፣ እዚያ ጉራግኛ፣ እዚያ አገውኛ፣ እዚያ ሲዳምኛ፣ እዚያ ሶማልኛ፣ እዚያ ኦሮምኛ፣ እዚያ ኩናምኛ፣
እዚያ አፋርኛ፣ እዚያ በርትኛ፣ እዚያ አኝዋክኛ ይዜማል፡፡ ሁሉም ያለውን ይዞ ይወጣል፡፡ አንዱ ወደ ሌላው
ሄዶ ይጋራል፤ የራሱንም ያጋራል፡፡ መደመር ይሄ ነው፡፡ የጥምቀት በዓል ውበት ከመደመር ዕሴቱ የሚመነጭ
ነው፡፡ ‹የነብርን ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም› እንደሚባለው የለውጥ ጉዟችንን ይዘናል፤ የለውጡ ፋና
ይበልጥ እየተገለጠ በሄደ ቁጥር ችግሮቻችንም ይበልጥ እየቀነሱ ይሄዳሉ፡፡ በዋናው ተልዕኳችን ላይ አተኩረን
ጋሬጣዎችንና ዕንቅፋቶችን ካለፍናቸው ከባሕር ወለል በታች የጀመርነውን ለውጥ ከከፍታ በላይ እንጨርሰዋለን::
የምንጠብቀውም ሆነ የማንጠብቀው ችግር ከምንጓጓለት ግብ እንዳያስቀረን ትኩረታችንን በለውጥ ሂደታችን ላይ እናድርግ፡፡ ያንን ካደረግን በጥምቀት መስክ ላይ የምናያትን ኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች ላይ እናያታለን፡፡
ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራ፣ ተከብራና በልጽጋ ለዘላለም ትኑር!”
ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
መልካም በዓል!
አመሰግናለሁ፡፡
ጥር 10፣ 2011 ዓ.ም
Filed in: Amharic