>
5:13 pm - Sunday April 19, 2026

ሰበር ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ከትውልዱ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር (መስፍን ማሞ ተሰማ)

ሰበር ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ከትውልዱ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር

መስፍን ማሞ ተሰማ

እኛ የአባቶቻችን ልጆችና የዚህች ጎስቌላ ኢትዮጵያ ተረካቢዎች ይህንን በርግጠኝነት እንናገራለን።

እኛ በምንገነባት ኢትዮጵያ፤

  • የእኛ ልጆች እንደ እኛ ቡትቶ ለብሰው አያድጉም።
  • የእኛ ልጆች ህልማቸው ጠግቦ ማደር ሳይሆን ከምንሞላው የኢትዮጵያ ጎተራ ለተራቡት መለገስ ይሆናል።
  • የእኛ ልጆች ትግላቸው ከድህነት ማጥ ለመውጣት ሳይሆን የበለፀገች ኢትዮጵያን ዓለም ማማ ላይ ማውጣት ነው።
  • የእኛ ልጆች እርስ በርስ መፈላለጊያቸውና መፈቃቀሪያቸው ዘራቸው ሳይሆን ኢትዮጵያዊነታቸው ይሆናል።
  • አባቶቻችን ከአባቶቻቸው ተረክበዋትና አጎሳቁለዋት ያስረከቡንን ኢትዮጵያ እኛ ጎስቌላ ልጆቻቸው ግን፤ የበለፀገችና ልጆቿን ያበለፀገች፤ የተከበረችና ልጆቿን ያከበረች፤ የታፈረችና ሰው መሆንን ያስቀደመች፤ ህግ ማውጣት ብቻ ሳይሆን ለህግ የተገዛች፤ የታመነችና በዜጎቿ የምትተማመን፤ ሀገራዊ ዝርፊያንና ሀገራዊ ሌብነትን የተጠየፈች፤ አፈናንና ጭቆናን ሰብዓዊ መብት ገፈፋንና ኢሰብዓዊ ሰቆቃን ከምድሯ ያስወገደች፤ ቂም በቀልንና ዘረኝነትን ያንበረከከች፤ ሠላም ፍቅርና አንድነት የሰፈነባትን ኢትዮጵያን ለልጆቻችን እናስረክባለን!!

እናንት የዚህ ጎስቌላ ትውልድ ጋዜጠኞች ሂዱና በምድሪቱ ሁሉ ለኛ ትውልድ ይህንን ንገሩ!!!

ታህሳስ 2011 ዓ/ም (ጃንዋሪ 2019)

ሲድኒ አውስትራሊያ

mmtessema@gmail.com

Filed in: Amharic