>
5:13 pm - Thursday April 20, 9448

የአረመኔዋ ህወሓት ሳዲስትነት ከየት የመጣ ይሆን? (ዘመድኩን በቀለ) 

የአረመኔዋ ህወሓት ሳዲስትነት ከየት የመጣ ይሆን?
ዘመድኩን በቀለ 
~ ከዚህም ዘግናኝ የሳዲስቶች የግፍ ዜና በኋላ ትግራይ በድጋሚ ለእነ ዓባይ ፀሐዬ የድጋፍ ሰልፍ ትወጣ ይሆን? ወይንስ በጉያዋ የተወሸቁትን ወንጀለኞች ለፍርድ አሳልፋ ትሰጥ ይሆን?
~ ” ለሰባት ዓመት ስታሰር ዐይኔ ጠፍቷል። ልጄን አጥቻለሁ። አባቴን ሳላይ በሞት ተነጥቄአለሁ። “የትግራይ ህዝብ እንደኛው ጭቁን ህዝብ ነው። ምን አደረገ? ህዝብና  ድርጅት ይለያያል። እኛን ሲገርፉና ሲያሰቃዩ የነበሩት የህወሓት አመራሮች ናቸው” ከግፍ ሰለባዎቹ አንዱ የተናገሩት ነው።
~ ስለዚህ ጉዳይ ሀብታሙ አያሌው በተናገረ ጊዜ ” የትግሬ ጥላቻ ” ስላለበት ነው እያላችሁ ስታላዝኑ የከረማችሁ ሁሉ አሁን የሀብትሽ ምስክርነት እውነት ሆኗልና ዛሬ እርማችሁን አውጡ። የትግርኛ ተናጋሪ ሳዲስቶቹን ግፍ መንግሥት ራሱ ገድላቸውን በይፋ መመስከር ጀመሯልና ተደበቁ። ከዐማራም፣ ከኦሮሞም፣ ከደቡብና ከሶማሌም ሳዲስቶች አልነበሩም ማለት ግን አይደለም።
~ በዘጋቢ ፊልሙ ላይ ” ትግርኛ ተናጋሪ መርማሪዎች” ተባለ እንጂ የትግራይ ህዝብ አልተባለም። ትግርኛ ተናጋሪዎች ማለትን የትናንቱ ዘጋቢ ፊልም አልጀመረውም። ቀደም ሲል ትግራዋዮቹ እነ ክቡር አቶ ኃይሉ ዓርአያ ከዛሬ 14 ዓመት በፊት የተናገሩት ሀቅ ነው። እነ ነውር ጌጡ እባካችሁ እፈሩ።  ባታዝኑ እንኳ በሰው ስቃይ አታሹፉ። ልክ እንደ ሀውዜንና መርሳው ታሪክ ህዝቡ ውስጥ አትወሸቁ። ባታዝኑ፣ ባይሰማችሁ እንኳ እስቲ ኡስስስ! ጭጭ በሉ። አትንጫጩ። ጮጋ በሉ።
ይሄ ነገር ለህወሓት አዲስ ነገር አይደለም። ህወሓት እኮ ገና ትግል ስትወጣ ጀምሮ ነው መጀመሪያ የራሷ ወገን የሆኑ የተንቤን ትግሬ ልጆችን አርዳ በመብላት የጭካኔ ተግባሯን ሀ ብላ የጀመረችው። ከዚያ በኋላ ነው አቅም ስታገኝ የወልቃይት ዐማራውንና የኦሮሞን ልጆች አርዶ መብላት፣ ደማቸውንም መጠጣቱን የቀጠለችው። እናም ድርጊቱ ለህውሓት አዲስ አይደለም።
ስለ እውነት እነዚህ የህወሓት ሰዎች ግን ከምር ኢትዮጵያውያን ናቸው? ሃይማኖተኛ ለተባለው የትግራይ ህዝብስ መገለጫው ናቸው? የትግራይ ህዝብስ ልጆቹ እንዲህ ዓይነት አረመኔያዊ ድርጊት በኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ላይ እንዲፈጽሙስ ነው እንዴ የላካቸው? ህዝቡስ የዚህ ዘግናኝ ግፍ ደጋፊስ ነው ወይ ? የትግራይ እናት ይህን ዘግናኝ ግፍ ስታይ ምን ተሰምቷት ይሆን ?
በዚህ ዓይነት እኮ ደርግን ጻድቅ ነው ማለት እንችላለን። ደርግ እኮ መጀመሪያ ይጣላሃል። አንተም ትጣላዋለህ። ልደብድብህም ትለዋለህ፣ እሱም ና እንደባደብ ይልሃል። እንደምንም ቡጢ ትሰነዝርበታለህ። እሱ ወታደር ነውና ፀቡ አልመጣጠን ይልና ትሸነፋለህ። ደርግ ይፈርጅሃል፣ ቀጥሎ ይይዝሃል፣ ከዚያ ያስርሃል፣ ከዚያ ይገድልሃል። ከዚያ የፍየል ወጠጤን እያዘፈነብህ ማታ በዜና የገደላቸውን ሰዎች ስም ዝርዝር እየነገረ እርምህን እንድታወጣ ያደርግሃል። ግፋ ቢል የገደለበትን የጥይት ወጪ ወላጆችን ያስከፍላል።
የህውሓት ግን ይለያል። የዐይኑ ቀለም ያላማረውን ሁሉ ይጣላል። ይጠላል በቃ። ሊደባደብህ ሲፈልግ ኪሎ አይመርጥም። ቦታም አይመርጥም። መጀመሪያ ይፈርጅሃል። ከዚያ ያስርሃል። እስር ቤቱም በፈለገበት ሥፍራ ያዘጋጃል። የመንግሥትም የግልም እስር ቤት ስላለው ደስ ባለው ሥፍራ ያስርሃል። ከዚያ ብልትህ እንዳይሠራ ዘርም እንዳትተካ ያኮላሽሃል። ሁለቱንም እግርህን በቁምህ ይጎምደዋል። ወላጅ እናታህን ወኅኒ አስገብቶ ይገድልብሃል። ቀጥቅጦ የነርቭ ታማሚ ያደርግሃል። 7ወር እግርህን በሰንሰለት አንጠልጥሎ እንደ ዶሮ ተዘቅዝቀህ እንድታሳልፍ ያደርግሃል። ከ22 ግሮሰሪ የሰከሩ ሰዶማውያን ጓደኞቹን አስመጥቶ እጅና እግርህን አስሮ በእስረኞች ላይ ግብረ ሰዶም ይፈጽምብሃል። ያስፈጽምብሃል። ጆሮህ እንዲደነቁር፣ ዐይን እንዲታወር፣ ኩላሊትህ እንዲፈርስ አድርጎ በቁምህ ያሰቃየሃል። በተለይ ዐማራ ከሆንክ እንደ የኔታ እንደሥራቸው አግማሴ ትግራይ ወስዶ ከምድር በታች አስሮ ለ25 ዓመት በወኅኒ ይቆልፍብሃል።
በሴት ልጅ ማኅፀን ብረትም እንጨትም እየከተተ ማኅፀኗን እንዳይሠራ ከጠቅም ውጪም ያደርጋል። እስረኛ አስሮ በፊቱ ላይ ሰገራና ሽንቱን ይፀዳዳል። የምትወዱትን ወንድማችሁን ከፎቅ ላይ ወርውሮ በአደባባይ በህዝቡ ሁሉ ፊትና በእናንተም ፊት በአስፓልት ላይ አስተኝቶ በአይፋ መኪና ጨፍልቆና ደፍጥጦ ለቀብር እንዳይመች አድርጎ ይገድለዋል። እንጦጦ ጫካ ወስዶ እርቃናችሁን ከግንድ ጋር አስሮ ያሳድርሃል። ገርፎህ ሲያበቃ ከነ ቁስልህ በጉንዳን እንድትወረር ያደርግሃል። በብልትህ ላይ ሃይላንድ ውኃ ያንጠለጥልብሃል። ራሱ አስሮህ ሲያበቃ ደብዛህንም ካጠፋህ በኋላ ከቤተሰብህ ጋር ሆኖ ሲያፋልግህ ይውላል።
የሚገርመው ዳኛው እሱ ነው። መርማሪው ራሱ ነው። ዐቃቤ ህጉም እሱው ነው። ፖሊሱም እሱው ነው። ምስክሩም ራሱ ነው። ይይዝሃል፣ ያስርሃል፣ ይመሰክርብሃል። ያስፈርድብሃል። ይፈርድብሃል። ሀኪሙም እሱ ነው። መርፌ ወግቶ ያበላሽሃል። እግርህን ቆርጦ በስህተት ነው ይቅርታ ብሎ ጤነኛውን እግርህን ደግሞ ይቆርጥና በእንፉቅቅህ እንድትሄድ ያደርግሃል።
ህውሓት ጋዜጠኛም ነው። ከፍርዱ በፊት እኔ ነኝ ያለ ዶክመንተሪ ፊልም ይሠራብሃል። ” ጅሃዳዊ ሀረካት፣ አዲስ አበባን እንደ ባግዳድ” ብሎ የቢን ላዲን ታናሽ ወንድም አድርጎህ ያሳቅቅሃል። ጊዜ ደጉ ይኸው ራሱ በቀደደው ጅቡ ገብቶ የእጁን እያገኘ መጥቷል። ብድር በምድር አለ ሌኒን። ይኸው ነው።
ህውሓት ቄስም ይሆናል። መስቀል ጨብጦ ቤተመቅደስ ጉብ ብሎ ታገኘዋለህ። መነኩሴም ባህታዊም ይሆናል። ዋልድባ ድረስ ገብቶ እስከ አበምኔት ድረስ ይዘልቃል። ጳጳስም ፓትሪያርክም ከመሆን የሚያግደው የለም። ሲፈልግ ንስሃ አባት ሆኖ ያናዝዝሃል። ሲፈልግ መስቀል አውጥቶ ይገዝትሃል። እንደፈለገው ይነዳሃል።
ህውሓት እንደ ሼኮች ጠምጥሞ የመስጊድ አለቃም ይሆናል። አስሮህ ወኅኒ ካስገባህ በኋላ ፓስተርም ሆኖ መጥቶ ፓስተር አድርጎህ ከወኅኒም ያስወጣሃል። አሽከሩ፣ ባሪያው፣ አገልጋዩና ታዛዡም አድርጎ ይገዛሃል ይነዳሃልም።
ህውሓት ባለሀብት ነው። ያውም ገንዘብ በጆንያ የሚያመርት ባለሃብት። በግፍ በገነባው ህንፃ ምድርቤት ሥር የግሉን እስርቤት ገንብቶ ለአጋንንቱ የሰው ደም የሚገብር ርኩስ። በ8 ወር አራስ ልጁ ስም ሦስት ቪላ የሚገነባ ጨካኝ። በ3 ዓመት ልጁም ስም በባንክ 8 ሚልየን ዶላር የሚያስቀምጥ ደፋር። ሌባ፣ ሞላጫ ሌባ፣ ጨካኝ አረመኔ ነው። ቢበቃኝስ። እዚህ ላይ ካላቆምኩት የእሱ ጉድ እንዲህ እንደዋዛ በቀላሉ የሚቆም ነገርም አይደለም።
ሻሎም !  ሰላም ! 
ታህሳስ 3/2011 ዓም
ከራየን ወንዝ ዳር።
Filed in: Amharic