>

የመፍረስ አደጋ የተጋረጠበት የደቡብ ክልል  (መስከረም አበራ)

የመፍረስ አደጋ የተጋረጠበት የደቡብ ክልል

መስከረም አበራ

የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ክልል ሃገሪቱ ካሏት ከሰማኒያ በላይ የሚሆኑ ብሄረሰቦች ውስጥ ከሁለት ሶስተኛ በላይ የሚሆነውን የያዘ ነው፡፡ በክልሉ ከሃምሳ ስድስት በላይ ብሄረሰቦች እንደሚኖሩ ይገመታል፡፡ የዚህ ክልል አከላለል ከሌሎች ስምንት ክልሎች የተለየ ነው፡፡ ሌሎቹ የሃገሪቱ ክልሎች በቋንቋቸው ስም የወጣላቸው ናቸው፡፡ የክልሉ ዋነኛ ባለቤቶችም ክልሉ የተሰየመበትን ቋንቋ የሚናገሩ ብሄረሰቦች እንሆኑ አንዳንዶቹ በየህገመንግስታቸው አውጀውዋል፡፡ያላወጁትም ቢሆኑ በተግባር ይህንን ካወጁት በተመሳሳይ የክልሉ አንደኛ ደረጃ ባለቤት የሆነ ዘውግ ያላቸው ናቸው፡፡ ሁለተኛው እና ዋነኛው ልዩነት ግን ከሃምሳ በላይ የሚሆኑ ዘውጎች በአንድ ክልል ተደርገው መከለላቸው ነው፡፡ በተጨማሪም እነዚህ በርካታ ብሄረሰቦች ደኢህዴን በሚባል አንድ ፓርቲ ስር እንዲተዳደሩ ሆኗል፡፡ ይህ ሲደረግ ደኢህዴን በሚባለው እምቅ ፓርቲ ውስጥ ከሃምሳ በላይ የሚሆኑት ብሄረሰቦች እንዴት ባለ ሁኔታ በፍትሃዊ የስልጣን ክፍፍል እንደሚወከሉ የተቀመጠ ነገር የለም፡፡ አለ ከተባለም ሲሰራበት አልታየም፡፡

‘ሌላው በየብሄረሰቡ ክልል ተሰይሞለት እኛ በአቅጣጫ በተሰየመ ክልል ውስጥ የምንኖረው እንዴት ነው?’ የሚለው ነገር በክልሉ ውስጥ በሰፊው ሲብላላ የኖረ ነገር ነው፡፡ ሆኖም ከሲዳማ ብሄር ልሂቃን በቀር በሌሎች የክልልሉ ነዋሪ ብሄረሰቦች ዘንድ የራስን ክልል የመመስረቱ ነገር ብዙ ጎልቶ የሚነሳ ነገር ሳይሆን ኖሯል፡፡ የዚህ ምክንያቱ በክልሉ ያሉ ልሂቃን እና ምሁራን በአመዛኙ የብሄር ማንነትን ከማጉላት ይልቅ በኢትዮጵያዊ ማዕቀፍ ውስጥ ሆኖ ሃገራዊ ነገርን የማስቀደም ዝንባሌ ያላቸው በመሆናቸው ነው፡፡የደቡብ ክልል ልሂቃን የፖለቲካ ትግል ውስጥ ሲገቡም ከዘውግ ፓርቲ ይልቅ ህብረ-ብሄራዊ ፓርቲን ወደ መቀላቀሉ ያደላሉ፡፡ ይህ በአክራሪ የኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ የማይወደድ የደቡብ ክልል ሊሂቃን/ምሁራን ዝንባሌ ነው፡

Map of Southern Nations Nationalities and Peoples Regional State (SNNPRS) displaying administrative zones and special woredas

አፄ ምኒልክ ደቡብ ምዕራባዊ ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ገዝተዋል በሚል ተረክ ላይ ትግላቸውን የመሰረቱት አክራሪ የኦሮሞ ልሂቃን እና ምሁራን የደቡብ አቻዎቻቸው ፈለጋቸውን ተከትለው ምኒልክን የመርገሙን ፖለቲካ እንዲያፋፍሙ ይከጅላሉ፡፡የደቡብ ልሂቃ በአንፃሩ የነፍጠኛው ብቻ ጉዳይ ተደርጎ የሚቀርበውን ኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት አንደኛ አድርገው የዘውግ ፖለቲካን ችላ ይላሉ፡፡ እንደውም ለኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ዘበኛ ተደርጎ ከሚቆጠረው የአማራ ክልል እኩል አንዳንዴም በሚልቅ ሁኔታ በደቡብ ክልል ኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ይቀነቀናል፣ ከዘውግ ማንነቶች ይልቅ የሃገር ምልክቶች ይጎላሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ከደቡብ የማይወለደው ኢትዮያዊ ወደ ሌላ ክልል ከማምራት ይልቅ የዘውግ ነገር ዋና ጉዳይ ወዳልሆነበት ደቡብ ክልል መኖርን ይመርጥ ነበር፡፡ ይህ ለክልሉ ማደግ ያበረከተው አስተዋፅኦ አለው፡፡ ክልሉ ለህብረ-ብሄራዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም እንደልባቸው የሚንቀሳቀሱበት ዋነኛ መሰረታቸው ነው፡፡

የደቡብ ህዝቦች፣ ልሂቃን እና ምሁራን ወደ ኢትዮጵያዊ ብሄረተኝነት እንዲያዘነብሉ ያደረጓቸው ብዙ ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ እና ስነ-ልቦናዊ ምክንያቶች ይኖራሉ፡፡ ኢኮኖሚያዊውን ምክንያት ብናይ አካባቢው እንደ ቡና፣ ፍራፍሬ፣ ቅመማቅመም ያሉ የገበያ ምርቶች (Cash Crop) በአብዛኛው የሚያመርት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከዘውግ ቀርቶ ከሃገርም ሰፋ ያለ የገበያ መስተጋብር ይፈልጋል፡፡ ሰፋ ያለ የገበያ መስተጋብር ለመፍጠር ደግሞ ወደ ክልሉ/ዞኑ/ወረዳው የሚመጣው የሌላ አካባቢ ህዝብ የመግዛት አቅም ይዞ እንደሚመጣ መገንዘብን ይፈልጋል፡፡ ከክልሉ ውጭ ላለ ገበያ ደግሞ ሃገር የሚባል ሰፊ መስተጋብር መኖር አለበት፡፡ ሃገር የሚባለው ሁለንተናዊ ሰፊ ገበያ መኖሩ ሸቀጥ የሌለው እንኳን ጉልበቱን ሼጦ የሚኖርበት የስራ እድል ይፈጥራል፡፡ ዘውግ በሚባል ጠባብ ጥብቆ መወሰን ይህን ሁሉ የዘመናዊ ካፒታሊስት ማህበረሰብ አቋም ማጣት ነው፡፡

የገበያ ምርቶችን በማምረት የሚተዳደረው የደቡብ አብዛኛ ማህበረሰብ በመላ ሃገሪቱ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሶ ካፒታል ያለው ነግዶ፣ የሌለው ጉልበቱን ሼጦ የሚኖር ነው፡፡ ጋሞ፣ የወላይታ፣ የጉራጌ፣ የከምባታ፣ የሃድያ፣ ስልጤ፣ ከፋ ህዝቦች ለዚህ እንደ አብነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ በዚህ ላይ በደቡብ ክልል በተለይ በወላይታ፣ ከንባታ እና ሃድያ ዞኖች ከህዝብ ቁጥር መጨመር ጋር የማይጣጣም የመሬት ጥበት አለ፡፡ በዚህ ምክንያት እነዚህ ህዝቦች የሥራ ዕድል ፍለጋ በሃገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ይንቀሳቀሳሉ፡፡ የጉራጌ ህዝብ ማብራሪያ የማያስፈልገው ነው፡፡ የወላይታ ህዝብም ከኦሮሚያ እስከ ቤኒሻንጉል፣ ከአዋሳ እስከ አዲስ አበባ ስራ ባለበት ሁሉ ለፍቶ ለማደር የሚጓዝ ህዝብ ነው፡፡ የከንባታ እና ሃድያ ህዝብ እንደ ወንጅ/መረሃራ/አፋር ባሉ ፋብሪካ ባለባቸው ቦታዎች ሄዶ ከመስራት አልፎ ወደ ደቡብ አፍሪካ ድረስ ያመራል፡፡ የተማረ የሰው ሃይል በኩልም ደቡብ ክልል በሃገሪቱ ዳርቻ የሚሰሩ በርካታ ምሁራንን አበርክቷል፡፡ እነዚህ ለአብነት ተነሱ እንጅ ሌሎችም የክልሉ ህዝቦች ተንቀሳቅሰው የሚሰሩ ናቸው፡፡ ይህ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሶ የመስራት ልምድ ክልሉ ካለው የገበያ ምርት አምራችነት ጋር ተደምሮ ህዝቡ ከዘውግ ማንነት ይልቅ ዘመኑን የሚመጥነውን መደባዊ ማንነቱን እንዲያስቀድም ሳያደርገው አልቀረም፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤቱ የዘውግ ፖለቲካ በደቡብ ክልል ስር እንዳይሰድ አድርጎ ኖሯል፡፡

አዲሱ ዘፈን

የሃገራችን ህገ-መንግስት ለመገነጣጠል ህጋዊ ድጋፍ የሚሰጥ የዓለማችን ብቸኛው ህገ-መንግስት ነው፡፡ ሆኖም በደቡብ ክልል የሚኖሩ በርካታ ዘውጎች መነጣጠሉ ላይ ትኩረት አያደርጉም ነበር፡፡እንዴት እንደተመሰረተ በማይታወቅ ክልል ውስጥ ኢትዮጵያዊነታቸውን እያሰቡ ለሃያ ሰባት አመት ኖረዋል፡፡ አሁን ከሰሞኑ ግን በክልሉ ባልተለመደ ሁኔታ በየዘውጉ ተከፋፍሎ ክልል ለመሆን የመፈለግ ተከታታይ ጥያቄዎች እየተደመጡ ነው፡፡የሲዳማ፣ የጉራጌ፣ የወላይታ፣ የከፋ፣ የከንባታ፣ የሃዲያ ዞኖች በተጨባጭ ክልል የመሆን ጥያቄ ያቀረቡ ዞኖች ናቸው፡፡ የነዚህ ዞኖች ጥያቄ ለደቡብ ክልል በተለይ ተብሎ የተዘጋጀ የሚመስል ህገ-መንግስታዊ ድንጋጌን የተመረኮዘ ነው፡፡

ደቡብ ክልል ከሌሎች ክልሎች በተለየ የብሄረሰቦች ምክር ቤት የሚባል አወቃቀር አለው፡፡ ይህ ምክር ቤት ክልሉ ውስጥ የብዙ ዘውግ አባላት በአንድ ክልል ስለሚኖሩ እነዚህ ክልል የተነፈጋቸው ዘውጎች ጉዳያቸውን የሚመክሩበት የየዘውጉ ምክርቤት ይኑራቸው የሚል እንደ ማፅናኛ ያለ ነገር ነው፡፡ ይህ የብሄረሰቦች ምክርቤት የሚባለው ነገር ሌላ ዋና ነገር አዝሏል፡፡ ደቡብ የሚባለው ክልል ብዙ ብሄረሰቦችን አጭቆ የያዘ፣ እንዴት እንደተፈጠረ ለመታሪው ኢህአዴግ ብቻ በሚገባ መስፈርት የተፈጠረ ክልል ነው፡፡ ይህን የሚረዳው የብልጣብልጡ አቶ መለስ ዘመን ኢህአዴግ እነዚህ ብሄረሰቦች የተከለሉበት አከላለል ትርጉም ግልፅ አይደለምና አንድ ቀን በየዘውጋችን ክልል ይኑረን የሚል ጥያቄ ማንሳታቸው እንደማይቀር አስቧል፡፡ ነገር ግን ይህ እርሱ በስልጣን ላይ እያለ እንዳይነሳ “ክልል ባይኖራችሁም የየዘውጋችሁን ጉዳይ የምትመክሩበት የብሄረሰቦች ምክርቤት ለእናንተ ብቻ አዘጋጅተን ሰጥተናል” በማለት የክልል ጥያቄን ሲከላከል ኖሯል፡፡ ከዚህ አልፎ ለሚሄድ በጠመንጃው መልስ ይሰጥ ነበር፡፡ “የሎቄው ግድያ” በሚባል የሚታወቀው በ1995 የተደረገው ወደ አርባ የሚጠጉ የሲዳማ ተወላጆች ያለቁበት እርምጃ ተጠቃሽ ነው፡፡

በአንፃሩ ለህወሃት/ኢህአዴግ ዘመን የክልል ጥያቄን መከላከያ ተደርጎ የተቀመጠው የብሄረሰቦች ምክርቤት የሚባል አካል ህወሃት ከስልጣን የሚወገድ ከሆነ ደግሞ “ህወሃት የሚዘውረው ኢህአዴግ ከሌለ ሃገር ትፈራርሳለች” ለሚለው ፕሮፖጋንዳው ማመሳከሪያ የሚሆን ፈንጅ ተደርጎ ቀብሯል፡፡ የህገመንግስቱ አንቀፅ 47 ንዑስ አንቀፅ 3 ስር ከሀ-ሠ በተዘረዘሩ ቅድመ ሁኔታዎች ‘ማንኛውም ብሄረሰብ በፈለገው ሰዓት፣ በብሄረሰቦች ምክርቤት በሚቀርብ ጥያቄ እና በጠያቂው ብሄረሰብ አባላት በሚደረግ ሪፈረንደም ዙሪያ በሚዞር ውሳኔ (የማዕከላዊው መንግስትም ሆነ ሌላ አካል እውቅና ሳያስፈልገ) ክልል መሆን ይችላል’ ይላል፡፡

ከኢትዮጵያ በቀር እንደዚህ ያለ አዲስ ክልል ወይም አስተዳደር የሚፈቅድ አንቀፅ ያላቸው ሃገራት ጉዳዩን ከመነሻው እስከ መድረሻው በአካባቢያዊ ምክርቤቶች ወሳኔ እንዲያልቁ የሚተው አይደሉም፡፡ ለምሳሌ የጀርመን ህገ-መንግስት ተመሳሳይ የአዲስ አስተዳደር መመስረትን በሚፈቅድበት አንቀፁ (አንቀፅ 29 ንዑስ ቁጥር 1 እና 2) ጉዳዩ ከመነሻው በማዕከላዊ መንግስቱ የሚታዩ ቅድመ-ሁኔታዎች ታይተው የሚያስችሉ ሆነው ሲገኙ ነው ጉዳዩ እንዲቀጥል ለአካባቢያዊ ምክርቤቶች የሚላከው፡፡በማዕከላዊው መንግስት ጥናት ከሚደረግባቸው ጉዳዮች መካከል አዲስ አስተዳደር የሚጠይቀው አካባቢ በራሱ ለመቆም የሚያስፈልጉትን ኢኮኖሚያዊ፣ የሰው ሃይል፣ የመሰረተ-ልማት፣ መልከዓምድራዊ ቅድመ-ሁኔታዎችን ያሟላ ስለመሆኑ ነው፡፡

በእኛ ሃገር ህገ-መንግስት ሁኔታ ግን የማዕከላዊው (የፌደራሉ) መንግስት ክልሎች በራሳቸው የብሄረሰቦች ምክርቤት እና የክልል ምክር ቤት ዙሪያ በሚዞር ውሳኔ ብቻ ስንት ቦታ እንደተሸነሸኑ እየቆጠረ በጀት ከመመደብ ያለፈ ስልጣን እንዳይኖረው አድርጎታል፡፡ ይህ ድንጋጌ መቼም አቶ መለስ በሚመሩት ሃገር ውስጥ ተግባራዊ ይሆናል ተብሎ የተደረገ አይደለም፡፡ ይልቅስ በህወሃት/ኢህአዴግ የምትዘወረዋ ሃገር በህወሃት ዋናነት መዘወሯን እምቢ ያለች ቀን የሚፈነዳ ህገ-መንግስታዊ ቦምብ ነው፡፡ መንገድም ህይወትም እኔ ነኝ የሚለው ህወሃት አጋፋሪዎች ደፍሮ ስልጣናቸውን ለሚመኝ ትልቅ ፈተና አስቀምጠው ለመሄድ እንደማያመነቱ ግልፅ ነው፡፡ በተግባር የሆነውም ይሄው ነው፡፡በደቡብ ክልል የመጀመሪያው የክልልነት ጥያቄ የተነሳው ዶ/ር አብይ ተስተካክለው ወንበራቸው ላይ ሳይቀመጡ ነበር፡፡ ይህን ተከትሎ “እኔስ ምን እጠብቃለሁ?” የሚሉ ሌሎች ዞኖች የክልል ልሁን ጥያቄያቸውን ፋታ በሌለው ሁኔታ እያከታከተሉ ነው፡፡

ከህገ-መንግስታዊው የሽንሸና ማበረታቻ አንቀፅ በተጨማሪ የጎሳ ፌደራሊዝሙ የፈጠረው አለመተማመን የክልል ጥያቄዎች እንዲጧጧፉ ሳያደርግ አልቀረም፡፡ እንደሚታወቀው የደቡብ ክልል ለሃያ ሁለት አመት ያህል ዋና ከተማውን ያደረገው በሃዋሳ ከተማ ላይ ነው፡፡ ይህ ሲሆን ከተማዋ በሁሉም የክልሉ ብሄረሰቦች አስተዋፅኦ አድጋ አሁን የደረሰችበት ደረጃ ደርሳለች፡፡ አሁን የሲዳማ ዞን የክልል ጥያቄ ሲያነሳ ሃዋሳ ከተማን የአዲሱ የሲዳማ ክልል ዋና ከተማ የማድረግ ጥያቄ አብሮ እየተነሳ ነው፡፡ ሃዋሳ ከተማ የሲዳማ ክልል ዋና ከተማ ስትሆን የቀረው የደቡብ ክልል አንድ ላይ ሆኖ ሌላ አዲስ ዋና ከተማ ከክልሉ በአንድ ቦታ ላይ እንዲመሰርት ነው እሳቤው፡፡ ዋናው ጥያቄ የሚመጣው እዚህ ላይ ነው፡፡

እንበልና የተቀሩት የደቡብ ክልል ብሄረሰቦች አንድ ላይ ሆነው አርባምንጭ ወይም ሆሳዕና አለያም አንዱ የደቡብ ክልልለ ከተማ ላይ አዲስ ዋና ከተማ ለመመስረት ይስማሙ፡፡ የተመረጠችው አዲስ ዋና ከተማ ሆሳዕና ብትሆንና ከተማዋ የደቡብ ክልል ዋና ከተማ ሆና ማደግ ስትጀምር ያረፈችበት ሃዲያ ዞን ደግሞ “ሆሳዕና ከተማን ይዤ የሃድያ ክልልን እመሰርታለሁ” ቢል በደቡብ ክልል ውስጥ ያሉት የተቀሩት ብሄረሰቦች እጣ ምን ይሆናል? ደሞ ሌላ ዞን ፈልገው፣ ዋና ከተማ ከትመው፣ ማደግ ስትጀምር ከተማዋ ያለችበት ዘውግ “ከተማየን ይዤ ክልል መሆን እፈልጋለሁ” ሲል አስረክበው፣ ደሞ ሌላ የሚያቀኑት ከተማ ፍላጋ ሊሄዱ ነው? ይህ መተማመኛ ማጣት ነው በደቡብ ክልል ያሉ ዞኖችን የራሳቸው አካባቢ ላይ ክልል ስለመመስረት አጥብቀው እንዲጠይቁ ያደረጋቸው፡፡ ይህ የአለመተማመን ፖለቲካ ስሩን የተከለው ደግሞ በሃገሪቱ ህገመንግስት አንቀፅ 47 ንዑስ አንቀፅ 3 ላይ ነው፡፡ የመሸንሸን ፖለቲካውን ችግር ለመፍታት ከተፈለገ መፍትሄው መሰራት ያለበት መበታተንን የሚያበረታቱ የህገ-መንግስቱን አንቀፆችን በማሻሻል ነው፡፡

ጥያቄው ምን ጉዳት አለው?

የክልልነት ጥያቄ እያዥጎደጎዱ ያሉ የደቡብ ክልል ዞኖች ክልል እንዲሆኑ ቢፈቀድ ሚመጣው የመጀመሪያው ጉዳት ከክልሉ አልፎ ወደ ሃገሪቱ የሚሻገር ኢኮኖሚያዊ እክል ነው፡፡ ከመበታተን ይልቅ አንድ መሆኑ ለኢኮኖሚያዊ እድገት ያለው በጎ አስተዋፅኦ የሚያነጋግር አይደለም፡፡ አሁን ክልሉን ስንት ላይ ሲደርስ እንደሚያቆም በማይታወቅ አዳዲስ ክልሎች መከፋፈሉ በአዲሶቹ ክልሎች ውስጥ አፍላ የዘውግ ብሄርተኝነትን ስለሚቀሰቅስ ክልሉ እንደ ወትሮው ሳቢ ከመሆን ይልቅ ገፊ የመሆኑ ነገር ያደላል፡፡ ይህ ኢኮኖሚውንም ምርታማነቱንም ማዳከሙ አይቀሬ ነው፡፡ ሁለተኛው ችግር ፖለቲካዊ ነው፡፡ እነዚህ ዞኖች ተሳክቶላቸው ክልል መመስረት ቢችሉ ደኢህዴን የሚባለው ፓርቲ ፈረሰ ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት አሁን እየተቃረበ ባለው ምርጫ ኢህአዴግ በደቡብ ክልል እንዴት እንደሚወከል ግራ ያጋባል፡፡ ደኢህዴንን ጥለው አዲስ ክልል የመሰረቱ ክልሎችስ በአጭር ጊዜ ውስጥ ፓርቲ መስርተው በሃገራዊ ምርጫ የሚወክላቸውን ፓርቲ የሚያገኙት እንዴት ነው?በዚህ ላይ የደቡብ ክልል ምሁራን እና ልሂቃ ለብሄር ፖለቲካው ባትዋር የመሆናቸው ነገር ፓርቲዎቹን በአጭር ጊዜ መስርቶ በሃገራዊ ምርጫ የመሳተፉን ነገር ዳገት ያደርገዋል፡፡ ሌላው ችግር የኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ጠንካራ መሰረት የነበረው የደቡብ ክልል በዘውግ የመሸንሸኑ ነገር በኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ላይ የሚደቅነው ከባድ አደጋ ነው፡፡

 

መስከረም አበራ ጦማሪና በሐዋሳ መምህራን ኮሌጅ መምህር ናት፡፡ የተለየ ሃሳብና አስተያየት ካላችሁ በሚከተለው የመልዕክት አድራሻ መላክ ይቻላል፡፡Email: meskiduye99@gmail.com

ethiothinkthank

Filed in: Amharic