>

ታጋይ ካህናትና መነኮሳት እንደ አሸን የፈሉባት ቤተክርስቲያን !!! (ዘመድኩን በቀለ)

ታጋይ ካህናትና መነኮሳት እንደ አሸን የፈሉባት ቤተክርስቲያን !!!!
ዘመድኩን በቀለ
አረሱት የእኛን መሬት ያውም የእኛን ዕጣ
እነሱ ምን ያድርጉ ከእኛ ሰው ሲታጣ!!
 አለ አዝማሪው።
ዛሬ የምነግራችሁ ሰው ደግሞ ጉደኛ ነው። ሥልጣነ ክህነት የለውም። ነገር ግን መቅደስ ይገባል። መስቀል ያሳልማል። አይሰብክም። ነገር ግን የስብከተ ወንጌል ኃላፊ ተደርጎ የተሾመ ግለሰብ ነው። አይቀድስም፣ ማኅሌት አይቆምም፣ ከየትኛውም መንፈሳዊ ኮሌጅ አልተመረቀም፣ በሀገረ ስብከቱም መዝገብ ላይ አይታወቅም። ነገር ግን ከሊቃውንቱ በላይ ደመወዝ ይከፈለዋል።
ሰውየውን በዚህ የስብከተ ወንጌል ኃላፊነት ስፍራ የመደበው ደግሞ የትግራዩ ጨፍጫፊ የጌታቸው አሰፋ ረዳት የነበረውና ዛሬ እነደ እሱ ጊዜ በብልቱ ላይ ኮዳ ባይንጠለጠልበትም፣ግብረ ሰዶም ባይፈጸምበትም፣ ነገር ግን አንገቱን ደፍቶ፣ ቅስሙ ተሰብሮ በውርደት ወኅኒ የተወረወረውና የቀድሞው የብሔራዊ መረጃ ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ኃላፊ እና የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል የነበረው አቶ ያሬድ ዘሪሁን ነው።
ሁሉን ቢያወሩት ሆድ ባዶ ይቀራል ተብሎ እንጂ በዚህ በእኛ በጉደኞቹ ዘመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን መቼም ያልተሸከመችው ጉድ የለም። ህውሓት ደፋሩ አንዳዋረዳት ማንም አላዋረዳትም። ህወሓት ወታደሮቹን ገዳም በማስገባት መነኩሴ አበምኔት አስደርጎ ተልእኮውን ሲያስፈጽም መኖሩን በአደባባይ እየፎከረ ቅሽሽ ሳይለው ነግሮናል። በዚህ መንገድ መጥተው ጳጳስ የሆኑ ታጋዮች የትየለሌ ናቸው። አንድ ሁለት ብለን መቁጠር እንችላለን። በጦር ሜዳ ወንድማቸውን ሲገድሉ የነበሩ አሁን ደግሞ ሽጉጣቸውንም መስቀሉንም ታጥቀው የሚዞሩ። በመስቀሉ የሚባርኩ፣ በሽጉጡ የሚያብረከርኩ ታጋይ ካህናትና መነኮሳት እንደ አሸን የፈሉባት ናት ቤተክርስቲያኒቷ።
ህውሓት ተቀናሽ ታጋዮቿን አብዛኛዎቹን ቤተክህነት ነው የመደበቻቸው። እዚህ ብሉ፣ ጋጡ፣ እንደፈለጋችሁም ሁኑ። የዚህን ሞኝ ህዝብ ገንዘብ ተምነሽነሹበት በማለት ነው የደብር አለቃ፣ የመምሪያ ኃላፊ፣ ገንዘብ ያዥ፣ ጸሐፊና ቁጥጥር አድርጋ በየደብሩ የሰገሰገቻቸው። ታጋዮቹ በየደብሩ እየተዘዋወሩ ይዘርፋሉ፣ አይከሰሱም፣ አይታሰሩም። ግለሰቦቹ ሲበዛ ጠጪ፣ ሰካራም፣ ሴሰኛና ውሽልሽል ናቸው። የእነዚህ ማፍያዎች ዋነኛ መለያ ምልክትም አመንዝራነት ነው። የሙዳየ ምጽዋት ገንዘብ እንደ ቅጠል የሚሸመጥጡ። ሙዳየ ምፅዋቱን የግል ገቢያቸውና የማይቋረጥ ምንጫቸውም ያደረጉ፣ እንደ አንበጣ ቤተክርስቲያኒቱ ላይ የሰፈሩ። ነውር ጌጣቸው የሆኑ ግሪሳዎችም ናቸው።
ህውሓት ይሄን ነፃ የዝርፊያ ሜዳ የሆነውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰፊ እርሻ ለራሷ ትግሬ ታጋዮች ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም ቀለብ እየሰፈረች ለምታስተዳድራቸውና እንደ እንጉዳይ በየቦታው ላበቀለቻቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትም ጭምር እንደምትከፍለው መረጃዎች እየወጡ ነው። አደገኛ የምትላቸውንና አያያዛቸው የሚያስፈራ የሆኑ ፓርቲዎች በገጠሟት ጊዜ ሁሉ በደኅንነት መሥሪያ ቤቱ የሰለጠኑ የራሷን ሰዎች አስርጋ በማስገባት ፓርቲዎቹን ስታፈራርስ መኖሯም ይታወሳል። ለእነዚህ የፓርቲ መሪዎች ደግሞ ደሞዛቸውን በእነ ታጋይ ጎይቶም ያይኑ የሚመራው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከቱ የህውሓት የማዘዣ ጣቢያ አንድ ሁለት ብሎ እየቆጠረ የምእመናንን ገንዘብ ለተለጣፊ የኢህአዴግ ተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች እንዲከፍላቸው ስታደርግ ቆይታለች። የዚህ ገንዘብ ዋነኛ ምንጩ ደግሞ የአዲስ አበባ ህዝብ ነው። የአዲስ አበባ ምእመናን ለእግዚአብሔር ብለው የሚሰጡት ገንዘብ ለካህናቱ ሳይደርስ ለህውሓት ታጋዮችና ለተለጣፊ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ይከፈላቸዋል። አከተመ ።
የሌሎቹን ሌላ ቀን እመለስበታለሁ። ለዛሬ የምናየው የአንድ አጥቢያ የስብከተ ወንጌል ኃላፊ አድርገው እነ ጎይቶም ያይኑና እነ ጌታቸው አሰፋ ስለሾሙት ጉደኛና ደፋር የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ መሪ ነው።
ስሙ አቶ ሙሉጌታ አበበ ይባላል። የመኢአድ ምክትል ፕሬዘዳንት ተደርጎ በእነ ጌታቸው አሰፋ የተመደበ ነው። አቶ ሙሉጌታን የመለመለው ጎሃ ፅባህ የሚባለውና በእነ አቦይ ስብሃት ነጋ በቤተክህነቱ የተመደበና እስከአሁንም ድረስ በቤተክህነት የህውሓት የደኅንነት ኃላፊ ሆኖ ከእነ ንቡረዕድ ኤርምያስ ጋር በመሆን የድርጅቱን ጉዳይ የሚያስፈፅም ምድብተኛ ካድሬ አማካኝነት ነው።
አቶ ሙሉጌታ አበበን የመኢአድ ምክትል ፕሬዘዳንት አድርገው ህውሓቶች ከመደቡት በኋላ ደሞዙን 6000 ሺ ብር መድበው ይሰፍሩለታል። አቶ ሙሉጌታም ይሄ ከመቀሌ የሚሰፈርለት ደሞዝ አይበቃኝም ብሎ ያመለክታል። እናም የሙሉጌታን ቅሬታ የሰማችው ህውሓት እንደተለመደው ባለቤት የሌላት እርሻ ትዝ ይላትና ወደእዚያች ምስኪን እርሻ ሙሌን ትልከዋለች። ይህቺ ባለቤት የሌላት እርሻ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መሆኗ ነው። ደግሞም ናት።
ህውሓት ቀለብ ስፈሩለት ብላ የላከችው ሙሌንም እነጎሃ ጽባህ፣ ንቡረዕድ ኤልያስና ፓትሪያርኩም ይኑሩበት አይኑሩበት አላውቅም ብቻ በወቅቱ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ የነበረው ታጋይ ጎይቶም ያይኑ ይሆኑና የመኢአዱን ምክትል ፕሬዘዳንት አቶ ሙሉጌታ አበበን ቄጤማ ጎዝጉዘው ይቀበሉታል። ጠርተውም ያነጋግሩታል።
★ እነ ጎይቶም ~ አቶ ሙሉጌታ ለምን የአንድ ደብር አለቃ አድርገን አንሾምህም እና ከዚያ ደሞዝህንም፣ ጥቅማጥቅምህንም አታገኝም።
★ አቶ ሙሉጌታ አበበ ፦ ኧረ በፍፁም እንደዚያማ አላደርግም። ክህነት ሳይኖረኝ። መቅደስ ልገባ ? በፍፁም አላደርገውም። ባይሆን ብዙም የማልገኝበት የሥራ መደብ ፍጠሩልኝ።
★ እነ ጎይቶም፦ መልካም መቅደስ የማያስገባህ የስብከተ ወንጌሉ አካባቢ ነው። እናም የስብከተ ወንጌል ኃላፊ አድርገን እንሾምሃለን። ብዙም መገኘት አይጠበቅብህም። እንዲያው አለፍ አለፍ ብለህ ለመታየት ብቅ ብትል መልካም ነው። በማለት በ4 ሺህ ብር ደሞዝ የስብከተ ወንጌል ኃላፊ አድርገው ይሾሙታል። ያዝ እንግዲህ።
የመኢአድ ምክትል ፕሬዘዳንት ተደርጎ በእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ የተሾመው አቶ ሙሉጌታ አበበም ከየትኛውም መንፈሳዊ ኮሌጅ ሳይመረቅ፣ ሳይለፋ፣ ሳይወጣና ሳይወርድ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት #የጎፋ_ቅዱስ_መርቆሬዎስ ቤተክርስቲያን የስብከተ ወንጌል ኃላፊ ሆኖ ተሹሞ አረፈው።
ይኽ ሰው ቀድስ ሲሉት ረስቻለሁ ይላል። ስበክ ሲሉት መንግሥት ሥራ አዞኝ ቤተመንግሥት ነው ያለሁት ይላል። ካህናቱም በቴሌቭዥን መግለጫ ሲሰጥ ስለሚያዩት ይፈሩታል።
የአቶ ሙልጌታ አበበ ባለቤት የመሰንቆ ቤት አዝማሪ ናት። ይሄ ጉደኛ ሰው ሰሞኑን ደግሞ ሌላ ተአምር ማሳየት ጀምሯል። መስቀል ያሳልማል። ቤተመቅደስ ይገባል። ድፍረቱ ከመጠን በላይ ሆኗል።
አንዳንዴ የእስልምና እምነት ተከታዮች ያስቀኑኛል። በሃይማኖታቸው ላይ የሚቀልድን መንገደኛ በብዙ አይታገሱትም። የእኛ አማኝ ግን ምስኪን ነው። ካድሬና ታጋዩ ሁሉ አስጎንብሶ ይቀልድበታል። ይኸው ነው።
ይህቺ ናት የዛሬዋ ኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ገፅታዋ። ታጋይና የብዙ ልጆች አባቶች የሆኑ ባለ ሚስትና ወላድ ጳጳሳት የሚንጎማለሉባት፣ ሌባው በክብር ተንፈላሶ የሚኖርባት፣ ያውም እንደ አህዛብ ከሁለት ሴት ሁለት ልጅ የወለዱ ደፋር መነኮሳት ተከብረው የሚኖሩባት ናት የዛሬዋ ቤተክርስቲያን።
በአንጻሩ ደግሞ መከራቸውን በልተው የዕድሜ ዘመናቸውን እኩሌታ በአብነት ትምህርት ቤት ያሳለፉ የቤተክርስቲያንኒቱ ልጆች ከመአዱ ተገፍተው ሎቶሪ አዟሪ፣ ዘበኛ ሆነው በሰቀቀን ይኖራሉ። እህህህ ወይ ነዶ !
Filed in: Amharic