>

በሰብአዊነት ላይ የሚፈፀም ወንጀል፣ በኢትዮጵያ ህግ  ይቅርታና ምህረት አያሰጥም!!! (የህግ ባለሙያ አቶ ተማም አባቡልጉ)

በሰብአዊነት ላይ የሚፈፀም ወንጀል፣ በኢትዮጵያ ህግ  ይቅርታና ምህረት አያሰጥም!!!

የህግ ባለሙያና ጠበቃ አቶ ተማም አባቡልጉ
*  ህገ መንግስቱ ባልተሻሻለበት ሁኔታየሚደረጉ የአዋጅ ማሻሻያዎች መድረሻቸው አይታወቅም!
* የምርጫ አዋጁ፤ የፓርቲ ሃብቶች መኖራቸው ከተረጋገጠ፣ ወደ ህዝብ ይመለሳሉ ይላል!
* ኢህአዲግም በሰብአዊ መብት ጥሰት ና በሙስና መጠየቅ አለበት!

ከሰሞኑ በሰብአዊ መብት ጥሰትና በሙስና በተጠረጠሩ ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣናት ላይ እየተወሰደ ያለውን እርምጃና እየተሰነዘሩ ያሉ ቅሬታዎችን እንዲሁም በአፋኝ አዋጆች ላይ እየተደረጉያሉ የማሻሻያ እርምጃዎችን በተመለከተ የህግ ባለሙያና ጠበቃ አቶ ተማም አባቡልጉ፤ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ከህግ አንጻር ምላሽና አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡ እነሆ፡-

መንግሥት በሰብአዊ መብት ጥሰትና በሙስና የጠረጠራቸውን የቀድሞ ባለስልጣናት ለፍርድ የማቅረቡን ሂደት በተመለከተ ምን አስተያየት አለዎት?

ጉዳዩ መጀመሩ ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን ሙስናውም ሆነ የሰብአዊ መብት ጥሰቱ መነሻው ሥርአቱ ነው። ስለዚህ መጠየቅ ያለበት ሥርዓቱ ነው፡፡ የመንግስት ባለሥልጣናት ስርአቱን ተገን አድርገው የፈፀሙት ድርጊት ነው፡፡ በእርግጥ እንደ ግለሰብም መጠየቅ አለባቸው። በተለይ በሰብአዊነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች በግልም በቡድንም ያስጠይቃሉ፡፡ የፌደራል ፖሊስ ማቋቋሚያ አዋጅ ላይ፤ አንድ አባል በስሩ ለሚደረገው ነገር በግልም በጋራም ተጠያቂ ነው ይላል። ስለዚህ የህግ ጥያቄው መቅረብ ያለበት በኢህአዴግ ላይ ጭምር ነው። ድርጅቱ ነው መንግስት ሆኖ፣ መንግስታዊ ስልጣኑን ተጠቅሞ፣ እነዚህን ወንጀሎች የሰራው፡፡ ሙስናውም በተመሳሳይ፡፡ ኢህአዴግ ራሱ ሙስና ነው፡፡ በዘር የተደራጁ ሰዎች ተጠራርተው፣ አንድ ቡድን ፈጥረው ነው ስልጣን የያዙት፡፡ ስለዚህ ይሄ ድርጅት ራሱ ሙስና ነው፡፡ መንግስታዊ ሙስና ነው የተፈፀመው፤ ስለዚህ ግለሰቦቹ እንደ ግለሰብ፣ ሥርአቱ እንደ ቡድን መጠየቅ አለባቸው፡፡ የህግ ማስከበሩ አሰራርም በዚህ መልኩ ነው መሄድ የነበረበት፡፡ በግለሰብ ደረጃ፣ በቡድን ደረጃ በሥርአት ደረጃ ተከፍሎ ነው መሄድ ያለበት፡፡
የኢትዮጵያ የፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ፤ ፓርቲ አይነግድም ይላል፡፡ አንድ ፓርቲ በንግድ ላይ ተሰማርቶ ከተገኘ፣ ፍቃዱን ለምርጫ ቦርድ ያስረክባል ይላል ህጉ። ነገር ግን የኢህአዴግ ድርጀቶች፣ በተለይ ህወሓት፣ ትልቅ ንግድ አለው። ህወሓት በኤፈርት በኩል ይነግዳል፡፡ ይሄ ደግሞ ከህግ ጥሰት ባለፈ መንግስታዊ ሙስና ነው፡፡ የያዘውን የመንግስት ስልጣን መከታ በማድረግ ነው ህግ እየጣሰ፣ ባልተሰጠው ስልጣን ነጋዴ የሆነው፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰቱም ሥርአታዊ ነው። ስለዚህ ከግለሰብ ባለፈ ሥርአቱ ላይም ተጠያቂነቱ መቅረብ አለበት፡፡
በዚህ የሰብአዊ መብት ጥሰትና በሙስና ወንጀል ማን ነው በዋናነት ተጠያቂ ሊሆን የሚገባው ይላሉ? በተለይ ከግለሰብ አመራሮች አንፃር?
ዋነኛ ተጠያቂው መሬት ላይ አቅም ያለው አካል፣ ህወሓት/ኢህአዴግ ነው፡፡ ያንን ሲመሩት የነበረው ደግሞ አቶ መለስ ናቸው፤ ስለዚህ እሳቸው ናቸው ለዚህ ሁሉ ዋነኛ ተጠያቂ መሆን ያለባቸው። ከእሳቸው ጋር ሆነው እንዲህ ያለውን ሙሰኛ ሥርአት ያበጁ ግለሰቦችም መጠየቅ አለባቸው። በዘር ተጠራርቶ የህዝብን ትልቁን የሉአላዊነት ጥቅም (ስልጣን) መያዝ፣ የመጨረሻው ትልቁ ሙስና ነው፡፡ አንተ የኔ ዘር ነህ ተባብሎ፣ የህዝብን ጥቅም ተደራጅቶ ከመያዝ በላይ ሙስና የለም። ያ ስርአት እንዲፈጠር ያደረጉ ሰዎች ናቸው፣ ዋነኛ ተጠያቂ የሚሆኑት፡፡ አንዳንዶች አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ተጠያቂ መሆን አለባቸው ይላሉ። በእርግጥ በፖለቲካ ተዋረድ ሲታይ ይመስላል ግን በተጨባጭ መሬት ላይ ባለው እውነታ አቶ ኃ/ማርያም የሚመሩትን ድርጅት ጨምሮ ሶስቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች፣ የህወሓት ጉዳይ አስፈፃሚነት ሚና ነው የነበራቸው፡፡ ስለዚህ ዋነኛ ተጠያቂው ህወሓት ነው፡፡ ሥርአቱን የዘረጋው ህወሓት ነው፤ ቀሪዎቹ ተባባሪዎች ናቸው፡፡ በተባባሪነት ነው ሊጠየቁ የሚችሉት፡፡
እስሩና ክሱ “ፖለቲካዊ ሆኗል፤ የውጭ ኃይሎች ጣልቃ ገብነት አለ” የሚል ቅሬታ በአንዳንድ ወገኖች እየተሰነዘረ ነው፡፡ በዚህ ቅሬታ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
ምናልባት በጉዳዩ ላይ በኢህአዴግ ውስጥ ድርድር ሳይካሄድ አልቀረም፡፡ ያንን ድርድር አክብሩ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ዞሮ ዞሮ ህግ በድርድር አይከበርም። አሁን በተጨባጭ ወንጀል ሰርተዋል ተብለው የተጠረጠሩትን ነው ለፍርድ የማቅረብ ስራ እየተሰራ ያለው፡፡ ይሄ ደግሞ ትዕዛዝ የሰጡ የህወሓት/ኢህአዴግ መሪዎችንም ማካተት አለበት፡፡  እነ ዶ/ር ደብረፂዮንን ጨምሮ ማለት ነው፡፡
የሰሞኑ  ቅሬታ የሚያሳየው ድርድር እንደነበር ነው፤ ነገር ግን ያ ድርድር በህግ ፊት ተቀባይነት የለውም፡፡ ፖለቲካዊ መስሏል ማለት ምን ማለት ነው? ህወሓት አይደለም እንዴ ሃገሩን ያቆመው? ራሱ ያበጀው ሥርአት አይደለም እንዴ፣ ያንን ሥርአት አበጅቶ፣ የራሱን ፍላጎት ሲያስፈፅም የኖረው? ስለዚህ ወንጀልም ከተሰራ በሱ ስር ነው የተሰራው ማለት ነው፡፡ ይሄ ጉዳይ ዞሮ ዞሮ የሚያርፈው ህወሓት ላይ ነው፡፡ ከኤርትራ ጋር ተነጋግሮ አስገንጥሎ፣ ኢትዮጵያን የተቆጣጠረው ህወሓት ነው፡፡ ስለዚህ ከሚታሰሩ ሰዎች 90 በመቶው የህወሓት አባላት ቢሆኑ ሊያስደንቅ አይገባም። ምክንያቱም ትልቁን ስልጣን ይዘው፣ ድርጊቱን ሲፈፅሙ የነበሩት እነሱ ናቸው፡፡ ይሄ ማለት የትግራይ ህዝብን ይመለከታል ማለት አይደለም፡፡ ህወሓትን ግን የግድ መመልከት አለበት፡፡
የሚወሰደው እርምጃ  እስከ  ምን ድረስ መሄድ አለበት ይላሉ?
ዛሬ በስልጣን ላይ ያሉትም እኮ የህወሓት ጉዳይ አስፈጻሚ የነበሩ ናቸው፡፡ በዚህም አለ በዚያ የህወሓት ተባባሪ ነበሩ፡፡ ነገሩን ለሆነ ሰሞነኛ የፖለቲካ ፍጆታ ብቻ እንዳያውሉት ስጋት አለኝ፡፡ እነ ዶ/ር ዐቢይ ምንም እያደረጉ አይደለም የሚለውን ለማስተንፈስ የተወሰደ እርምጃ እንዳይሆን ስጋት አለኝ፡፡ ይሄ እርምጃ ችግሩን በሚገባ እንዲያጠራ ከተፈለገ፣ ገለልተኛ ኮሚሽን መቋቋም አለበት፡፡ ሌሎች ጉዳዮችንም  የማጣራትና የመመርመር  ስራ የሚሰራ፣ ከሁሉም የተውጣጣ ኮሚሽን ሊቋቋም የሚገባ ይመስለኛል። በዚህ ኮሚሽን አማካይነት ነው አጥፊዎች ለፍርድ መቅረብ ያለባቸው። የእርምጃውን ስፋትና ወሰን የሚለካውም፣ ይህ ኮሚሽን በሚያደርገው ማጣራት ልክ ቢሆን የተሻለ ይሆናል፡፡
አንዳንድ ወገኖች ጉዳዩ በይቅርታ ከታሰረ በኋላ እርምጃ መውሰዱ አግባብ አይደለም ይላሉ። እርስዎ በዚህ ላይ ምን ይላሉ?
ለሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ለሙስናና ለሌብነት ይቅርታ አይደረግም፡፡ እነ ህወሓትና ሌሎችም እኮ ኤፈርትን የመሳሰሉ ድርጅቶች ፈጥረው፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ሃብትን በእጅ አዙር ወደ እነሱ እንዲዞር ሲያደርጉ ነው የኖሩት፡፡ ያ ማለት እነዚያ ሃብቶች፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ሃብቶች ናቸውና፣ ለባለቤቱ መመለስ አለባቸው። ይሄ ሳይሆን  ህግ ተከበረ ማለት አይቻልም፡፡ እነዚህ ሃብቶች ወደ ኢትዮጵያ ህዝብ መመለስ አለባቸው፡፡ ለዚህ ደግሞ በቂ የህግ ድጋፍ አለ፡፡ የምርጫ አዋጁ፤ የፓርቲ ሃብቶች መኖራቸው ከተረጋገጠ፣ ወደ ህዝብ ይመለሳሉ ይላል፡፡ ይሄን ለምን ማድረግ አይቻልም። በሰብአዊነት ላይ የሚፈፀም ወንጀል፣ በኢትዮጵያ ህገ መንግስት መሠረት ይቅርታና ምህረት አያሰጥም። የሀገር ሃብት ዘረፋም እንደዚሁ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር፣ በይቅርታ ታልፏል የሚለው መከራከሪያ የሚያስኬድ  አይመስለኝም፡፡
የፀረ ሽብር ህጉ “ተመጣጣኝ ቅጣት”ን ሲፈቅድ፣ ዝርዝር ማብራሪያ የሌለው ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የደህንነት ሃይሉ ሰብአዊ ጥሰት ለመፈፀሙ በር ከፋች ነው፤ ከዚህ አንፃር የደህንነት አካሉን በሰብአዊ መብት ጥሰት መጠየቅ አይቻልም የሚሉ ክርክሮችም አሉ፡፡ ይሄን እንዴት ያዩታል?
በመሠረቱ ህጉ የመደብደብ መብት ሊሰጥ አይችልም፡፡ እንደተባለው ተመጣጣኝ ቅጣት ይላል። ያ ቅጣት ምንድን ነው? አይታወቅም። በእርግጥ ኢህአዴግ ሽብርተኛ ነበርኩ ብሎ አምኗል፡፡ ለዚህ ነው ኢህአዴግ ነው በአሸባሪነት መጠየቅ ያለበት፣ የእሱ አባላት ናቸው ለፍርድ መቅረብ ያለባቸው የምንለው። ሽብርተኛ ነበርኩ ብሎ በማመን ደግሞ ከሰብአዊ መብት ጥሰት ተጠያቂነት ማምለጥ አይቻልም፡፡ አሁን እየተደረገ ያለው፤ ዋነኛ  የሽብርተኛ ተላላኪዎቹን ተጠያቂ የማድረግ ነገር ነው፡፡ ስለዚህ ይሄን ጉዳይ በተመለከተ ገለልተኛ ኮሚሽን ተቋቁሞ፣ ተጠያቂዎች አንድም ሳይቀሩ ለፍትህ መቅረብ አለባቸው፡፡ ይሄ ጉዳይ መሄድ ያለበት እዚህ ድረስ ነው፡፡
ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ፤ በመንግስት ለተፈፀሙ ስህተቶች ይቅርታ መጠየቃቸው ከግምት ውስጥ  አይገባም?
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይቅርታ ቢጠይቁም፣ ህወሓት እኮ ዛሬም ወደ ቦታችን እስክንመለስ እንታገላለን፤ እንዋጋለን እያለ ነው፤ እንኳን ይቅርታ ሊጠይቅ ይቅርና። ዶ/ር ዐቢይ ናቸው በራሣቸው ቀናነት ይቅርታ የጠየቁት እንጂ እነሱ እኮ ዛሬም ስህተት ሰርተናል ብለው አላመኑም፡፡ እነሱ ይቅርታ አልጠየቁም፡፡ ጉዳዩም በባህሪና በይቅርታ የሚታለፍ አይደለም፡፡
በሌላ በኩል ለአፈና መሠረት ናቸው የተባሉ አዋጆችና ህጎች  አሁን እየተሻሻሉ ነው፤ ይሄን ሂደትስ እንዴት ይመለከቱታል?
ህገ መንግስቱ ባለበት ነው ያለው፤ አልተሻሻለም። አዋጆቹ የተሠሩት ይሄን ህገ መንግስት ተመስርተው ነው፡፡ ወይም ደግሞ ፓርቲዎች በጉዳዩ ላይ ተነጋግረው አቅጣጫ አላስቀመጡም፡፡
ታዲያ ምንን መሠረት ተደርጐ ነው አዋጆቹ የሚሻሻሉት? 
አጠቃላይ ስርአቱን ፍትሃዊ ማድረግ እንጂ አዋጅ በማሻሻል ማህበራዊ ፍትህ አይሰፍንም፡፡ ዞሮ ዞሮ መድረሻው አይታወቅም።
ምክንያቱም በመጀመሪያም ስህተቶች ያሉት ህገ መንግስቱ ላይ ነው፡፡ ህገ መንግስቱ ባልተሻሻለበት ሁኔታ ወይም ሌላ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ተወያይተው አቅጣጫ ባላስቀመጡበት ሁኔታ፣ ህግ የሚሻሻልበትና የሚወጣበት ሂደት ጤነኛ መስሎ አይሰማኝም፡፡ ውጤቱም የሚታወቅ አይሆንም። ምክንያቱም ታች ያሉት ህጐች፣ እላይ ያለው ህግ ውጤቶች ናቸው፡፡ ህገ መንግስቱ ባልተሻሻለበት ወይም ባልተፈተሸበት ሁኔታ የሚደረጉ ማሻሻያዎች መድረሻቸው አይታወቅም። ግቡም ከጊዜያዊ የፖለቲካ ፍጆታ የሚሻገር አይመስለኝም፡፡
ህገ መንግስቱ በቅድሚያ መሻሻል አለበት ሲሉ ምንን መሠረት አድርገው ነው?
ህገ መንግሥቱ መሻሻል አለበት ሳይሆን መሻር አለበት የሚል አቋም ነው ያለኝ፡፡ ህገ መንግስት፤ የፖለቲካ ስልጣን የያዙ ወገኖች ወይም በቁጭት ስልጣን የያዙ ሃይሎች የሚያወጡት ህግ ነው። በሌላ ፍልስፍናው ግን ህገ መንግስት ህዝብ ተደራድሮ ሊያመጣው የሚገባ ሰነድ ነው፡፡ አሁን ያለው ህገ መንግስት፤ በደማችን ያመጣነው ነው የሚባልለት ነው፡፡ እርግጥ ነው ህገ መንግሥት በደምና በትግል ነው የሚመጣው፡፡ የኛም ህገ መንግስት፤ ህወሓት ደርግን በማሸነፉ በደም ያገኘነው ነው በሚል የፃፉት ነው፡፡ ስለዚህ በህወሓትና ጥቂቶች ደም የመጣው ህገ መንግስት መሻር አለበት፡፡ ህወሓት/ኢሕአዴግ በሌሎች ላይ ያገኘውን ድል ያስጠበቀበት፤ እኛን ያስገበረበት ህገ መንግስት ስለሆነ መሻር ነው ያለበት፡፡ ህገ መንግስት ሃሳብ ነው፡፡ የኛ ህገ መንግስት ሃሳብ ደግሞ የሕወሓት/ኢህአዴግ ሃሳብ ነው። ህወሓት ደርግን መነሻ አድርጐ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የተጐናፀፈበት ድል ሃሳብ ነው፤ ይህ ህገ መንግስት። በዚህ የተነሳ የኢትዮጵያ ህገ መንግስት ሊሆን አይችልም፡፡ አሁን የህዝብ ትግል ድል አምጥቷል ካልን፣ የህዝብን ድል የሚያስጠብቅ ህገ መንግስት ከህዝቡ መምጣት አለበት፡፡
Filed in: Amharic