>

ብሄራዊ መግባባት ለማምጣት የታሪክ ሂሳብ ማወራረድ ውስጥ መግባት አያስፈልግም!!! (ፕሮፌሰር  መረራ ጉዲና) 

ብሄራዊ መግባባት ለማምጣት የታሪክ ሂሳብ ማወራረድ ውስጥ መግባት አያስፈልግም!!!
ፕሮፌሰር  መረራ ጉዲና 
”በኢትዮጵያ ብሄራዊ መግባባትና ብሔራዊ እርቅ ለማምጣት ምን መደረግ አለበት?” በሚል ዙሪያ ከተለያዩ የሙያ ዘርፎች የተውጣጡ የኀብረተሰብ ክፍሎች ትናንት ምሽት በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ውይይት አካሂደዋል።
‘ኢምፓውር አፍሪካ’ በተሰኘ ተቋም አዘጋጅነት የተካሄደው ውይይት አዲሲቷን ኢትዮጵያ እንዴት እንፍጠር? መልካም አጋጣሚዎችና ፈተናዎች ምንድን ናቸው? በሚሉ ጉዳዮች ላይ የሀሳብ ልውውጥ ተደርጓል።
ዶክተር መረራ ጉዲና ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ ባቀረቡበት ወቅት እንዳሉት፤ በአገሪቱ ብሄራዊ መግባባትን ለማምጣት በታሪክ የተፈጸሙ ድርጊቶችን ለማወራረድ መሞከር አያስፈልግም።
”ለዘመናት በኢትዮጵያ ሁሉም የሚስማማበት፣ የጋራና ሞዴል ሊሆን የሚችል መሪ አለመኖር ትልቅ ፈተና ሆኖ ቆይቷል” ብለዋል።
አጼ ምኒሊክ በተወሰኑ አካባቢዎች ዘላለማዊ ጀግና ተደረገው ይወሰዳሉ፤ በሌላ አካባቢ ደግሞ ቀኝ ገዥ ተደርገው መታየታቸውን በማሳያነት የጠቀሱት ምሁሩ ብሄራዊ እርቅ ለማምጣት ከዚህ ዓይነት አስተሳሰብ መላቀቅ እንደሚገባ አስረድተዋል።
ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር በኢትዮጵያ የሀሳብ የበላይነት አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ ሁሉም የኀብረተሰብ ክፍል የበኩሉን አስተዋጽኦ ማድረግ እንዳለበት ዶክተር መረራ ገልጸዋል።
”በአገሪቱ ታሪክ የነበሩ የሚጋጩ ህልሞችን ይዞ መኳተን የትም አያደርስም” ያሉት ዶክተር መረራ ህልሞቹ በአግባቡ ካልተያዙ ወደለየለት አለመረጋጋት የሚወሰዱ በመሆናቸው ሁሉም የሚጠበቅበትን የቤት ሥራ መስራት እንደሚገባው አመልክተዋል።
ፖለቲከኞች፣ የሐይማኖት መሪዎች፣ አባ ገዳዎችና የአገር ሽማግሌዎች አዲሲቷን ኢትዮጵያን እንዴት እንፍጠር? የሚለውን በጥልቀት ሊሰሩበት ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል።
”መግባባት በሚቻልበት ቋንቋ ምን ያስፈልጋል? የነገዋ ኢትዮጵያ ምን መምሰል አለባት?” በሚሉና መሰል ጉዳዮች ላይ በሰከነ አእምሮ መወያየት እንደሚያስፈልግ ነው ዶክተር መረራ በመነሻ የውይይት ሀሳባቸው አጽንኦት የሰጡት።
”ህዝብ የእኔ መንግሥት ነው” የሚል አስተሳሰብ አለማምጣቱ በአገሪቱ የሚታይ ትልቁ ፈተና መሆኑን የተናገሩት ዶክተር መረራ ”በቀጣይ ህዝቡ የኔ መንግሥት ነው” እንዲል የሚያስችሉ ሥራዎችን መሥራት እንደሚገባም ጠቁመዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ከነበረው የኢትዮጵያ ታሪክ ለምን መማር አልቻልንም? እስከ መቼ ነው በትንንሽ ቁርሾዎች መቃቃሩ የሚቀጥለው? እውነተኛ ለውጥ እንዲመጣ በመሸነጋገል ላይ የተመሠረቱ ሥራዎች መቆም እንዳለባቸው ተናግረዋል።
አቶ ብርሃኑ አሰፋ በሰጡት አስተያየት ”የኔ ብቻ ልክ ነው ከኔ ውጭ ያለው አስተሳሰብ የተሳሳተ ነው” የሚለው አመለካከት ከየት መጣ የሚለውን ከመሰረቱ መለየት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።
በተለይ ደግሞ እንደዚህ አይነት ልዩነቶች የሚጎሉት ተማሩ በሚባሉ ሰዎች ላይ ነው ትምህርቱስ ምኑ ላይ ነው? ሲሉም ይጠይቃሉ።
ሌላው የውይይቱ ተሳታፊ አቶ ታምራት ነገራ ደግሞ ”ጠላትነት ተቋማዊ መዋቅር እንዲይዝ ተደርጓል” የሚል ሀሳብ ያነሱ ሲሆን ይህም ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር ትልቅ ሳንካ ሆኗል ብለዋል።
በውይይት ብቻ ብሔራዊ መግባባት ሊመጣ አይችልም ያሉት አቶ ታምራት በትምህርትና በሐይማኖት ተቋማት በኩል ስለ ብሔራዊ መግባባት በኀብረተሰቡ ዘንድ የማስረጽ ሥራ መሥራት እንደሚገባ ገልጸዋል።
ሌላዋ የውይይት ተሳታፊ ወይዘሮ መቅደስ አዳነ በበኩላቸው ብሔራዊ መግባባትን አደጋ ላይ የጣለው ዋናው ምክንያት የነበረው የጥላቻ ትርክት እንደሆነም አስረድተዋል።
ዶክተር መረራ በሰጡት የማጠቃለያ ሀሳብ ብሔራዊ መግባባት በተጨባጭ ለማምጣት የታሪክ ሂሳብ ማወራረድ ውስጥ መግባት እንደማያስፈልግ አመልክተዋል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለው የለውጥ እንቅስቃሴ ለብሔራዊ መግባባት ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑን ያብራሩት ዶክተር መረራ የነገውን ፖለቲካ ለማስተካከል ሁሉም የቤት ሥራውን መሥራት እንዳለበት አስረድተዋል። ምንጭ:- መሳፍንት ተፈራ
Filed in: Amharic