>

ለውጡ ያለመለሳቸው በርካታ የህዝብ ጥያቄዎች አሉ! እንቅፋቱን ግን መጥረግ ጀምረናል!!! (ንጉሱ ጥላሁን)

ለውጡ ያለመለሳቸው በርካታ የህዝብ ጥያቄዎች አሉ! እንቅፋቱን ግን መጥረግ ጀምረናል!!!
ንጉሱ ጥላሁን
“በህዝብ ቀስቃሽነት እና በድርጅት መሪነት የጀመርነው ለውጥ አልጋ በአልጋ ሊሄድ አይችልም፤  ወይ ይሳካል አለዚያም ሊቀለበስ ይችላል” ስንል በርካቶች እንደዋዛ ሲመለከቱት ይስተዋላል::
 ለውጡ በራሱ በመሪ ድርጅቱ ውስጥ ፍልሚያ የተካሄደበት ከውስጥ ህይወት የዘራ ለውጥ  ነው:: ለውጡ ሁለት ሀይሎች የሚፋለሙበት፤ የሞት ሽረት ትግል የሚደረጉበት ትግል መሆኑን መገንዘብ ይገባል። ለውጡ “ህዝብ ነፃ ይውጣ፤ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ፍትሀዊነት ይረጋገጥ፤ የዜጎች ሰብአዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ይከበሩ፤ ዜጎች በገዛ በሀገራቸው በያዙት ሀሳብ ብቻ አይሳደዱ፣ በደልና ግፍ አይድርስባቸው፤ የፖለቲካ ምህዳሩ ይስፋ፤ ዘረፋ እና ሌብነት ይቁም ” የሚለው ሀይል በአንድ ወገን “የህዝብ እና የሀገር ሀብት በመዝረፍ ትልቅ ጡንቻ የፈጠረ እና ይህንኑ ለመቀጠል የሚፈልገው ወይም እንዳይጋለጥ ጫካውን የሚፈልገው፤ ዜጎችን ያሰቃየው፣ ያኮላሸው፣ ሰው በሰው ላይ ይፈፅመዋል ተብሎ የማይገመተውን ተግባር የፈፀመው ሀይል በሌላ ወገን ጉሮሮ ለጉሮሮ የተናነቁበት ነው።
የለውጡ ሀይል ለህዝብ እና ሀገር ነፃነት ከሚጥረው በላይ እጥፍ የሚሰራ፤  የካበት ልምድ  ያለው እና የረቀቀ የሌብነት መረብ የዘረጋ ግዙፍ ሀይል የመገርሰስ ከባድ ፈተና ከፊቱ ተጋርዶበት አላራምድ ሊለው እንደሚችል የተገነዘበ በመሆኑ ይህንን ሀይል ለህዝብ የማጋለጥ እና ህዝቡም የትግሉን ባህርይ እንዲገነዘብ ማድረግ አንዱ ስራው ነበር።
በሌላ በኩል ለውጡ የመጣለት ሳይሆን የመጣበት፤ ሀገር የዘርፈው እና ዜጎችን በምድር ሲዖል ሲያሰቃይ የኖረው ሀይል ለውጡን ለመቀልበስ እና ጨለማው እንዲቀጥል ህዝቡን በመከፋፈልና በማደናገር ለመቀጠል ያለ የሌለ ሀይሉን በመጠቀም እየተፍጨረጨረ ይገኛል። በዘረፈው እና ስለ አገባቡም ሆነ አወጣጡ ጠያቂ በሌለው፤ እንደልብ በሚዛቀው ገንዘብ ሲፈልግ መሳሪያ፤ ሲፈልግ ሰው እየገዛ ህዝብን ከህዝብ እያበጣበጠ ሾልኮ ለማለፍ ብዙ ርቀት ሄዷል። ቦምብ አፈንድቷል፤ ረብሻ አስነስቷል፤  የለውጥ ሀይሉን ለመከፋፈል ሞክሯል።  ብቻ ያዋጣኛል፤  ከመጋለጥ ያድነኛል ያለውን ማንኛውንም ሙከራ አድርጏል። ሊንጋ ሲል ጨለምለም ብሎም ነበር። የህዝቡ የለውጥ ፍላጎት እና “የእርምጃ የለም፤ ንግግር ብቻ አበዛችሁ፤  ሀብት የዘረፉ፣  ግፍ የሰሩ አልተጠየቁም … ወዘተ” የሚሉ ትችቶችም በዝተው ነበር።
እነሆ አሁን ያ የደለበ አቅም፣ በህዝብ ሀብት ለውጡን በፈለገው አቅጣጫ ሊጠመዝዝ የመሸገ ሀይል
ምሽጉ መፍረስ ጀምሯል። ራሱን ለማዳን ሽሽት ይዟል። አሁን ህዝብን ሊያደናግር አይችልም። ሌባ የሌብነት አጋር እንጂ የኔ ብሎ ከለላ የሚሆነው ብሄር፣ ሀይማኖት ወይም ሌላ ማንነት የለውም።  የትኛውንም ህዝብ ወይም አካባቢ ወክሎ አልሰረቀም ወይምአልገረፈም። ያንን ሁሉ በድል ሲፈፅም ከየትኛውም ህዝብ ዝረፍልኝ፣ ግረፍልኝ፣  አሰቃይልኝ የሚል ውክልና አልወሰደም።  የዘረፈው መላውን ኢትዮጵያዊያንን እና የኢትዮጵያን ሀብት ነው። ዜጎችን በማንነታቸው ብቻ ቢያሰቃይም እንኳን ከየትኛውም ህዝብ ይህንን የመሰሰለውን ፀያፍ ስራ እንዲሰራ ውክልና አልወሰደም። ይህ ሀይል ያፈራው  ሀብት እንጂ ቋሚ ወዳጅ ወይም ዘመድ የለውም።
=
ለውጡ ከመቀልበስ አደጋ መውጣት ጀምሯል። ምክንያቱም እንቅፋቱ ሽሽት ጀምሯል :: ግማሹ በምዕራብ፣  ቀሪው በምስራቅ  አይኑ ወደ ውጪ አማትሯል:: ለውጡ ግን ገና አስተማማኝ ደረጃ ላይ አለደረሰም። አሁንም ከጠንካራ ሀይል ፈተና ይጠብቀዋል::
መፍትሄው መስከን፣ ትዕግስት፣ አንድነት እና መተባበር ነው:: ለውጡ ያለመለሳቸው በርካታ የህዝብ ጥያቄዎች አሉ:: እንቅፋቱን መጥረግ ጀምረናል :: በተስተካከለው ሜዳ ይህዝብ ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ይመለሳል :: ግን ብዙ እንቅፋት ከፊታችን ይጠብቀናል ::
Filed in: Amharic