>
5:14 pm - Friday April 20, 3055

ልፋ ያለው አንድ እንጨት ያስራል!!! (ሀይለ ገብርኤል አያሌው)

ልፋ ያለው አንድ እንጨት ያስራል!!!
ሀይለ ገብርኤል አያሌው
ያልታደለ ግራ የተጋባ ትውልድ የነጻነት ትርጉም የሃገርን ዋጋ ተሰዶ እንኳ ይጠፋዋል:: በጀርመን የታየው የድርጅት አርማ ብዛት ምንን ለመግለጽ ነው:: የሌለን ሃገር ፍለጋ ሊገኝ የማይችል የህልም አለምን ከመዞር እንዴት ቆም ብሎ ማሰብ ያቅታል:: እንዴት የሃገር  ትርጉምና ዋጋ ይጠፋዋል:: የሂትለር የዘር ማጽዳት ታሪክ : የአርዐያን ዘር የበላይነት ስብከት ምን ያህል ሰብዐዊ ውድመት እንዳስከተለ ጀርመን ሃገር ላለ ስደተኛ እንዴት ይጠፋዋል::
በጥቁር ዓለም ብቸኛውና አንጸባራቂው የነጻነት ሰንደቅ የሆነው የኢትዮጵያ ባንዲራ ይህን ያህል መጥላት ምን የሚሉት ተቃውሞ እንደሆነ ሊገባን አልቻለም:: እንግዳውን ጠቅላይ ሚንስትር እየደገፉ መቃወም : እያከበሩ መናቅ መሆኑን አለመረዳታቸው ያሳዝናል::  ጎበዝ ሃገር በጀብራሬዎች ቀረርቶና በቁጭበሉ ሕልመኞች ተረት አልተገነባም:: በደምና አጥንት በውዴታ ሳይሆን በግዴታ ነው:: ባለ ልዩ ባንዲራ ወንድሞች የዛሬይቷ ታላቋ ጀርመን እንዴት እንደተመሰረተች ጠይቃችሁም ይሁን አንብባችሁ ብታውቁት ይረዳችሁ ይሆናል::
እንደ ብረት ጠንካራው መሪ የሚል መጠሪያ የነበረው ቢስማርክ በ 25 ግዛቶች ተበታትና የነበረችውን ጀርመንን አንድ አድርጎ ለረጅም አመታት ያስተዳደረ የመጀመሪያው መሪ ነው:: የተበታተነውን የጀርመን ግዛት አንድ ለማድረግ የተጠቀመበት ዘዴ ደግሞ  (blood and Iron) የሚል ሃይልን ብቻ መሰረት ያደረገ መርሆ ነው:: ይህው ዛሬ ሃገራቸው ጀርመን ከራሷ አልፋ ለዓለም ሁሉ የምትበቃ ሃይለኛና ባለጸጋ ሆናለች:: ይህው ለኛም ተርፉ ከነልዩነታችን ከነተምታታ ማንነታችንና ኢኮኖሚያዊ ችግራችን አቅፋ ይዛናለች::
ትላንት በሃገራችንም የተደረገውና የሆነው ከዚህ ብዙም አይርቅም:: ልፉ ብሎን እንደክማለን:: ቢያድለንማ የተገኘውን ለውጥ ጠንካራ መሰረት ላይ እንዲቆም መጣር :: መሪውን  በሞራልና በገንቢ ሂስ ማገዝን ነበር:: በውጭ ስደት ላይ ያለንው በመረጃም በኢኮኖሚም ሆነ በነጻነት ሃገር ውስጥ ካለው የምንሻል በመሆኑ በሃገር ውስጥ ለሚካሄደው እንቅስቃሴ አርዐያና ምሳሌ ሆነን መገኘት ሲገባን ግራ ተጋብተን ግራ ባናጋባው መልካም ነው::
ልቦና ይስጠን!!
Filed in: Amharic