>
5:13 pm - Saturday April 18, 9665

የማለዳ ወግ ... አንዳርጋቸው ጽጌ፣ የስደተኛው "ሲኦል ምድር " የመን እና የእኛ ስጋት ... [ነቢዩ ሲራክ]

እግረ መንገድ…

ANdargachew tsigeሰሞነኛ የአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በየመን መታገትና ወደ ኢትዮጵያ የመተላለፍ ዜና ብዙዎችን እያነጋገረ ያለ ጉዳይ ሆኗል። በአረብ ሃገር የሚገኙን ጨምሮ ኢትዮጵያውያንን ከአድማስ አድማስ በተቃውሞና በድጋፍ እያነቃነቀ ይገኛል። ምሽቱን በፊስ ቡክ በ Facebook ማህበራዊ ገጽ ከተንሸራሸሩት አስተያየቶችና ወቅታዊ መወያያ ርዕሶች መካከል የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ መታገት ሲሰማ የመን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ለኢትዮጵያ መንግስት አሳልፋ እንደምትሰጥ ምንጩን ሳይነግረን መረጃ ያቀበለን የአውራምባ ታይምስ አዘጋጅ የዳዊት ከበደ የምሽት ላይ ባስተላለፈው የማወያያ መጠይቅ አስገርሞ አሳዝኖኛል።
ዳዊት በዚህ መጠይቁ”አቶ አንዳርጋቸው የኢትዮጵያ ፖስፖር ይዞ መቆየት የለበትም ትላላችሁ ? ” በማለት ዳዊት ራሱ በአለማችን ነባራዊ ሁኔታ የነጻነት ታጋዮችን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ እያወቀ እንዳላወቀ ሆኖ በለቀቀው በሚመስለኝ መጠይቁ ሊያወያየን ከጅሏል…

ወዳጀ የአውራንባው ጋዜጠኛ Dawit Kebede ይህን ጉዳይ ሲያነሳ በዘመነ ደርግ “ሽፍታ ፣ ወንበዴ እና ገንጣይ! ” በሚል ስም ይወገዙ የነበሩት የወያኔ መሪዎች በሃገር ቤት ፣ እውቁ የነጻነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ፣ የኩርዱ ነጻነት ታጋይ ኦጀላንን ጨምሮ በርካታ በአለማችን የምናውቃቸው የነጻነት ታጋዮች አንባገነን የሚሉትን መንግስት ለመጣል የሃገራቸው ፖስፖርት ይዘው እንዳልነበር ጠፍቶት አይመስለኝም። ሌላው ይቅርና በኢትዮጵያ ውስጥ የኤትራውን ጨቋኝ የኢሳያስን መንግስት ለመጣል በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሰው ቡድን መሪዎች በኤርትራ ፖስፖርት ይሆን የሚንቀሳቀሱት ? ይህ በዳዊት አፍንጫ ስር ያለ መረጃ ነውና ወዳጀ ዳዊት እንዲፈትሸው በማሳሰብ ዳዊት የአቶ አንዳርጋቸውን እንቅስቃሴ የማይደግፍ ከሆነ እንደ ዜጋ በግልጽ የራሱን ሃሳብ የማቅረብ መብቱ የተጠበቀ እንደሆነ የወንድም ምክሬን መክሬዋለሁ። በእኔ በኩል ግን ከላይ በሰጠው የወረደ ማወያያ ሃሳብ መነሻ ሚዛናዊነት መጉደል አካሄዱ ስላላማረኝም። ይህም በመሆኑ ወዳጀ ጋዜጠኛ ዳዊት ያነሳው ማወያያ ሃሳብ አላስደሰተኝም! … ዳዊት የጀመረው ተራ ብሽሽቅ እንጅ መረጃ ቅበላ አልመሰለኝምና አዝኛለሁ! እግዚአብሔር ዳዊትንም እኛንም ይታረቀን ብየ ብዘለው ይሻለኛል: ( ከመነሻ እግረ መንገዴ ይህን ካልኩ ወደ የመን ሰሞነኛ እርምጃ እና እርምጃው ወዳስከተለው ስጋት በጨረፍታ ላምራ …

የየመን መንግስት በኢትዮጵያ መንግስት “ቀንደኛ” ተፈላጊ የሆኑትን አቶ አንዳርጋቸወ ጽጌ በማገትና በማስተላለፉ ረገድ ያሳየው ፍጥነት ብዙዎችን አስገርሟል። ላለፉት አስርት አመታት በየመን ምድር ታይቶ ተሰምቶ የማይታወቅ ግፍ በኢትዮጵያውያን ላይ ሲፈጸም ተመልካች የሆነው የየመን መንግስት የዛሬ አርምጃ ፍጥነት ብዙዎችን አስገርሟል።

ያልታደሉ ስደተኞች ኢትዮጵያውያን ግፍ ከተበራከተባቸው አረብ ሃገራት መካከል የመንን የሚተካከላት የለም። ግፍ ተፈጽሞባቸው እዚህ ሳውዲ አረቢያ ያገኘኋቸው ግፉአን ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በየመንን ምድር እንደ እንስሳ ተቆጥረው ያዩትን የስደትና እንግልትና እገታ ሲገልጹት “የሲኦል ምድር!” ማለት ይቀናቸዋል። ስደተኛ ወገኖቻችን ዛሬ ድረስ በየመን ከተማ ጉራንጉሮችና በየበርሃው የከፋ በደል እየተፈጸመባቸው ለመሆኑ የአደባበይ ሚስጥር በመሆኑ ዋቢ የሚያሻው አይደለም። የኢህአዴግ መንግስት በኢኮኖሚ ሰደተኞች በሆኑ ዜጎቹ ላይ በየመን ምድር የሚፈጸመውን ግፍ ተቃውሞ አርባና ያለው እርምጃ መውሰድ ባለመቻሉ እስካሁን ያለው የስደተኞች ይዞታ አሳሳቢ እንደሆነ ቀጥሏል ። በግዛት መሬቱ ላይ በዜጎቹ ግፍ ሲፈጸምብን መገደብ የተሳነው የየመን ስንኩል መንግስትም ቢሆን አለም አቀፍ ህግጋትን አክብሮ የወሰደው ቅንጣት እርምጃ ካለማሳየቱ በተዛማጅ የዛሬ አቶ አንዳርጋቸውን የማስረከብ እርምጃ ለኢትዮጵያ ሰላም በማሰብ ሳይሆን የፖለቲካ ጥቅምን ለማጋበስ የወሰደው እርምጃ ነው በሚል ብዙዎችን ቂም አስቋጥሯል።

በየመን በሽዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን በግፍ በየባህሩና በርሃው ወድቀው ሲቀሩ የኢትዮጵያ መንግስት ተወካዮች የዜጎቻቸውን መብት ሲያስከብሩ አይተን ለማናውቅ ዜጎች የመንና ኢትዮጵያ “አሸባሪ! ” ያሏቸውን ግለሰብ በታገቱበት ጥቂት ቀናት ውስጥ ወደ ሃገር ቤት ማስተላለፋቸው ብዙዎቻችን አስደምሟል። ይህ ያልተጠበቀ ክስተትና የተወሰደ የማስተላለፍ እርምጃ ተከትሎ ነዋሪም የተለያየ አስተያየት በመስጠት ላይ ነው። በርካታ ነዋሪዎች ” አቶ አንዳርጋቸውንና የሚመሩትን ድርጅት ስም ማንሳት በወንጀለኝነት ያስቀጣል ” የሚለውን ማስጠንቀቂያ እየጣሱ መንግስት “በአሸባሪነት ” ስለፈረጃቸው የቀድሞ የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ጉዳይ የመጣው ይምጣ በሚል አንድምታ ድፍረት በተቀላቀለበት መንገድ ነዋሪው ዋንኛ መነጋገሪያ አድርጎታል። በኢትዮጵያ መንግስት “ነውጠኛ አሸባሪ ” የተፈረጁት እና በኢህአዴግ ላይ ጦር የሰበቀው የግንቦት 7 ድርጅት አራጊ ፈጣሪ ናቸው የሚባሉት አንዳርጋቸው ጽጌን ” ለዲሞክራሲና ነጻነታቸው የተጉ፣ ብርቱ አርበኛና ታጋይ !” እያለ ከንፈሩን የሚጥላቸው እና የሚያደንቋቸው ብዙ ነዋሪዎች አጋጥመውኛል። የመንግስት ደጋፊዎች በበኩላቸው “ትልቁ አሳ ወጥመድ ውስጥ ገብቷል!” ብለው ያምናሉና ጮቤ ከመርገጥ ባለፈ በትምክህት ” እኛ እንዲህ ነን! ” በሚል በኩራት ሲናገሩ አድምጫለሁ ! በማህበራዊ ድረ ገጾችና በሰሚ ሰሚ ወሬው ደርሶት አስተያየት ላለመስጠት የሚሸሸው ነዋሪ ብዙ ቢሆንም በሆነው ሁሉ ያደረበትን ስጋት ከመግለጽ አልተቆጠበም ።

በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ መታገትና ለኢትዮጵያ መንግስት መተላለፍ ከተደሰቱት ውጭ ያለው ብዙ ነዋሪ የበቀል እርምጃና የጥላቻው መተነኳኮስ ሃገሪቱን ወደ ለየለት ብጥብጥ እንዳይዶላት በነዋሪው ላይ ታይቶ የማይታወቅ ስጋት አጭሯል ።

“ዲሞክራሲና ሰብአዊ መብትን አላስከበራችሁም !” በሚሉ ተቃዋሚ ቡድኖችና ” በሁለት አስርት አመታት ዲሞክራሲን አስፍኛለሁ፣ ሰብአዊ መብት አስከብሬያለሁ! ” በሚለው ኢህአዴግ መካከል አመታት የዘለቀው መጓተት ባመጣው ጣጣ በርካቶች ከግንቦት 7 ጋር ግንኙነት አላችሁ በሚል ዘብጥያ ወርደዋል። አቶ አንዳረጋቸውም ቢሆን በኢህአዲግ ላይ ጠንስሰዋል በተባለው መፈንቅለ መንግስት በሌሉበት የሞት ፍርድ የተበየነባቸው መሆኑ ሲታወስ ተይዘው ወደ ኢህአዲግ እጅ ተላልፈዋል የመባሉ ዜና በቀል አስቋጥሮ ፣ በዛቻና ፉከራው ታጅቦ ዳግም በፖለቲካ ትርምስ ፍጥጫ እንዳይከታትና ኢትዮጵያን ወደ ሌላ የመጠፋፋት አዙሪት እንዳያስገባት ስጋታቸውን የሚገልጹ ነዋሪዎች ቁጥር ቀላል አይደለም።

አዎ ! አረብ ሃገራት እንዲህ ናቸው ፣ በአረብ ሃገር ያለን ስደተኞች መከራ ብዙ ነው  እኔም የአገሬ ህዝብ በነቂስ ስለሚነጋገርበት ሰሞነኛ አጀንዳ ቢያገባኝ ይህችን ታክል መረጃ አቀብል ዘንድ ነፍሴ ፈቅዳለች ። ከዚህ ባለፈ መጻፍና መናገር ግን አቅሙ የለኝም ልበል ይሆን?

እስኪ ቸር ያሰማን !

ነቢዩ ሲራክ

LikeLike ·  · 
Filed in: Amharic