>

"ጊዜው ባይሆንም "ኦሮሞ ከአ.አ ይውጣ" ስለተባለ ነው ያን ምግለጫ ያወጣነው!!!" (አቶ በቀለ ገርባ)

“ጊዜው ባይሆንም “ኦሮሞ ከአ.አ ይውጣ” ስለተባለ ነው ያን ምግለጫ ያወጣነው!!!”

 አቶ በቀለ ገርባ 

ቢቢሲ

ሰሞኑን የኦሮሞ ሕዝብ አንድነት እና አንገብጋቢ የወቅቱ ጉዳዮችን አስመልክቶ አምስት የኦሮሞ የፖለቲካ ድርጅቶች የጋራ መግለጫ አውጥተው ነበር።

ፓርቲዎቹ በመግለጫቸው የኦሮሞ ማንነትን ለማጥፋት እየተደረገ ያለው ሙከራ ያሉትን፣ የአዲስ አበባ ጉዳይን፣ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩ ስላሏቸው ሚድያዎች፣

በሃገሪቱ እየታየ ስላለው ለውጥን እና በቋንቋ ላይ ስለተመሰረተ ፌዴራሊዝም ትኩረትን ሰጥተዋል።

መግለጫው ከተሰማ ወዲህ አነጋጋሪ ሆኖ የተገኘ ሲሆን ጊዜውን የጠበቀ አይደለም፣ ከፋፋይ እንዲሁም አንድ ፓርቲ ላይ ያነጣጠረ ነው የሚሉ ትችቶች ሲሰነዘሩበት ቆይቷል።

እኛም ይህን አስመልከተን ከፓርቲዎቹ መካከል አንዱ የሆነው የኦፌኮ ምክትል ተቀዳሚ ሊቀ-መንበር ከሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ጋር ቆይታ አድርገናል።

ቢቢሲ፦ መግለጫውን አሁን ማውጣት ያስፈለገበት ምክንያት ምንድነው?

አቶ በቀለ፦ ሰሞኑን ውጭ ሃገር ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ወደ ሃገር ውስጥ መግባታቸውን ተከትሎ በተለይም ከመስከረም 5 በኋላ ባሉ ቀናት የኦሮሞ ንብረት የሆኑ ተቋማት ላይ፣ የክልሉን ታርጋ በለጠፉ መኪናዎች ላይ እንዲሁም በኦሮምኛ ተናጋሪዎች ላይ ከተማው ወስጥ ጥቃት ተፈፅሟል።

ይህ ነገር ዝም ብሎ ሊታለፍ የሚገባው ባለመሆኑ መግለጫውን ማውጣት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል።

የኦሮሞ ማንነት ላይ ጥቃት እየተሰነዘረ በመሆኑና ይህን የሚያደርጉ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ነው መግለጫውን ያወጣነው።

ቢቢሲ፦ መግለጫው ስሜታዊነት ይነበብበታል፤ በተፈጠሩት ግጭቶች ሕይወታቸው ላለፈ እንኳን የሃዘን መግለጫ አልሰጠም የሚሉ ትችቶች ይሰማሉ። ይስማሙበታል?

አቶ በቀለ፦ ከዚህ መግለጫ በፊት ሌላ መግለጫ ማውጣታችን ይታወቃል። የኦሮሞ የፖለቲካ ድርጅቶችና ሌሎችም ፓርቲዎች ጥቃቱን በማውገዝ መግለጫ አውጥተናል።

ድርጊቱ አሳዛኝ መሆኑንና የዜጎች መሞት ተገቢ አለመሆኑን አስፍረን ሃዘናችንን ገልፀናል።

በዚህኛውም መግለጫ ላይ በፅሁፍ ባይሰፍርም በቃል በሰጠነው መግለጫ ላይ የማንም ሰው ሕይወት መጥፋት አንደሌለበትና በድርጊቱ ማዘናችንን ገልፀናል።

በፅሁፍ መግለጫው ላይ አለመካተቱ ስህተት ሊሆን ይችላል፤ ለዚያም ይቅርታ መጠየቅ ይገባል። ከዚያም ባለፈ የኦሮሞ ቄሮዎች መስቀልን ምክንያት በማድረግ ወደ አርባምንጭ ይቅርታ እንዲጠይቁ የተደረገ መሆኑን ማስገንዘብ እንፈልጋለን።

ቢቢሲ፦መግለጫችሁ ላይ ፀረ-ኦሮሞ አቋም ያለው ድርጅት እንዳለ መረጃ አለን ብላችኋል። የዚህን ድርጅት ስም መጠቀስ ያልፈለጋችሁት ለምንድነው?

አቶ በቀለ፦ ይሄ ወደፊት ወደ ሕግ አግባብ ሲገባ ይፋ ሊሆን የሚችል ነው። ነገር ግን የተደራጀ ስለመሆኑ የሚያመልክቱ ነገሮች አሉ። በተለያዩ ቦታዎች ላይ የኦሮሞ ንብረቶች ላይ ጥቃት ሲፈፀም ይህ በአጋጣሚ ነው ብሎ ማሰብ ከባድ ነው።

ስለዚህ ከላይ ሆኖ የሚያስታባብር አካል ስለመኖሩ እሙን ነው። አሁን ባለው ሁኔታ ከሕግ አግባብም ጭምር ይሄ ድርጅት ነው ብሎ ማለት አስፈላጊ አይደለም።

ወደፊት አስፈላጊ ከሆነ ማጋለጥ የሚያስፈልግበት ሁኔታ ሊኖር ይችላል ማለት ነው።

ቢቢሲ፦ እናንተ የኦሮሞ ንበረቶች ላይ ጥቃት እየደረሰ ነው ብላቸሁ እንደምትሉት ሁሉ የተለያዩ ሰዎች ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ጥቃት ደረሰብን ሲሉ ይሰማል። በዚህ ምክንያት እናንተም እየፈረጃችሁ ነው ማለት አይቻልም?

አቶ በቀለ፦ እንደዚህ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ጉዳዩ ከምን ተነሳ የሚለው ነው። ጉዳዩ ከምን ተነሳ የሚለውን መንግሥት ሊያጣራ ይችላል።

ከፓርቲዎች አቀባበል ጋር በተያያዘ ብዙ የተፈፀሙ ጥቃቶችን ማንሳት ሃዘን መቀስቀስ ነው።

ተቃውሞ ሰልፍ ፈቃድ መጠየቅ፣ በሚድያዎች ላይ ማራገብ የመሳሰሉ ጉዳዮችን አስተውለናል። ግን በማናቸውም ዜጋ ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች ፈፅሞ ትክክል ያልሆነና እኛ የማንፈልገው መሆኑን ለማሳሰብ ነው።

ከየትኛውም ወገን ችግሮች ደርሶ ሊሆን ይችላል፤ ሰዎችም ሞተዋል፤ ይህ ትክክል ነው። በሁለቱም ወገን ይህንን ጉዳይ የፈፀሙ ሰዎች ወደ ሕግ መቅረብ እንዳለባቸው በመግለጫችንም ጠይቀናል።

ቢቢሲ፦ሌላኛው የመግለጫው አከራካሪ ክፍል አዲስ አበባን አስመልክቶ የወጣ ነው፤ መግለጫው ‘አዲስ አበባ የኦሮሞ ናት’ ይላል። መግለጫው ከወጣ በኋላ ‘አዲስ አበባ የናንተ ሳትሆን የኛ ናት’ የሚሉ ወገኖች በዝተዋል። ስለዚህ አዲስ አበባ የባለቤትነት ጥያቄ ለማንሳት አሁን ጊዜው ነው ብለው ያስባሉ?

አቶ በቀለ፦ እርግጥ ጊዜውም አይደለም። ይህ አካባቢ የኔ ነው ያንተ ነው ለማት ጊዜው እንዳልሆነ ይታወቃል። አስፈላጊነቱም ያን ያህል ነው።

ነገር ግን ይህንን እንድንል ያነሳሳን የአንድ ፓርቲ አርማ የያዙ ሰዎች አዲስ አበባ የኦሮሞ አይደለችም፤ ኦሮሞ ከአዲስ አበባ ይውጣ የሚል ግልፅ መፈክር ይዘው ወጥተዋል።

መታወቅ ያለበት ጉዳይ ስለሆነ እንዲታወቅ የተደረገ ስለሆነ እና ተያያዥ ጥቃቶች ስለደረሱ እንጂ ጊዜው እንዳልሆነ እሙን ነው።

ቢቢሲ፦ ‘አርማውን ይዘው ወጥጠተው ያልተገባ ነገር አሳይተዋል’ የተባለውን ፓርቲ ማነጋገር አይቀልም ነበር፤ መሰል አከራካሪ መግለጫ ከመስጠት?

አቶ በቀለ፦ በፓርቲዎች መካከል መሰል ውይይት አልተለመደም፤ ነገር ግን ሁኔታው በተፈጠረ ማግስት ፓርቲዎች ተሰብስበን የጋራ መግለጫ አውጥተን ነበር።

ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከማናቸውም ተንኳሽ ተግባሮች እንዲቆጠቡ የሚል ግንዛቤም ወስደን ነበር።

ቢሆንም ይህንን ስምምነት ተግባራዊ ያላደረጉ ኃይሎች በመገኘታቸው እና ከዛ በላይ መነጋገርም ብዙም አዋጭ ሆኖ ባለመገኘቱ መግለጫ ማውጣትና በዛ መልክ መገናኘት ይሻላል በሚል ነው ወደዚያ ያመራነው።

እኛ ቃላችንን ሳናጥፍ ደጋፊዎቻችንና አባሎቻችን ራሳቸውን እንዲያቅቡ አድርገናል፤ ሙከራ አላደረግንም ማለት ግን አይቻልም።

ቢቢሲ፦ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩ ሚድያዎች ሊተቃቡ ይገባል ብላችሁ ኢሳት የተሰኘው የሚድያ ተቋም ላይም አተኩራችኋል። ኢሳት ላይ ማተኮር ለምን አስፈለገ?

አቶ በቀለ፦ ኢሳት ሃገሪቱን አንድ የማድረግ ሚና አይደለም እየተጫወተ ያለው። ሕዝቡን አንድ የሚያደርግ ሚና አይደለም እየተጫወተ ያለው።

የተወሰኑ ድርጅቶችን ወይም የፖለቲካ ፓርቲን ግምት ውስጥ በማስገባት በሌሎች ድርጅቶች እና ግለሰቦች ላይ ግን ዘመቻ በመክፈት ላይ ያለ መሆኑን የምንገነዘበው።

መሰል ሁኔታዎች የሚስተዋሉት ደግሞ ‘የፖለቲካ ተንታኝ’ ተብለው በሚጠሩ ግለሰቦች አማካይነት ነው።

ይህንን ለማስተዋል ተቀርፀው የተቀመጡ ማህደሮችን ማገላበጥ ይበቃል። ከዚህ መግለጫ በኋላ እንኳን ተንታኞቹ የሰጡት አስተያየት በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው።

ከመግለጫው ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸው ሰዎች ሁሉ ኦሮሞ በመሆናቸው ብቻ የስም ማጥፋት ዘመቻ ተከፍቶባቸዋል። በጣም ተንኳሽ የሆኑ ቃላትን በመጠቀም የኔን ስም ሁሉ ሳይቀር ሲያንኳስሱ ነበር።

ከበፊት ጀምሮ ኢሳት የሚያስተላልፋቸው ዘገባዎች ሃገር ገንቢ አለመሆናቸውን ሁሉም ያውቀዋል። እኔ መግለጫውን ካወጡት መካከል ነኝ።

በአቋሞቹ አምንበታለሁ። ምላሴን አላጥፍም። ነገር ግን በግሰለሰብ ደረጃ ሳይሆን በድርጅት ደረጃ ያወጣነው መግለጫ ነው።

እኔ ብቻዬን እንዳወጣሁ አድርጎ በማቅረብ ኃላፊነት የጎደለው ሥራ ሠርተዋል።

ኢሳት ትላንትም ዛሬም ሚዛናዊ አይደለም፤ ትላንትም ዛሬም ለኢትዮጵያ አንድነት እየሠራ ያለ ተቋም ነው ብዬ አላስብም።

ቢቢሲ፦ ከሚድያ ጋር ተያይዞ የተነሳው ሌላው ትችት፤ ሌሎች ሃገር በውስጥም በውጭም ያሉ ሚድያዎች መወቀስ አለባቸው የሚሉ አሉ?

አቶ በቀለ፦ እኛ ሁሉንም ሞኒተር (መቆጣጠር) ማደረግ የምንችልበት አቅም የለንም። ነገር ግን የግልም የመንግሥትም ሚድያዎች ሚዛናዊ ያልሆነ ዘገባ ሲያስተላልፉ እንደበሩ ገልፀናል። ዛሬም እምነታችን ነው።

ኢሳትን የሚያህል ሚዛናዊ ያልሆነ ዘገባ የሚያቀርብ እስከዛሬ ድረስ አላየሁም። ኢሳትን የሚስተካከል የለም ማለታችን ነው እንጂ ሌሎቹ አይደሉም ማለታችን አይደለም።

ኦኤምኤን ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን በዚህ ደረጃ ሊወዳደሩ የሚችሉ ተቋማት ናቸው ብዬ አላምንም።

ቢቢሲ፦ ሌላው መከራከሪያ ደግሞ አቶ በቀለ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ በፊት የነበረውን አመራር የተዋጉት ኢሳትን የመሳሰሉ ሚድያዎችን በመጠቀም ነበር የሚል ነው?

አቶ በቀለ፦ እኔ እንደ ፖለቲከኛ ማንኛውንም ሚድያ እጠቀማለሁ። የእናንተን ሚድያ ተጠቅምኩ ማለት እናንተን ደገፍኩ ማለት አይደለም።

ሚድያ ደግሞ አንደ ሁኔታው ‘ስትራቴጂ’ ይቀይራል። ከማን ጋር መቼ መሥራት እንዳለበት ይወጥናል። እኔ የነሱን ሚድያ ከተጠቀምኩ ቆይቻለሁ።

ሰሞኑን የነበረውን ጉዳይ ለማብራራት ፈልጌ ላገኛቸው አልቻልኩም፤ የተወራው ግን ተቃራኒው ነው። ማንኛውም ሚድያ ሚዛናዊ እስከሆነ ድረስ ሃሳቤን እገልፃለሁ። ትላንትና እነሱን በመጠቀሜ ዛሬ ልተቻቸው አልችልም ማለት አይደለም።

ቢቢሲ፦ የእርስዎን ፓርቲ (ኦፌኮ) ጨምሮ መግለጫ ያወጡት ድርጅቶች በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ፌዴራሊዝም የሥርዓቱ ችግር መንስዔ ነው ብላችሁ እንደማታምኑ አሳውቋችኋል። በእርስዎ እምነት የችግሩ መንስዔ ምንድነው?

አቶ በቀለ፦ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አለመገንባቱ ነው። ሕገ-መንግሥቱ ላይ ያሉ ዴሞክራሲያዊ መብቶች መሬት ላይ መውረድ አለመቻላቸው፣ ሕዝቡ ራሱን በራሱ እንዲያስተዳድር አለመደረጉ፣ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ አለመካሄዱ እና የሰው ልጅ መብት መረጋገጡ ነው ትልቁ ችግር።

አሁን ያለው በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ፌዴራሊዝም ያመጣው ችግር ስለመሆኑ የሚያረጋግጥ አንዳችም ጥናት የለም።

እንዲህም ሆኖ ሕዝቡ አሁን ያለውን የፌዴራሊዝም ሥርዓት አንፈልግም፤ ሕገ-መንግሥቱ መሻሻያ ይደረግበት ካለ ሕግን ተከትሎ ማድረግ ይቻላል።

ቢቢሲ፦ ጥናት ባይኖር አንኳ ሃገሪቱ አሁን ያለችበትን ሁኔታ ተመልክተን ሥርዓቱ አዋጭ አለመሆኑን መናገር እንችላለን የሚሉ ወገኖች ደግሞ አሉ?

አቶ በቀለ፦ እርግጥ ነው እንደዚህ የሚሉ አሉ። እኛ ደግሞ የከፋፈለን የፌዴራሊዝም ሥርዓቱ አይደለም፤ የከፋፈለን ነገር ሌላ እንደሆነ ነው የምናምነው።

ይህ አይደለም፤ ይህ ነው የከፋፈለን እያሉ ሌላ መከፋፈያ ምክንያት ከመስጠት ለሕዝቡ በመረጠው መሪ እንዲተዳደር ዕድሉን እንስጠው ነው የምንለው።

ቢቢሲ፦ የከፋፈለን ማነው? ወይም ምንድነው ብለው ነው የሚያስቡት?

አቶ በቀለ፦ የከፋፈለን አተገባበሩ ነው። ሕዝቦች ራሳቸውን በራሳቸው ያለማንም ጣልቃ ገብነት ማስተዳደር አለመቻላቸው ነው። ራሳቸው በመረጡት መንግሥት መተዳደር አለመቻላቸው ነው። ሕገ-መንግሥቱ በትክክል ሥራ ላይ አለመዋሉ ነው። እኔ አውቅልሃለሁ፣ የእኔ ቋንቋ፣ የኔ ባህል ካንተ ይሻላል የሚሉ ሰዎች ጫና ለመፍጠር በሚያደርጉት ሩጫ ሃገር ወደትርምስ ገብታለች የምንለው።

ቢቢሲ፦ አሁን ባለው የሃገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ የኦሮሞ የበላይነት አለ ብለው ያስባሉ?

አቶ በቀለ፦ እኔ አለ ብዬ አላስብም። አለ ብዬ ባስብ በመጀመሪያ ደረጃ ለመቃወም የምነሳው እኔ ነኝ።

የታሠርኩት፣ የታገልኩት ወደፊትም የምታገለው ለማንም ብሔር የበላይነት አይደለም። የማንም ብሔር የበላይነት ባለበት ሃገር ውስጥ ዝም ብዬ መቀመጥ አልሻም።

እኔ ሰብዓዊ ፍጡር ነኝ፤ በአጋጣሚ ከአንድ ብሔር የተወለድኩ ሰው ነኝ። ትላንት ለተገኘሁበት ብሔር መብት የታገልኩ ሰው ነኝ። የታገልኩትም የሌላውን ብሔር መብት ለመንፈግ አይደለም። የአንድ ብሔር የበላይነት ምልክት ባይ እንኳ እቃወማለሁ።

ቢቢሲ፦ ፓርቲዎ (ኦፌኮ) አሁን የሚታገለው ማንን ነው? ገዢውን መንግሥት?

አቶ በቀለ፦ እኛ የምንታገለው ምንም የተወሰነ ብሔር የለንም፤ የምንታገለው ለሕዝቦች ነፃ ምርጫ ነው።

እኛም አንድ አንድ ፓርቲ በነፃነት ተወዳድረን፣ ሃሳባችንን አቅርበን፣ ሕዝቡ ከፈለገን ተመርጠን ካልሆነ ደግሞ ለተመረጠው መገዛት ነው የምንፈልገው።

ከተወሰነ ቡድን፣ ብሔር ወይም ፓርቲ ጋር አይደለም ትግላችን፤ ለሕዝቦች ነፃነት እንጂ። ለኦሮሞ ነፃነት ብቻ አይደለም። ሁኔታዎች አስገድደውን ነው ዝቅ ብለን በብሄር ደረጃ እንድንታገልን የሆነው።

ወደፊት ሕብረ-ብሔራዊ እና ሁሉንም ሕዝብ እኩል የሚመለከት ፓርቲ በሚፈጠር ጊዜ የእኛም ፓርቲ ህልውና አላስፈላጊ ይሆናል ማለት ነው።

ቢቢሲ፦ አሁን ላይ በሃገሪቱ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ እየተንቀሳቀሰ እንዳለ አንድ የፖለቲካ ሰው ስለወደፊቱ ሲያስቡ ምን ይሰማዎታል? ስለኢትዯጵያ ሲያስቡ?

አቶ በቀለ፦ እኔ ባለሙሉ ተስፋ ነኝ። አንድ የማምንበት ነገር አለ። ፍትህ፣ እውነት ብትረገጥም አንድ ቀን ቀና ማለቷ አይቀርም። ሃሰት የሚነዙ ግለሰቦች የትም እንደማይደርሱ አውቃለሁ።

መንገጫገጭ ሊኖር ይችላል፤ እኔ ግን የሚታየኝ አሁንም መልካም ነገር ነው። ችግሮች ሊኖሩ ይችላሉ። የማስመሰል ፖለቲካ ሊኖር ይችላል።

ግጭቶች እዚህም እዚያም ሊኖር ይችላል። ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ግን ሁሉም ነገር ይረጋጋል የሚል እምነት ነው ያለኝ።

Filed in: Amharic