>

ሰፊ የህዝብ ድጋፍ ያለው መንግስት ጨቋኝ የመሆን እድሉ ሰፊ ነው!!! (ሳሙኤል ገዛህኝ)

ሰፊ የህዝብ ድጋፍ ያለው መንግስት ጨቋኝ የመሆን እድሉ ሰፊ ነው!!!
ሳሙኤል ገዛህኝ
 
”መንቀል እንጅ መትከል አናውቅም” (የፕሮፍ መስፍን አባባል ነው) እርግጥ ነው ኢትዮጵያውያን ችለው ችለው አድፍጠው ጨቋኞችን መንቀል ይችላሉ:: እንችላለን:: በነቀልነው ክፉ መንግስት ፈንታ የህዝብ መንግስት ተክሎ ስር ስድዶ ለፍሬ እስኪበቃ መከታተል ግን አናውቅም::
ጨቋኙ ህወሃት ብሶት በወለደው ህዝብ ተነቅሏል:: የአብይ መንግስት የህዝብ መንግስት ነው:: በህዝብ ይሁንታ በህዝብ ፈቃድ የተተከለ::
የአብይ መንግስት ያልጠና ገና ለጋ መንግስት ነው:: በፍትህ: በእኩልነት እና በዴሞክራሲ የፀና ሆኖ ስር እንዲሰድድ የተከልነው እኛ የመከታተል የመንከባከብ ሃላፊነት አለብን::
ለመንቀል ከሚፈጀው ጊዜና ትእግስት ያላነሰ ተንከባክቦ ስር እንዲሰድድ በደምብ እንዲፀድቅ ማድረጉ ብዙ ጊዜ: ትእግስት: ዘዴም ይጠይቃል::
የተከልነውን የአብይ መንግስት ስር ስድዶ እንዲፀድቅ የሚከተሉትን ጥቂት ጉዳዮች አሁን ማድረግ እና መከታተል ያለብን ይመስለኛል::
– ለጨቋኙ መንግስት መነቀል ምክንያት የሆኑ እና ለአብይ መንግስት ይሁንታ የስጠንባቸው: ተስፋና ጥያቄዎች በፍጥነት በስርዓት እና በህግ እንዲ ደነገጉ መጠየቅ መከታተል::
– ተስፋ የተገቡ የህዝብ ጥያቄዎች መቼ በህጋዊ ማእቀፍ እንደሚመሰረቱ መጠየቅ መከታተል:: በዚህ ጊዜ ውስጥ ይህ ይደረጋል ሊባል ይገባል::
– የሚድያ ህግ: የህገ መንግስት አንቀፆች: የፀረ ሽብር ህግ: የመያዶች ህግ:… የመሳሰሉት መቼ እና እንዴት እንደሚሻሻሉ እንደሚፈፀም መጠየቅ::
– የህዝብን እና የአገር ሀብት በመዝረፍ የታወቁ ግለሰቦች እና ድርጅቶች እንዲመረመሩ ወይም ለፍርድ እንዲቀርቡ መጠየቅ:: ይህ በጊዜ ገደብ መታወቅ አለበት መቼ እንደሚፈፀም::
– የዜጎችን ሰብአዊ ምብት በመጣስ አሰቃቂ ወንጀል የፈፀሙ ግለሰቦችና ድርጅቶች በታወቀ ጊዜና ግልፅ በሆነ ሁኔታ ለፍርድ እንዲቀርቡ መጠየቅ:: ጥፍራቸው የተነቀለ: እግራቸው የተቆረጠ: እርቃናቸውን የተዋረዱ: የተደፈሩ: ቶርቸር የተደረጉ ወገኖች እንዲካሱ: ፍትህ እንዲያገኙ መጠየቅ::
– በመላው አገሪቱ በተለይ በሶማሌ ክልል ለዜጎች መፈናቀል እና ሞት ለሀብት ውድመት እና ዝርፊያ ተባባሪ እና ተሳታፊ እንደሆኑ የሚጠረጠሩ የጦሩ ጀነራሎች እና የህወሃት አባላት ለፍርድ እንዲቀርቡ መጠየቅ::
አደባባይ ወጥቶ ጨቋኙን ህወሃት የነቀለው ቄሮው: ፋኖው: ዘርማው: የሶማሌው: የደቡቡ: የመላው ኢትዮጵያ ወጣት አሁን ያለውን መንግስት በተደራጀና ግልፅ በሆኑ ጉዳዮች ከፍ ብለው የተጠቀሱትና ሌሎችም ጉዳዮች ባስቸኳይ ምላሽ እንዲያገኙ የአብይን መንግስት በአደባባይ ወጥቶ መጠየቅና ጫና ማሳደር ያስፈልጋል::
ክትትል እና ጥበቃ የማይደረግበት ከልክ በላይ የህዝብ ድጋፍና ይሁንታ ያለው መንግስት እጅግ ጨቋኝ የመሆን እድሉ ከፍተኛ ነውና ቁጥጥር ክትትል ሊደረግበት ይገባል:
Filed in: Amharic